Thursday, May 29, 2014

“ሰይድ ኸሊፋ” ሲዘከር



ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
--------

ቃር ቃር የሚለውን የሰሞኑ የጭንቀት ሰቀቀን በምንፈልገው መጠን  እንድንጫወት ባይፈቅድልንም በተገኘችው አጋጣሚ ሩሓችን “ኢስቲራሓ” እንድታደርግ ልንፈቅድላት ይገባል፡፡ በዛሬ ውሎአችን የሚያናፍሰን ደግሞ አንጋፋው ሱዳናዊ ድምጻዊ ሰይድ ኸሊፋ ነው፡፡ ጉዞ ወደ ቢላድ- አስ-ሱዳን! ጉዞ ወደ ኻርቱም! ጉዞ ወደ ኡምዱርማን! ጉዞ ወደ ከሰላ፣ ጉዞ ወደ ዋዲ ሀልፋ፣ ጉዞ ወደ ገዳሪፍ፣ ጉዞ አል-ኡቤይድ! ጉዞ ወደ ኮርዶፋን! ዳይ!!
---------
ከየትኛው እንጀምር እንግዲህ! ሰውዬው በበርካቶቻችን አዕምሮ ውስጥ የገዘፈ ምስል ጥሎብን ያለፈ በመሆኑ “ከሀ እስከ ፐ” እያሉ ስለርሱ ማውራቱ ያስቸግራል፡፡ ለማንኛውም በካይሮ ከተፈጠረ አንድ ክስተት ብንጀምር ጥሩ ይመስለኛል፡፡

ዘመኑ ራቅ ብሏል፡፡ በ1940ዎቹ አጋማሽ ነው፡፡ እውቁ የካይሮ ዩኒቨርሲቲ ለዓለም አቀፍ ተማሪዎች በሰጠው የስኮላርሺፕ እድል በመጠቀም በርካታ ሱዳናዊያን በዩኒቨርሲቲው ይማሩ ነበር፡፡ ከነዚያ ወጣቶች መካከል አንዱ በሙዘቃ ትምህርት ቤት የተመደበ ጠይም ዘለግ ያለ ኮበሌ ነው፡፡ ያ ወጣት በቤተሰቡ ወደ ግብጽ የተላከው ህግ አጥንቶ ጥሩ ዳኛ እንዲሆን ነበር፡፡ እርሱ ግን በራሱ ፍላጎት ምርጫውን ወደ ሙዚቃ አዞረ፡፡ በመሆኑም በእውቁ የዐረብ ሙዚቃ አካዳሚ ሊማር ተመዘገበ፡፡ ወጣቱ ሱዳናዊ ሙዚቃን በሀገር ቤት ያንጎራጉር ነበር፡፡ በትምህርት ቆይታውም በሀርሞኒካ እየተጫወተ ጓደኞቹን ያዝናናል፡፡

   አንድ ቀን ዩኒቨርሲቲው ለተማሪዎቹ ባዘጋጀው ታላቅ የሙዚቃ ድግስ ላይ እንዲዘፍን የተጋበዘው ፈሪድ አል-አጥራሽ የተባለው የዘመኑ ታዋቂ ግብጻዊ ዘፋኝ በሰዓቱ ይመጣል ተብሎ ሲጠበቅ የውሃ ሽታ ሆኖ ይቀራል፡፡ አዳራሹን ከዳር እስከ ዳር ያጨናነቁት ተማሪዎች በትዕግስት ጠበቁ፡፡ ነገር ግን ፈሪድ አል-አጥራሽን የበላ ጅብ አልጮኽ አለ፡፡ በመጨረሻም በአዳራሹ የነበረው ታዳሚ በጩኸትና በፉጨት ንዴቱን መግለጽ ጀመረ፡፡ ታላቁን ዘፋኝ ሲጠባበቅ የነበረው መድረክም በንዴተኛ ተማሪዎች ረብሻ ትርምስምሱ ወጣ፡፡
  
   የዩኒቨርሲቲው መምህራንና ሰራተኞች የተማሪዎቹን ቁጣ ለማብረድ አልቻሉም፡፡ ይሁንና ከሱዳናዊው ወጣት ተማሪ ጋር ይቀራረብ የነበረው አንድ አስተማሪ ወጣቱን እየገፋ ወደ መድረኩ አስገባውና “ዝፈን” አለው፡፡ ወጣቱ ሙዚቃን ለራሱና ለጓደኞቹ መደሰቻ ያህል ነበር የሚጫወተው፡፡ ህዝብ በተሰበሰበት አዳራሽ ላይ ቆሙ መዝፈኑን ቢመኘውም በዚያ ዕድሜው በባዕድ ሀገርና በባዕድ ታዳሚ ፊት ምኞቴን አደርገዋለሁ የሚል ሀሳብ አልነበረውም፡፡ እስከዚያን ጊዜ ድረስ በህዝብ ፊት መዝፈንን አልተለማመደውም፡፡ ስለዚህ የአስተማሪው ግብዣ በፍርሃት ማጥ ውስጥ ወረወረው፡፡

ይሁንና ወጣቱ ግብዣውን “እምቢ” ብሎ ከመድረኩ ለመውረድ አልሞከረም፡፡ እንደዚያ ቢያደርግ በፈሪድ አል-አጥራሽ መቅረት የተቃጠሉት ተማሪዎች ቁጭታቸውን በርሱ ላይ የሚወጡ መሰለው፡፡ ከተማሪዎቹ ቁጣ ለመዳን ሲልም እንደ አቅሙ ዘፍኖ ከመድረኩ ለመውረድ ወሰነ፡፡ በመሆኑም በፍርሃት እየራደና እየተርበተበተ ማይክራፎኑን ጨበጠ፡፡ የአዳራሹ ጸጥታ “ረጭ” ሲልም በቀጭን ድምጽ “አል-ማምቦ ሱዳኒ” (የሱዳን ጭፈራ) እያለ ዘፋፈነ፡፡ በፈሪድ አል-አጥራሽ መጥፋት የበገኑት ተማሪዎች ድንገት በመድረኩ ላይ በተከሰተው ሱዳናዊ ወጣት የድምጽ ቅላጼ ተማረኩ፡፡ ወጣቱ ዘፈኑን ሲጨርስ በከፍተኛ የአድናቆት ጭብጨባ አዳራሹን ቀወጡት፡፡ ዘፈኑንም ደግሞ እንዲዘፍንላቸው ጠየቁት፡፡

ሱዳናዊው ወጣት የስድብ ናዳ እንጂ የአድናቆት ጭብጨባ አልጠበቀም ነበር፡፡ የተማሪዎቹ ምላሽ የአድናቆት ጭበጨባ ሲሆንበት ግን መንፈሱ መለስ አለለት፡፡ በፍርሃት መንቀጥቀጡንም አስወገደ፡፡ እናም ዘና በማለት “አል-ማምቦ ሱዳኒን” እየደጋገመ ዘፈነ፡፡ የአዳራሹ ታዳሚ ከፊት በበለጠ ጭበጭባና አድናቆት አሞገሰው፡፡

የሱዳናዊው ወጣት ገድል በዚያ መድረክ ብቻ አልተገደበም፡፡ ስለድምጹ ማማርና ስለ ቅላጼው የሰማው ሁሉ በድግስና በሙዚቃ ኮንሰርት እንዲዘፍንለት ይጋብዘው ጀመር፡፡ በዘመኑ በካይሮ የሚኖሩት ከመቶ ሺህ በላይ የሚሆኑ ሱዳናዊያንም ወጣቱን የሀገር አለኝታና መታወቂያ አድርገው ወሰዱት፡፡ በየአጋጣሚው በሚያዘጋጇቸው የሙዚቃ ድግሶችም ወጣቱን ቁጥር አንድ ምርጫ በማድረግ አስዘፈኑት፡፡

