Friday, December 12, 2014

ኢትዮጵያዊው “ጌታቸው ካሳ” እና ሱዳናዊው “ሳላሕ ኢብን ባዲያ”




አፈንዲ ሙተቂ
----
የአንጋፋው አርቲስት የጌታቸው ካሳ እውነተኛ ስም “ጌታቸው እሸቴ” ነበረ፡፡ ይህ አርቲስት በኪነ-ጥበቡ ተማርኮ መዘፋፈን ሲጀምር አባቱ ድምጹን በሬድዮ ይሰሙታል፡፡ አባት “ልጅህ አዝማሪ ነው” መባላቸው ክብራቸውን የሚቀንስ ሆኖ ስለተሰማቸው ልጃቸውን ያስጠሩትና እንዲህ አሉት፡፡ “ከዛሬ በኋላ ከዘፈንክ ግንባርህን በጥይት እበሳዋለሁ”፡፡
 
Salah ibn Badiya, One of the legendary Sudanese pop stars.

 ልጅ ጌታቸው ግን በአባቱ ማስፈራሪያ አላረፈረም፡፡ ከውስጡ የሚንቀለቀለው የጥበብ ዛር አላስቀምጥ ስላለው ከአባቱ እየተደበቀ ወደ ዘመኑ ክለቦችና ልዩ ልዩ መድረኮች ጎራ እያለ መዝፈኑን ቀጠለ፡፡ በዚህን ጊዜም በአንጋፋው ጋዜጠኛ ጌታቸው ደስታ ዐይን ውስጥ ገባ፡፡ ጌታቸው ደስታም ወጣቱን ድምጻዊ በሬድዮ እንዲዘፍን ጋበዘው፡፡ ነገር ግን የዘፋኙ አባት ልጃቸው በሬድዮ እንደዘፈነ ቢሰሙ በልጁ ላይ አደጋ ሊያደርሱ እንደሚችሉ ገመተ፡፡ ስለዚህ ወጣቱን ለመደበቅ እንዲቻል ስሙን “ጌታቸው ካሳ” በማለት ቀየረው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ተወዳጁ አርቲስት ላለፉት አርባ አምስት ዓመታት ጌታቸው ካሳ ተብሎ እየተጠራ ነው፡፡
*****
አንጋፋው ሱዳናዊ ድምጻዊ “ሳላሕ ኢብን ባዲያ”ም ከኛው ጌታቸው ካሳ ጋር የሚመሳሰልበት ታሪክ አለው፡፡ የሳላሕ እውነተኛ ስሙ ሳላሕ ሼኽ ሙሐመድ ነበረ፡፡ በወጣትነቱ የዘፈናቸው ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ሲተላለፉ አባቱ እሳት ጎርሰው እሳት ለብሰው መጡለት፡፡ “አንተ አዝማሪ! ልታዋርደኝ ነው የምትፈልገው?… ከዛሬ ጀምሮ በኔ ስም የምትጠራ ከሆነ እረግምሃለሁ! ውርድ ከራሴ!” በማለት አስጠነቀቁት፡፡

  ሳላሕ የአባቱን ማስጠንቀቂያ ተቀበለ፡፡ ነገር ግን የአባቱን ስም ትቶ በሐሰት ስም መጠራቱን ነፍሲያው አልቀበል አለች፡፡ አሕመድ፣ ሰይድ፣ ኢብራሂም፣ ሱፍያን በመሳሰሉት የዐረብኛ ስሞች መጠራቱ አላመችህ አለው፡፡ ማን ተብሎ ይጠራ እንግዲህ?….  አንድ ቦታ ቁጭ ብሎ ሲያሰላስል እንዲህ የሚል ሐሳብ መጣለት፡፡

  “ሳላሕ አንተ የተወለድከው በገጠር ነው አይደል?… ለምን የገጠር ልጅ ነኝ ብለህ አትጠራም?… እግረ መንገድህንም የገጠር ሰው ታላቅ ተአምር መስራት እንደሚችል ታሳይበታለህ”

ሳላሕ በድንገት ውልብ ያለበትን ሓሳብ በተግባር ላይ ሊያውለው ተነሳ፡፡ የመጀመሪያ አልበሙን ሲያሳትምም “ሳላሕ ኢብን ባዲያ” (ሳላሕ የገጠር ልጅ) የሚል ስም ተጠቀመ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለሃምሳ ዓመታት በዚህ ስም እየተጠራ ነው፡፡
*****
ሳላሕ ኢብን ባዲያ ሱዳን ካበቀለቻቸው አንጋፋ አርቲስቶች አንዱ ነው፡፡ የሱዳንን ሙዚቃ በፍቅር የሚያዳምጡ አድናቂዎቹ በተለይም እንደ ብራቅ በሚወጣው ድምጹ በጣም ይገረማሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት እድሜው ወደ ሰባዎቹ አጋማሽ ቢሆንም በአዘፋፈን ዘይቤው ላይ ምንም ድካም አይታይበትም፡፡
ከሳላሕ ኢብን ባዲያ ዘፋኖች መካከል የሀገራችን ሙዚቃ አፍቃሪያን በደንብ የሚያዉቁት “ሻዕረ ዘሐብ” የሚለውን ዜማ ይመስለኛል፡፡ በነገዋ ዕለተ ቅዳሜ ከሳላሕ ቢን ባዲያ ጋር በሓሳብ ወደ ኦምዱርማን ትበሩ ዘንድ ይህንኑ ጨዋታ ጋብዘናችኋል፡፡
(ሳላሕ “ሻዕረ ዘሐብ”ን ሲዘፍን ለማየት ይህንን የዩቲዩብ ሊንክ ይክፈቱ)
-----
አፈንዲ ሙተቂ
ታሕሳስ 4/2007
ሀረር-ምሥራቅ ኢትዮጵያ
---
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links



No comments:

Post a Comment