ያ ወጣት የሙዚቃ ትምህርቱን በሚገባ ካጠናቀቀ በኋላ በ1946 ገደማ ተመረቀ፡፡ በታሪክ ሙዚቃን በአካዳሚ ደረጃ ያጠና የመጀመሪያው ሱዳናዊ ሆኖ ተመዘገበ፡፡ ከምርቃቱ በኋላ ወደ ሀገሩ ተመለሰ፡፡
---------
ይህ ነው እንግዲህ የሰይድ ኸሊፋ የዘፈን ጥንስስ! በዚህ መንገድ ነው እንግዲህ ዝነኛው ሱዳናዊ የጥበብ ጉዞውን የጀመረው፡፡ ይሁን እንጂ ሰይድ ኸሊፋ በመነሻው ላይ በካይሮ የተቀዳጀውን ዝና በሀገሪቱ ለመድገም አልቻለም፡፡ እንዲያውም መጀመሪያ ላይ የሱዳን ህዝብ “ዘፈን ሳያውቅ እዘፍናለሁ ብሎ የተነሳ መደዴ” የሚል የጥላቻ ቅጽል ለጥፎለት ነበር፡፡ ይህም የተፈጠረበት ምክንያት ሰይድ ኸሊፋ ይዞት የመጣው አዲስ የአዘፋፈን ዘውግ እና የግብጽና የኑቢያ ሙዚቃዎች ውህድ የሆነው የዘፈኖቹ ቅኝት ለሱዳናዊያን ጆሮ እንግዳ በመሆኑ ነው፡፡ ሱዳናዊያን በወቅቱ የለመዱት የአንጋፋዎቹን የነ በሺር አባስንና የነ አሕመድ አል-ሙስጠፋን የአዘፋፈን ስልት ነው፡፡ በመሆኑም እንደ ካሊፕሶ እና ዲስኮ ሞቅ እያለ የሚጓዘው የሰይድ ኸሊፋ ዘውግ ለነርሱ አልጣማቸውም፡፡

  እያደር ግን ሁሉም ነገር መስተካከል ጀመረ፡፡ ሱዳናዊያን ከሰይድ ኸሊፋ ስልት ጋር ተላመዱ፡፡ ከጥቂት አመታት በኋላ “መደዴ ዘፋኝ” የተባለው ወጣት የሁሉም ሱዳናዊ አርቲስቶች ቁንጮ ሆኖ ተገኘ፡፡ በተለይም “ኢዘየኩም” የተሰኘው ነጠላ ዜማው በኦምዱርማን ሬድዮ ሲለቀቅ ሱዳናዊያን ከዳር እስከ ዳር በአንድ ልብ አደመጡት፡፡ ስለቤተሰብና ፍቅርና ክብር የሚዘምረውን ዘፈኑን የሱዳን ብሄራዊ ዘፈን እስኪመስል ድረስ ተቀባበሉት፡፡

በ1950ዎቹ አጋማሽ ላይ የሰይድ ኸሊፋ ዝና በአባይ ግርጌ ካሉት ግብጽና ሱዳን ተነስቶ የአባይ ምንጭ ወደሆነችው ወደ ኢትዮጵያ ተሻገረ፡፡ ኢትዮጵያዊያንም ዘፈኖቹን ከመስማት አልፈው በአማርኛ፣ በኦሮምኛና በሶማሊኛ ቋንቋዎች እየተረጎሙ ዘፈኑት፡፡ በዚህም መሰረት ምኒልክ ወስናቸው “ጃሩ አነ ጃሩ” የሚለውን ዘፈኑን “ትዝታ አያረጅም” በሚል ቀይሮት ተጫወተው፡፡ ጥላሁን ገሠሠ ደግሞ “ወጠነል ጀማል” የሚለውን ተወዳጅ ዜማውን በአማርኛ ቋንቋ “እዩዋት ስትናፍቀኝ” በማለት ተጫወተው፡፡
-----
1961፡፡ የማይረሳ ዓመት፡፡ ኢትዮጵያዊያን በድምጹ ብቻ የሚያውቁትን ታዋቂ ዘፋኝ ያዩበት ዓመት፡፡ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት ከሱዳን ሪፐብሊክ መንግሥት ጋር ባደረገው የባህልና የኢኮኖሚ ግንኙነቶች ማዳበሪያ ስምምነት መሰረት አንጋፋና ወጣት ድምጻዊያን የተካተቱበት የሱዳን የሙዚቃ ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጣ፡፡ ዝግጅቱንም በቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ቴአትር (በአሁኑ ብሄራዊ ቴአትር) ማቅረብ ጀመረ፡፡ አሕመድ አል-ሙስጠፋ፣ በከር ሙስጠፋ፣ ኢብራሂም አውድ፣ ሳላህ ቢን ባዲያ እና ሌሎችም በታዳሚው ፊት ዘፈኑ፡፡ ከቆይታ በኋላ ግን ብዙዎች ሊያዩት የሚጓጉለት ሰይድ ኸሊፋ ወደ መድረኩ ተጋበዘ፡፡ አዳራሹ በአድናቆት ጭብጨባ ተናወጠ፡፡

ታዲያ ሰይድም ከህዝቡ ለተቸረው አድናቆትና ክብር አጸፋውን በአስገራሚ መልኩ መለሰ፡፡ በሁለት ሌሊቶች ውስጥ ያጠናቸውን የአማርኛ ቃላት ከዐረብኛ ጋር በማሰናኘት “ኢዘየኩም”ን እንዲህ ተጫወተው፡፡

 ኢዘየኩም ኬፍ ኢነኩም (2)
አነ-ሌ ዘማን ማ ሹፍቱኩም፡፡ (2)
“ጤና ይስጥልኝ እንደምን ናችሁ (2)
ከሱዳን መጣን ልናያችሁ” (2)
አነ ሌ ዘማን ማሹፍቱኩም፡፡

 በአዳራሹ የታደመው ኢትዮጵያዊ ተመልካች በሰማው ነገር እየተገረመ ጭብጨባውን አጠናክሮ ቀጠለ፡፡ በዚያች ቀን ተመልካቹን ለማስገረም ብቻ የተላከ ይመስል የነበረው ሰይድ ኸሊፋም ሌላ ዜማ ማከል አስፈለገው፡፡ እና ለሱዳናዊያን እንግዳ የሆነውን “ትዝታን” በተሰባበረ አማርኛ ተጫወተው፡፡ ተመልካቹም በሳቅ ፍርስ እያለ አጨበጨበለት፡፡
-------
አዎን! ሰይድ ኸሊፋ በኢትዮጵያዊያን ልብ ከነገሱ የሱዳን የኪነ-ጥበብ ፈርጦች መካከል ቀዳሚው ነው፡፡ “ሱዳን” ሲባልም ከሁሉ በፊት ለኛ ትዝ የሚሉን “ኢዘየኩም” እና የሰይድ ኸሊፋ የተሰባበረ አማርኛ ናቸው፡፡ ይህ አንጋፋ የጥበብ ፈርጥ በእጅጉ ከሚታወቅበት የምስራቅ አፍሪቃ ክልል ባሻገር በመካከለኛው ምስራቅ፣ በአውሮጳ እና በአሜሪካ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ለመቀዳጀት በቅቷል፡፡ ለዚህ ይበልጥ የረዳው ደግሞ “ኢዘየኩም”ን በሄደበት ሀገር ቋንቋ ሁሉ ለመዝፈን የሚሞክር መሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም እኛ “ጤና ይስጥልን፣ እንደምን ናችሁ” እያልን የምንዘምረው “ኢዘየኩም” በሀውሳ፣ በሰዋሂሊ፣ በእንግሊዝኛ፣ በጀርመንኛና በፈረንሳይኛ ቋንቋዎችም አቻ ትርጉሞች አሉት፡፡ ይህም ሰይድ ኸሊፋ ሙዚቃን ከመጫወት አልፎ የሌሎችን ቋንቋና ባህል ለማጥናት የነበረውን ጉጉት በአጭሩ ያስረዳል፡፡
------
ሰይድ ኸሊፋ እንደ ብሄራዊ መዝሙር ከሚዘፍነው “ኢዘየኩም” ባሻገር በመቶ የሚቆጠሩ ሌሎች ዜማዎች አሉት፡፡ በሀገራችን አድማጮች ዘንድ ተወዳጅ ከሆኑት ዜማዎቹ መካከል “ኢንቲ ያ ጀሚላ”፣ “ሐቢበተል በለዲያ”፣ “ወሽወሾ ሀምሳ”፣ “ጃሩ አነ ጃሩ”፣ ዚድኒ ሚን ደለክ ሺወይያ”፣ “አል-ዋሒድ ኸሊ ዓለል ዋሒድ”፣ “ተዓሊ ተዓሊ”፣ “ሳምባ”፣ “መሽጉል ባለኪ”፣ “ሲደ-ንናስ ሐደር”፣ “አህላ ገራም”፣ “ያ ዒቅደል ሉሊ” የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ሰይድ ኸሊፋን በመላው ዓለም ተወዳጅ ያደረጉት ግን አራት  ዜማዎች ናቸው፡፡ እነርሱም  “ዘኑባ”፣ “ኢዘየኩም”፣ “አወድዳዕኩም” እና “አል-ማምቦ ሱዳኒ” የተሰኙት ናቸው፡፡

“ዘኑባ” የፍቅር ዜማ ነው፡፡ በዘፈኑ ውስጥ “ዘኑባ” የተባለላት ወጣት የኑቢያ ተወላጅ ናት፡፡ ሰይድ ለዚያች ወጣት “ሐረቀት ገልቢ መሐባታ” (ፍቅርሽ ልቤን አቃጠለው) እያለ ልመናውን ይደረድርላታል፡፡ “ዘኑባ ያ ቢንተል ኒል”ም ይላታል፡፡ “አንቺ ኒል (አባይ) ያበቀላት የኑቢያ ወጣት” ማለት ነው፡፡ ሰይድ ኸሊፋ ይህንን ዘፈን ወደ ኢትዮጵያ በመጣበት ወቅት “ዘነበች” እያለ በአማርኛ አዚሞታል፡፡ እርሱ “ቢንት ኢትዮጵያ፣ ዘነበች” እያለ ሲዘፍን ዘነበች ታደሰ (ጭራ ቀረሽ) ደግሞ ከርሱ ጎን ቆማ ትደንስ ነበር፡፡ 

   “ኢዘየኩም” የሰላምታና የናፍቆት መጠየቂያ ነው-ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት፡፡ ታዲያ ሰይድ በዚህ ዘፈን የተጠቀመው “ኢዘየኩም” የተሰኘው ቃል ሰላምታን ከመግለጽ ባሻገር ትልቅ ታሪካዊ ፍካሬን ተሸክሟል፡፡ “ኢዘይ” (እንዴት) የሚለው ቃል መሰረቱ ዐረብኛ አይደለም፡፡ ይህ ቃል ከጥንታዊው የኑቢያ ቋንቋ ተወርሶ ከዐረብኛ ጋር የተደባለቀ ነው፡፡ በግብፅና በሰሜን ሱዳን ጠረፍ በሚነገረው የዐረብኛ ዘዬ ውስጥ ጉልህ ሆኖ ይሰማል፡፡ በኻርቱም አካባቢ በሚነገረው የዐረብኛ ዘዬ ውስጥ ግን የለም፡፡ የሰይድ ኸሊፋን ዜማዎች ያጠኑ ተመራማሪዎች እንደሚናገሩት ሰይድ ይህንን ቃል በዘፈኑ ውስጥ የተጠቀመው የናፍቆት ሰላምታን ከማስተላለፍ በተጨማሪ የጥንቷ ኑቢያ በታሪክ ውስጥ የነበራትን ሚና ለማስታወስ በሚል ነው፡፡

“አወድዳዕኩም” የተሰኘው ዘፈኑ ደግሞ የ“ኢዘየኩም” ተቃራኒ ነው፡፡ ሰይድ ኸሊፋ በዚህ ዘፈን “ልለያችሁ ነው፤ ልሰናበታችሁ ነው” ነው የሚለው፡፡ ብዙ ጊዜ ሙዚቃውን ለታዳሚዎቹ ሲያቀርብ ሁለቱን ዘፈኖች መክፈቻና መዝጊያ ያደርጋቸዋል (ማለትም በ“ኢዘየኩም” የተጀመረውን ዝግጅት በ“አወድዳዕኩም” ይዘጋዋል)፡፡ ሁለቱን ዘፈኖች የሚዘፍንበት ስሜትም እንደ ዘፈኖቹ ይለያያል፡፡ “ኢዘየኩም”ን በፍልቅልቅ ፈገግታና በደስታ ተሞልቶ ነው የሚጫወተው፡፡ “አወድዳዕኩም”ን ግን ጭንቅ ጥብብ እያለ ልብን በሚነካ ስልት ያስኬደዋል፡፡ አንዳንዴም አልቅሶ ታዳሚውን ያስለቅሳል፡፡ ታዲያ ሰውዬው ሰይድ ኸሊፋ ነውና ሁለቱም ያምሩለታል፡፡ በፈገግታ ሲፍለቅለቅም ሆነ ጉንጮቹን በእምባ ሲያርስ ታዳሚውን የመነቅነቅ ሀይሉ ከፍተኛ ነው፡፡
--------
ከሰይድ ኸሊፋ ታላላቅ ዘፈኖች መካከል ጉልህ ሆኖ የሚጠቀሰው “አል-ማምቦ ሱዳኒ” ነው፡፡ ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት “አል-ማምቦ ሱዳኒ” በመድረክ ላይ የተጫወተው የመጀመሪያ ዜማው ነው፡፡ ሰይድ ኸሊፋ “አል-ማምቦ ሱዳኒን”ን በወጣትነቱ ሲጫወተው “እኛም ሀገር እንዲህ ዐይነት ተአምር አለና ተመልከቱ” ለማለት ያህል ነው፡፡ ከጊዜ በኋላ የዘፈኑ ግጥም በሙዚቃ ኤክስፐርቶች ሲጠና ግን በርካታ ተአምራትን አጭቆ የያዘ እንደሆነ ተደረሰበት፡፡  እስቲ ሙሉ ግጥሙን ልጻፍላችሁ፡፡
----- 
(አዝማቹ)
አል-ማምቦ ሱዳኒ
አልማምቦ ፊኪያኒ
ፊዑዲ ፊከማኒ
ወአጅመል አልሓኒ
ማምቡ….!
----
(1ኛ ተከታይ ግጥም)
ያ ሐቢበ መሕላኪ
አል-ማምቦ ፊጊናኪ
አል-ለሕኑ ኸልላኪ
ቲትማየሊ ፊኹጣኪ
ዐላ-አንጋሚል ማምቡ
----
አልማምቦ ሱዳኒ
---
(2ኛ ተከታይ ግጥም)
ያ ሐቢበ የዑዲክ
ያ ወርደ ፊኹዱዲክ
አድኔቲ መርዩዲክ
ሚን ቡክረ መውዑዲክ
የርጉስ በሃኪ ጀንቡ
-----
ዐላ አንጋሚል ማምቦ
-----
(3ኛ ተከታይ ግጥም)
ረንነት ኹጣኪ አል-ሓን
ያ ወርደ ፊ ቡስታን
አነ ቀልቢ ባት ሐይራን
ማካን ያሬት ማካን
ማዱግና ናር ሑብቡ
------
የውም ረግሰተል ማምቦ
------
(4ኛ ተከታይ ግጥም)
በረደን-ነሲም ያሌል
ያሡረይያ ናዲ ሱሄል
ኩል ኺል መዓህ ኸሊል
አነ ወሕዲ ጀመል-ሽሼል
ዐሰረል-ሀዋ ገልቡ
------
የውም ረግሰተል ማምቦ
-----

“ማምቦ” የላቲን አሜሪካ የጭፈራ ዐይነት የሚጠራበት ስም ነው እንጂ ኦሪጅናሌ የሱዳን ቃል አይደለም፡፡ ሰይድ ኸሊፋም ግጥሙን ሲጀምር በፈረንጆቹ ዘይቤ “ማምቦ” ብሎታል፡፡ በማሳረጊያው ላይ ግን ቃሉን ወደ ዐረብኛ በመጎተት “ማምቡ” አድርጎታል፡፡ ይህንንም ያደረገው አዝማቹን ከተከታዮቹ ግጥሞች ጋር ለማስማማት እንዲያመቸው ነው፡፡

  ተከታዮቹ ግጥሞች ባለ አምስት መስመር ናቸው (ስድስተኛው መስመር ዘፈኑን ለማሳመር የሚደጋገም መነባንብ ነው እንጂ የግጥሞቹ አካል አይደለም፤ ለዚህም ነው ለብቻው የጻፍኩት)፡፡ ከአምስቱ መስመሮች መካከል አራቱ በተመሳሳይ ፊደል ነው የሚያሳርጉት፡፡ በአምስተኛ መስመር ላይ ያሉት ሁሉም ስንኞች ግን “ቡ” በተሰኘው ፊደል ነው የሚያበቁት፡፡ ይህም ከአዝማቹ ጋር በሚጣጣም መልክ መሆኑ ነው (አዝማቹም ባለአምስት መስመር መሆኑን ልብ በሉ)፡፡

እንዲህ ዓይነት ግጥም በዘመናዊው ዐረብኛ ውስጥ የለም፡፡ በጥንታዊው ዐረብኛ (Classical Arabic) ግን የግጥሙን ውበት መጠበቅ ግዴታ ነው፡፡ ገጣሚዎች ስለስንኙ መልዕክት ብቻ ሳይሆን የግጥሙን ውበት በሚያበለጽጉ ቴክኒካዊ ጉዳዮችም ላይ ይጨነቃሉ፡፡ የያንዳንዱ ስንኝ ቃላትና ፊደላት ብዛት፣ ስንኙ ቤት የሚመታበት ሁኔታ፣ ከተከታይ ስንኞች ጋር ያለው ትስስር ሁሉ ትኩረት ይሰጠዋል፡፡ ሰይድ ኸሊፋም በአል-ማምቦ ሱዳኒ ውስጥ ያንጸባረቀው ይህንኑ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ቋንቋው የሱዳን ዐረብኛ ዘዬ ነው፤ ግጥሙ ግን በጥንታዊው ዐረብኛ ስልት ነው የተጻፈው)፡፡
--------
ሰይድ አሕመድ አል-ኸሊፋ በ1923 ከኻርቱም አጠገብ ከነበረችው “ሙንቀተ-ዲባባ” በተሰኘች መንደር ተወለደ፡፡ የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በኻርቱም ካጠናቀቀ በኋላ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ካይሮ ተላከ፡፡ በክፍል አንድ እንደጻፍኩት ሙዚቃን በካይሮ አሐዱ ብሎ ከጀመረ በኋላ ወደ ሀገሩ በመመለስ እስከ ህይወቱ ፍጻሜ ድረስ ተጓዘበት፡፡

  ሰይድ ኸሊፋ ከሌሎች ሱዳናዊ ድምጻዊያን የሚለይበት አንድ ገጽታ አለው፡፡ ይህም ከማንም ጋር ሳይዳበል በራሱ ጥረት ብቻ ከከፍተኛ ደረጃ ላይ ለመድረስ የበቃ የመጀመሪያው ድምጻዊ መሆኑ ነው፡፡ የጥንቱ የሱዳን ዘፋኞች ሙዚቃን የሚጀምሩት በሌላ ታዋቂ ዘፋኝ ጥላ ስር በመሆን ነው፡፡ ለጥቂት ጊዜ ከዋናው ዘፋኝ ጋር እየተጫወቱ ይቆዩና በህዝቡ ውስጥ መታወቅ ሲጀምሩ የራሳቸውን ነጻ ኦርኬስትራ ይመሰርታሉ፡፡ ሰይድ ኸሊፋ ግን “አል-ማምቦ” ሱዳኒን በካይሮ ከዘፈነበት ጊዜ ጀምሮ ራሱን ችሎ ለብቻው ነው የተጓዘው፡፡ በዚህም ከርሱ ኋላ ለመጡት በርካታ ድምጻዊያን አርአያ ሊሆን በቅቷል፡፡ ሰይድ ኸሊፋ ለዘፈኖቹ ዜማ የሚሰራው ለራሱ ነው፡፡ ብዙዎቹን ግጥሞች ግን ከሌሎች አርቲስቶች ነው የወሰደው፡፡ ከሰይድ ኸሊፋ የዘፈን ግጥሞች መካከል ብዙዎቹን የጻፉት ኢድሪስ ጀማል እና ሙሐመድ ዓሊ የተባሉ ገጣሚያን ናቸው፡፡

ሰይድ ኸሊፋ ሁለት ጊዜ አግብቷል፡፡ የመጀመሪያ ጋብቻው በፍቺ የተቋጨ ሲሆን በሁለተኛ ጋብቻው ከተጣመራት ሴት ጋር እስከ ህይወቱ መጨረሻ ድረስ ኖሯል፡፡ በዚህ ጋብቻም አራት ልጆችን አፍርቷል፡፡ ይሁንና ከልጆቹ መካከል አንዳቸውም በርሱ መንገድ አልተጓዙም፡፡
------
ሰይድ ኸሊፋ በህይወቱ መጨረሻ ላይ በልብ ህመም መሰቃየት ጀመረ፡፡ በሀገሩ ውስጥ ባሉ ክሊኒኮችና ሆስፒታሎች ለመታከም ሞከረ፡፡ ነገር ግን ከህመሙ ሊፈወስ አልቻለም፡፡ ወደ ዩናይትድ ስቴት እየተመላለሰ ቢታከምም ምንም ለውጥ ሊያገኝ አልቻለም፡፡ በሰኔ ወር 1993 (እንደኛ አቆጣጠር) የልብ ህመሙ ከጫፍ ላይ አደረሰው፡፡ የሱዳን ሪፐብሊክ መንግሥትም ነፍሱን ለማትረፍ ወደ ዮርዳኖስ ዋና ከተማ “አማን” ሰደደው፡፡ የዮርዳኖሱ አል-ኻሊዲ ሆስፒታል የህክምና ባለሙያዎችም በድንገት እጃቸው ላይ የወደቀውን ታላቅ የጥበብ ገበሬ ህይወት ለማትረፍ ተጣጣሩ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ነገር በምድራዊ ሀይል የማይመለስ ሆነ፡፡ ያ ዝነኛ አርቲስት ሰኔ 26/1993 የመጨረሻ እስትንፋሱን ተነፈሰ፡፡ ሩሑ ለህክምና በሄደበት ሀገር ከስጋው ተለየች፡፡

በቀጣዩ ቀን አስከሬኑ ወደ ኻርቱም ሲመለስ የሱዳን ፕሬዚዳንት ዑመር ሐሰን አል-በሺርና ከፍተኛ ባለስልጣናት የጀግና አቀባበል አደረጉለት፡፡ ቀብሩም በመቶ ሺህ የሚቆጠር ህዝብ በተገኘበት ተፈጸመ፡፡
--------
ግንቦት 16/2006
ሸገር-አዲስ አበባ
-------
የመረጃ ምንጮች
1.      ሱዳን ትሪቢዩን ዌብሳይት
2.     ዐረብ ኦን ላይን ዌብ ሳይት
3.     የሱዳን ቴሌቪዥን ጣቢያ ያሰራጫቸው ፕሮግራሞች
4.     በሬድዮ ኦምዱርማን የተሰራጩ ፕሮግራሞች
5.     ሰይድ ኸሊፋ ያሳተማቸው አልበሞች
6.     ልዩ ልዩ የቃል መረጃዎች
  


Wednesday, May 14, 2014

“አንድ ሺህ አንድ ሌሊት”


 አፈንዲ ሙተቂ
------
  ከዐረቡ ዓለም የተገኘው ታላቅ የስነ-ጽሑፍ ቅርስ “አልፍ ለይላ ወለይላ” በመባል ይታወቃል፡፡ በቀጥታ ሲተረጎም “አንድ ሺህ አንድ ሌሊት” (1001 nights) እንደማለት ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ብዙዎች ያለመሰልቸት እየደጋገሙ ካነበቧቸው ድርሰቶች መካከል ይመደባል፡፡ በብዙ ቋንቋዎች ከተተረጎሙ ምርጥ መጻሕፍት መካከልም አንዱ ነው፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ካሉት የጀብድና የትንግርት ተረቶች መካከል በርካቶቹ የሌሎች ህዝብ ስነ-ቃል አካል እስከ መሆን ደርሰዋል፡፡

የ“አልፍ ለይላ ወለይላ” ታሪኮች በጥንት ዘመን በአፍ ሲነገሩ ነው የኖሩት፡፡ ከጊዜ በኋላ ግን ዐረቦች ታሪኮቹን በመጽሐፍ ሰብስበዋል፡፡ በመሆኑም የምዕራቡ ዓለም መጽሐፉን “Arabian Nights” በማለት ይጠራዋል፡፡ ይህ ማለት ግን ታሪኮቹ በሙሉ የዐረቦች ናቸው ማለት አይደለም፡፡ መጽሐፉን የመረመሩ ሊቃውንት የአልፍ ለይላ ወለይላ ተረቶች ከቻይና እስከ ግብጽ ድረስ ካሉት ህዝቦች የተገኙ መሆናቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ከጥንታዊ የግሪክ ተረቶች ጋር የሚመሳሰሉ ታሪኮችም አሉበት፡፡

  ===የመጽሐፉ መነሻ===

“አልፍ ለይላ ወለይላ”ን ለመጀመሪያ ጊዜ በመጽሐፍ ያጠናቀረው ሰው በውል አይታወቅም፡፡ በታሪኮቹ አጻጻፍ ላይ የሚታየውን ልዩነት ያጠኑ ምሁራን መጽሐፉ በአንድ ደራሲ የተጻፈ ሊሆን እንደማይችል ይናገራሉ፡፡ በተጨማሪም ታሪኮቹ በተለያዩ የዐረብኛ ዘዬዎች የተጻፉ በመሆናቸው መጽሐፉ በአንድ ሀገር ብቻ የተጠናቀረ እንዳልሆነ ይወሳል፡፡ በብዙዎች ግምት መሰረት የመጽሐፉ ጥንስስ የተዋቀረው በኢራቅ ዋና ከተማ ባግዳድ ውስጥ ነው፡፡ መጽሐፉ የመጨረሻ ቅርጹን ያገኘው ደግሞ በግብጽ ነው፡፡

  ለመጀመሪያ ጊዜ ስለ ታሪኮቹ የተናገረው አል-መስዑዲ የሚባል ታዋቂ የዐረብ ታሪክ ጸሐፊ ነው፡፡ መስዑዲ በ947 ባጠናቀረው ኢንሳይክሎፒዲያ መሰል መጽሐፉ አራናዊያን “ሐዛር አፍሳና” (Hazaar Afsaana) በሚል ስያሜ የሚጠራ ተረቶችን የመጨዋወት ወግ እንደነበራቸው ተናግሯል፡፡ ይህም ዘወትር ማታ ማታ አንድ ሺህ ተረቶችን እየተረኩ የሚጨዋወቱበት ልማድ ነው (“ሀዛር አፍሳ” በፋርሲ ቋንቋ “አንድ ሺህ ተረቶች” ማለት ነው)፡፡ በመስዑዲ ዘገባ መሰረት ኢራናዊያኑ የሚጨዋወቷቸው ተረቶች ከኢራን፣ ዐረቢያ፣ ህንድና ግሪክ የተገኙ ናቸው፡፡ እንግዲህ የዐረቦቹ  “አልፍ ለይላ ወለይላ” የተፈጠረው የኢራናዊያኑ “ሃዛር አፍሳና”ን እንደ አርአያ በማድረግ ነው ተብሎ ይገመታል፡፡

===“ሻህረዛድ” እና “ሻህሪያር”===

የ“አልፍ ለይላ ወለይላ” ታሪኮች የተደረደሩት እንደ ሌሎች የተረት መጻሕፍት አይደለም፡፡ መጽሐፉ በቀዳሚነት የሁለት ገጸ-ባህሪያት ታሪክ ነው፡፡ ከነዚህ ገጸ-ባህሪያት መካከል አንዱ ሻህሪያር ይባላል፡፡ ሻህሪያር የአንዲት ሀገር ሱልጣን (ንጉሥ) ነበር፡፡ ይህ ሰው መጀመሪያ ካገባት ሚስቱ ጋር ሲኖር ሴቲቱ ከአንድ የርሱ ባለስልጣን ጋር ስትባልግ ይይዛታል፡፡ በዚህም የተነሳ ልቡ በሐዘን ይሰበራል፡ ሚስቱንም ያለ ርህራሄ ይገድላታል፡፡

   ሻህሪያር ሚስቱን በመግደል ብቻ ንዴቱ አልበረደለትም፡፡ “ሴቶች ታማኝ ፍጡራን አይደሉም፤ ከምድር ላይ መጥፋት አለባቸው” የሚል እምነት በልቡ አሳደረ፡፡ በመሆኑም በየቀኑ አዲስ ሚስት እያገባ አብሯት ካደረ በኋላ በማግስቱ ይገድላት ጀመር፡፡ በዚህ የጭካኔ መንገድ ብዙ ኮረዳዎች አለቁ፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አዲስ ሚስት የሚመለምልለት ወዚር (ሚኒስትር) ለርሱ የምትሆን ልጃገረድ ቢያጣ ከቤቱ ቁጭ ብሎ መተከዝ ጀመረ፡፡ “ሻህረዛድ” የተባለችው ልጁ ያዘነበትን ምክንያት እንዲነግራት ስትጠይቀው የንጉሡን የጭካኔ አድራጎት አንድ በአንድ አጫወታት፡፡ በታሪኩ ልቧ የተነካው ሻህረዛድ የሌሎች ሴቶችን ህይወት ለመታደግ ራሷን ቤዛ ለማድረግ ወሰነች፡፡ በመሆኑም አባቷ ለንግሡ እንዲድራት ጠየቀችው፡፡ አባቷ ሀሳቧን ሊያስቀይራት ቢሞክርም እርሷ ግን ውሳኔዋን እንደማትቀለብስ ነገረችው፡፡ “ንጉሡን አግብቼ ጀብዱ ስሰራ ታየኛለህ” በማለትም አግባባችው፡፡ አባቷም በልበ-ሙሉነቷ ተገርሞ ለንጉሡ ሊድራት ተስማማ፡፡
    -------
    ንጉሥ ሻህሪያር አዲሱን ሚስት (ሻህረዛድን) አገባት፡፡ የመጀመሪያውን ቀን አብሯት ካሳለፈ በኋላ መሸ፡፡ ሁለቱ ጥንዶች ሊተኙ አልጋ ላይ ወጡ፡፡ ሻህሪያር “እንግዲህ ካሳደርኳት በኋላ ሊነጋጋ ሲል እገድላታለሁ” እያለ ሲያስብ ሻህረዛድ አንድ ቆንጆ ተረት ታወራለት ጀመር፡፡ ይሁንና ተረቱን ሳትጨርሰው “የቀረውን ነገ ማታ አጫውትሃለሁ፤ አሁን እንተኛ” አለችው፡፡ ሻህሪያር የተረቱን መጨረሻ ለማወቅ ስለፈለገ እርሷን የመግደሉን ሀሳብ ለሚቀጥለው ሌሊት አስተላለፈ፡፡

  በቀጣዩ ሌሊት ሻህረዛድ የጀመረችውን ተረት ካጠናቀቀች በኋላ ሌላ ረጅም ተረት ጀመረችለት፡፡ ሆኖም ተረቱን ልብ በሚያንጠለጥበት ቦታ አቋረጠችው፡፡ ለሻህሪያርም “አሁን ስለደከመኝ ልተኛ፤ የቀረውን በሚቀጥለው ሌሊት እጨርስልሃለሁ” አለችው፡፡ ሻህሪያርም የልቡን በልቡ አድርጉ ሃሳቧን ተቀበላት፡፡ “ነገ ከጨረሰችልኝ በኋላ እገድላታለሁ” በማለት ግድያውን አስተላለፈ፡፡ በሚቀጥለው ሌሊትም ሻህረዛድ የጀመረችውን ታሪክ ከጨረሰችለት በኋላ ሌላ አዲስ ታሪክ ታወጋለት ጀመር፡፡ ሆኖም ተረቱን ሳታጠናቅቀው “ነገ እጨርስልሃለው” አለችው፡፡ ሸህሪያርም የግድያ ውጥኑን ለቀጣዩ ሌሊት አስተላለፈ፡፡

    ሻህረዛድ “ቀጣዩን ነገ እጨርስልሃለው” ስትለው ሻህሪያርም “እሺ” እያለ የግድያ እቅዱን ሲያስተላልፍ አንድ ሺህ አንድ ሌሊቶች አለፉ፡፡ ሻህረዛድ አንድ ሺህ አንደኛውን ተረት ስታወራለት ከቆየች በኋላ “እስቲ እንደሚገድለኝ አያለሁ” በማለት ለነገ ሳትል መጨረሻውን ነገረችው፡፡ ይሁንና ሻህሪያር ድሮ ሲያደርግ እንደነበረው ሻህረዛድን አልገደላትም፡፡ ምክንያቱም እርሷ በየቀኑ ተረቱን ስታወጋለት የርሱም ልብ በየቀኑ እየተለወጠች በመሄድ ላይ ስለነበረች ነው፡፡ ልቡን የሞላው የጥላቻና የበቀል መንፈስ ቀስ በቀስ እየተጠረገ በፍቅርና ይቅር ባይነት ተተክቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ድሮ ሲፈጸም የነበረውን የጭካኔ አድራጎት ለሻህረዛድ ከተናዘዘላት በኋላ ከርሷ ጋር በፍቅር ለመኖር ወሰነ፡፡
-------
ከላይ የቀረበው የመጽሐፉ አስኳል ታሪክ (frame strory) ነው፡፡ በዚህ ታሪክ መሰረት በመጽሐፉ የቀረቡትን 1001 ተረቶች የምታጫውተን ሻህረዛድ ናት፡፡ በመሆኑም እኛ አንባቢያን እንደ ሻህሪያር ሆነን ነው ታሪኮቹን የምናነበው ማለት ነው፡፡ ታዲያ ሻህሪያር እና ሻህረዛድ በእውነታው ዓለም የነበሩ ሰዎች ስለመሆናቸው እስከ አሁን ድረስ ማረጋገጫ አልቀረበለትም፡፡ ሆኖም የዓለም ህዝብ “ሻህረዛድ” የምትባለው ትውፊታዊ ንግሥት ያወራቻቸውን ታሪኮች በደንብ ያውቃቸዋል፡፡

Tuesday, May 13, 2014

“ጄኔራል ፋንታ በላይ” እና “የግንቦት 8/1981 የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ”



ጸሓፊ፡- አፈንዲ ሙተቂ
---------
ይህንን ጽሑፍ ልክ የዛሬ ዓመት ገደማ ፖስት አድርጌው ነበር፡፡ ዛሬም ታሪካዊነቱ ጎልቶ ስለታየኝ ልደግመው ወሰንኩ፡፡ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው በተካሄደበት ግንቦት 8/2006 ቀን ሌላ ጽሑፍ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡
-------
በዚህ የሁለት ደቂቃ ቪዲዮ ላይ የሚታዩት ሜጀር ጄኔራል ፋንታ በላይ ናቸው። ጄኔራል ፋንታ ግንቦት 8/1981 ተሞክሮ የከሸፈውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ በማቀነባበር ከፍተኛ ሚና እንደተጫወቱ በሰፊው ተነግሯል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የወጡት የህትመት ውጤቶችም ይህንኑ አረጋግጠዋል ( ቪዲዮውን ለማየት ይህንን ሊንክ ይክፈቱ http://www.youtube.com/watch?v=GDjRkfq-toM )፡፡

ጄኔራል ፋንታ መፈንቅለ መንግሥቱን የጠነሰሱት በ1977 ዓ.ል. ክረምት ላይ በተካሄደው “ዘመቻ ባህረ ነጋሽ” ወቅት እንደሆነ በሰጡት የምርመራ ቃል አረጋግጠዋል። ዘመቻው ምዕራባዊውን የኤርትራ አውራጃዎች ከሻዕቢያ (EPLF) ነጻ የማውጣት ዓላማ ነበረው። በዘመቻው የኢትዮጵያ ጦር ድል ቢቀዳጅም የተከፈለው መስዋእትነት ከተጠበቀው በላይ ሆኖ ተገኘ። በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ወጣቶች (በተለይም በአንደኛው የብሔራዊ ውትድርና አገልግሎት ፕሮግራም የዘመቱ) አለቁ። የዚህ አሳዛኝ ትራጄዲ መንስኤ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም በሀገራቸው የጦር መኮንኖች የተወጠነውን የዘመቻ ስትራቴጂ በመግፋት ከሶቪየት ህብረት አማካሪዎቻቸው የተሰጣቸውን እቅድ መተግበራቸው ነው። በወቅቱ የኢትዮጵያ አየር ሀይል ዋና አዛዥ የነበሩት ጄኔራል ፋንታ በላይ የዘመቻ ባህረ ነጋሽን ውጤት ሲሰሙ “ይህ ሰውዬ ዘወትር እኛን እየገፋን የሀገራችንን ወጣቶች እንደ ማገዶ እንጨት የሚቆጥሩትን የሶቪየት አማካሪዎችን ሃሳብ የሚተገብረው ለምንድነው? በዚህ ዓይነትስ እስከ መቼ ልንዘልቅ ነው?” እያሉ ማሳላሰል ጀመሩ። ብዙ አውጥተው ካወረዱ በኋላ መፍትሄው ሰውዬውን ማስወገድ ብቻ እንደሆነ አመኑ። “ለዚህም ዓይነተኛው ዘዴ በከፍተኛ መኮንኖች የሚመራ መፈንቅለ መንግሥት ነው” ከሚል መደምደሚያ ላይ ደረሱ።

ጄኔራል ፋንታ ኩዴታውን በጸነሱበት ማግስት ሶስት ከፍተኛ መኮንኖችን በጉዳዩ ላይ በማወያየት ስምምነታቸውን አገኙ። እነርሱም ሜ/ጄኔራል መርዕድ ንጉሤ (የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም)፣ ሜ/ጄኔራል ደምሴ ቡልቶ (የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ዋና አዛዥ) እና ሜ/ጄኔራል አበራ አበበ (በሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የዘመቻ መምሪያ ሃላፊ) ነበሩ። አራቱ ጄኔራሎች እቅዳቸውን ለተወሰነ ጊዜ በሚስጢር ይዘውት ቆዩ። ይሁንና ሁለት አደገኛ ሀይሎች ሚስጢሩን አገኙት። እነርሱም KGB የተሰኘው የሶቪየት ህብረት የስለላ ተቋም እና የደህንነት ሚኒስትሩ ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደ ሥላሴ ናቸው።

ለኮሎኔል ተስፋዬ ሚስጢሩን የነገሩት ጄኔራሎቹ ራሳቸው ናቸው። ይህም በጄኔራል ፋንታ የምርመራ ቃል ተረጋግጧል። እነ ጄኔራል ፋንታ ለደህንነት ሚኒስትሩ የነገሩት ነገር ለሶቪየቱ KGB እንደሚደርሰው አያውቁትም ነበር ለማለት ይከብዳል። ይሁንና ጄኔራሎቹ በወቅቱ ነገሩን የረሱት ይመስላል (ወይንም ነገሩን አቃለው አይተውታል)። ታዲያ ምትሀተኛው KGB ሞስኮ ቁጭ ብሎ ያገኘውን ሚስጢር ሳያባክን ከከፍተኛ ትዕዛዝ ጋር አዲስ አበባ ለሚገኙት የሶቪየት አምባሳደር አስተላለፈው። አምባሳደሩም በከፍተኛ ፍጥነት እየበረሩ ወደ ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለ ማሪያም ቢሮ ደረሱና ሚስጢሩን ነገሯቸው።

ኮ/ል መንግሥቱ ከሶቪየቱ አምባሳደር የሰሙትን በመጠራጠር የደህንነት ሚኒስትሩን አስጠሩና ስለጉዳዩ የሚያውቁት ነገር እንዳለ ጠየቋቸው። ኮ/ል ተስፋዬ ከመንጌ በሰሙት ነገር ተደናገጡ። ሙሉ ሰውነታቸው ተርበተበተ። ኮ/ል መንግሥቱ ዛሬ ላይ ቆመው እንደሚያስታውሱት “ኮ/ል ተስፋዬ መናገር አቅቷቸው ቡ..ቡ…ቡ..” አሉ።  ኮሎኔሉ ከመንጌ ጥያቄ ለማምለጥ ያህል “ይህንን ነገር አልሰማሁትም፤ ከዛሬ ጀምሮ በቅርበት እከታተለውና የምደርስበትን ውጤት እነግርዎታለሁ” አሉ። መንጌም በነገሩ ተስማምተው ተለያዩ። እስከዚያ ጊዜ ድረስ በመፈንቅለ መንግሥቱ ደጋፊነት የሚታወቁት ኮሎኔል ተስፋዬ በመንጌ ፍጥጫ (እና ምናልባትም በኬጂቢ ፍራቻ) ወደ ተቃዋሚነት ተለወጡ። ጄኔራሎቹ በስልክ የሚነጋገሩትን እየጠለፉ ማዳመጥና በየጦር ክፍላቸው የሚያደርጉትን ሁሉ በአይነ ቁራኛ መከታተል ጀመሩ። መንጌም ኩዴታው ጎላ ብሎ ባይታያቸውም እንኳ “እንዲያው ለምናልባቱ” በሚል ጄኔራል ፋንታ በላይን ከአየር ሀይል አዛዥነታቸው አንስተው “የኢንዱስትሪ ሚኒስትር” አድርገው ሾሟቸው። 
*****
ማክሰኞ ግንቦት 8/1981 የቁርጥ ቀን ሆነ። ጄኔራሎቹ በመጋረጃ ጀርባ ለአራት ዓመታት ሲያንከባልሉት የነበረውን የመፈንቅለ መንግሥት ሀሳብ በዚህ ቀን ወደ ድርጊት ሊቀይሩት ተነሱ። በእለቱ ወደ ጀርመን ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ (ምስራቅ ጀርመን) የሚጓዙትን ኮ/ል መንግሥቱ ሀይለማሪያምን ከሸኙ በኋላ እኩለ ቀን ላይ በሀገር መከላከያ ሚኒስቴር ተገናኙ። በወቅቱ በአዲስ አበባ ይገኙ የነበሩትን ዋና ዋና የጦር መኮንኖች ሰበሰቡና ስለመፈንቅለ መንግሥቱ ነገሯቸው።

    ከነዚያ ጄኔራሎች በስተቀር በየትኛውም የስልጣን እርከን ላይ የነበረ የደርግ ሰው ስለስብሰባው ያወቀው ነገር አልነበረም። ይሁንና ከጥቂት ጊዜ ወዲህ የጄኔራሎቹን ጉዳይ ስራዬ ብሎ መከታተል የጀመረው  የደህንነት ሚኒስትሩ ስብሰባው “የመፈንቅለ መንግሥት አድማ” እንደሆነ ወዲያውኑ ነበር ያወቀው። ለዚህም የረዱት ሶስት ነገሮች ናቸው። አንደኛ ጄኔራል መርእድ ንጉሤ (ኤታማዦር ሹሙ) በጠዋቱ የፕሬዚዳንት መንግሥቱ አሸኛኘት ፕሮግራም ላይ መገኘት ሲኖርባቸው አልተገኙም። ሁለተኛ የመከላከያ ሚኒስትሩ ሜጀር ጄኔራል ሀይለ ጊዮርጊስ ሀብተ ማሪያም በስብሰባው ቦታ አልነበሩም። በመሆኑም መከላከያ ሚኒስትሩ ያልተሳተፉበት ስብሰባ የርሳቸው እውቅና እንዳልነበረው ለደህንነት ሚ/ሩ ታይቶታል። ሶስተኛ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር የነበረው ጄኔራል ፋንታ በላይ በስብሰባው ላይ ተገኝቷል። በወቅቱ ሲቪል የነበረው ጄኔራል ፋንታ በዚያ ቦታ መገኘቱ ለደህንነት ሚኒስትሩ አንድ ፍንጭ ሰጥቷል። 
*****
የደህንነት ሚኒስትሩ እነዚህን ነገሮች ካገናዘበ በኋላ በቀጥታ ወደ ብሔራዊ ቤተ መንግሥት በረረና የደረሰበትን ሁሉ የፕሬዚዳንቱ ልዩ ረዳት ለነበረው ሻምበል መንግሥቱ ገመቹ ነገረው። ሁለቱ ሰዎች በነገሩ ላይ ለጥቂት ደቂቃዎች ከተማከሩ በኋላ የመከላከያ ሚኒስትሩን አስጠርቶ መጠየቅ እንደሚበጅ ከስምምነት ላይ ደረሱ። በዚሁ መሰረት ሚኒስትሩ ተጠርተው ሲጠየቁ  ስለስብሰባው የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናገሩ። ሁለቱ ሰዎችም (ሻምበል መንግሥቱና ኮ/ል ተስፋዬ) እርምጃ ከመውሰዳቸው በፊት ሚኒስትሩ ወደ መከላከያ ሄደው ተሰብሳቢዎቹን ቢያነጋግሩ የተሻለ እንደሚሆን ሀሳብ አቀረቡ። ሚኒስትሩም ከአንዴም ሁለቴ መኪናቸውን ወደ መከላከያ ሚኒስቴር እየነዱ ተሰብሳቢዎቹን ለማነጋገር ሞከሩ። ይሁንና በሁለቱም ጊዜያት ከተሰብሳቢዎቹ ዘንድ ለመድረስ አልቻሉም። ይባስ ብሎም የመፈንቅለ መንግሥቱ የዘመቻ መኮንን ተብሎ በተመደበው ጄኔራል አበራ አበበ ተገደሉ።

 የጄኔራል ሀይለ ጊዮርጊስ (መከላከያ ሚኒስትሩ) መገደል መፈንቅለ መንግሥቱ ጥርጣሬ ብቻ እንዳልሆነ የሚያረጋግጥ ድርጊት ሆነ። በአንጻሩም መፈንቅለ መንግሥቱን ለውድቀት ያበቃው ይኸው ድርጊት ሆኖ ተገኘ። ከዚህ ክስተት በኋላ ጄኔራል አበራ ከቢሮ ውስጥ ለተሰበሰቡት ጄኔራሎች አድራሻውን ሳያሳውቅ ከግቢው ወጥቶ ተሰወረ። ቤተ መንግሥቱን የሚጠብቀው የልዩ ጥበቃ ብርጌድም (በተለምዶ አጠራር “ቅልብ ጦር”) ሳይታሰብ የመከላከያን ግቢ በታንክና በብረት ለበስ ከበበው። ከአስመራ ጄነራሎቹን ለመርዳት የተላከው የአየር ወለድ ጦርም መሪው ጄኔራል ቁምላቸው ደጀኔ ጥርት ያለ አመራር ስላልሰጡት በነመንግሥቱ ገመቹና ተስፋዬ ወ/ሥላሴ ተጠለፈ። ይሄኔ በመከላከያ ግቢ “ነፍስ ግቢ ነፍስ ውጪ” ሆነ። ለጥበቃቸው አንድ ሻምበል ተጠባባቂ ጦር እንኳ ያላዘጋጁት ጄኔራሎች ተዋከቡ።  እዚያው ቡድን አበጅተው መጣላት ጀመሩ። “የህጻን እቅድ አውጥታችሁ እንድናንቦጫርቅ አደረጋችሁን” ተባባሉ።

   የአድማው መሪ ሆነው የዋሉት ጀኔራል መርዕድ ንጉሤ ግን ተስፋ ሳይቆርጡ እስከ ምሽት ድረስ ዕድላቸውን ሞከሩ። በተለይ ደብረ ዘይት ላይ የከተመው አየር ሀይል ጄቶቹን አንቀሳቅሶ በመከላከያ ሚ/ር ዙሪያ የተኮለኮሉትን ታንኮች እንዲደበድብላቸው ብዙ ወተወቱ። ሆኖም ምንም ምላሽ አላገኙም።

  ከምሽቱ ሁለት ሰዓት አካባቢ ሁሉም ነገር ያበቃለት መሰለ። ለግማሽ ቀን ያህል መከላከያን ከበው የዋሉት የቅልብ ጦር ኮማንዶዎች ወደ ግቢው መግባት ጀመሩ። በዋናው ህንጻ ላይ ወዳለው የሚኒስትሩ ቢሮ ሲደርሱ አስራ ሁለት ጄኔራሎች ተቀምጠው በስጋት ዓይናቸውን ሲያቁለጨልጩ አገኟቸው። ሁሉንም አውጥተው ለሻምበል መንግሥቱ ገመቹ አስረከቧቸው።

  ሻምበል መንግሥቱ የተያዙትን ሰዎች ትክ ብሎ ሲያይ አራት መኮንኖች ከጄኔራሎቹ ቁጥር መጉደላቸውን አረጋገጠ። ለኮማንዶዎቹም “እያንዳንዱን ክፍል እየከፈታችሁ ፈትሹ” የሚል ትዕዛዝ ሰጣቸው። ኮማንዶዎቹም በተባሉት መሰረት ክፍሎችን መፈተሽ ሲጀምሩ ከዋናው ህንጻ ምዕራባዊ ጥግ አካባቢ “ድው” የሚል የተኩስ ድምጽ ሰሙ። ድምጹ ወደተሰማበት አቅጣጫ በዝግታ እያማተሩ ሲጓዙም “ድው” የሚል ሌላ ድምጽ ተሰማ። በዚህን ጊዜ ወታደሮቹ ሁለት ረድፍ ሰርተው በጥንቃቄ እያዘገሙ ከቦታው ደረሱ። ሁለት ከፍተኛ ጄኔራሎች ሽጉጣቸውን ጠጥተው ተገኙ። ሜጀር ጄኔራል መርዕድ ንጉሤ- የኢህዲሪ የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም፣ እና ሜጀር ጄኔራል አምሐ ደስታ- የኢህዲሪ አየር ሀይል ዋና አዛዥ….
*****
   ግንቦት 8/1981። ከምሽቱ 5፡00 ሰዓት። የኢትዮጵያ ድምጽ ብሔራዊ አገልግሎት (የአሁኑ የኢትዮጵያ ሬዲዮ) እንዲህ የሚል ዜና አስተላለፈ።
“በጥቂት ከሀዲ ጄኔራሎች የተካሄደው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ሙሉ በሙሉ መክሸፉን የኢህዲሪ የመንግሥት ምክር ቤት ቃል አቀባይ አስታወቁ”
*****
  በዚያች ምሽት ሁለት ጄኔራል መኮንኖች የገቡበት ሳይታወቅ ጠፍተዋል። ከአስር ቀናት በኋላ ግን አንደኛው ጄኔራል የነበረበት ቦታ በውስጠ አዋቂ ተደረሰበትና አዳኝ ጦር ተላከበት። ጄኔራሉ በጦር እንደተከበበ ሲያውቅ ጣሪያ ለጣሪያ እየሮጠ ለማምለጥ ሞከረ። ግን አልቻለም። ሰፈሩን በድርብርብ ክብ ያጠረው አዳኝ ጦር የጀኔራሉን የማምለጥ እድል አጨናጎለው። ጄኔራሉም ልክ እንደ ጓደኞቹ ወደቀ። ሜጀር ጄኔራል አበራ አበበ- የሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የዘመቻ መምሪያ ሃላፊ።

   ይህ ከመሆኑ ከአንድ ሳምንት በፊት ሁለተኛው ጄኔራል በራሳቸው ፍላጎት ከተደበቁበት ቦታ ወጥተው ለመከላከያ ሚኒስቴር የጥበቃ ዘቦች እጃቸውን ሰጥተዋል። ጄኔራል ፋንታ በላይ- የቀድሞው የኢህዲሪ አየር ሀይል ዋና አዛዥ፣ በወቅቱ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር……

 ጄኔራል ፋንታ ለሶስት ቀናት ያህል በኮንቴነር ውስጥ ተደብቀው መቆየታቸውን ገልጸዋል። ጄኔራሉ ለሶስት ቀናት ያለ ምግብና ውሃ መቆየታቸው ያስደነቀው የአዲስ አበባ ህዝብ በወቅቱ እንዲህ የሚል ስንኝ ቋጥሮ ነበር።
     “ፔፕሲ ኮካ ኮላው ከከተማው ጠፍቶ
       ፋንታ ተገኘ አሉ በኮንቴነር ሞልቶ”

በመፈንቅለ መንግሥቱ ጦስ ከተያዙት ጄኔራሎች መካከል ነገሩን ከውጥኑ ጀምሮ የሚያውቁት ጄኔራል ፋንታ በላይ ብቻ ነበሩ። ይሁንና ምርመራ ሲደረግባቸው አጠቃላይ ነገሮችን ከመናገር ውጪ ዝርዝር የሆኑ ጉዳዮችን ከማውጋት ተቆጥበዋል። ጄኔራል ፋንታ የተናገሩት አንድ ትልቅ ሚስጢር ቢኖር የደህንነት ሚኒስትሩ ከሃዲነት ነው። በማዕከላዊ ምርመራ ላነጋገሩዋቸው ኦፊሰሮች “ሚኒስትሩ ‘ከናንተ ጋር ነኝ’ ብሎን ነበር፤ እኛም አምነነው በእርምጃችን ቀጠልንበት። በኋላ ላይ ግን ከዳን” በማለት ገልጸዋል። ታዲያ የደህንነት ሚኒስትሩ ይህንን ሲሰሙ እጅግ በጣም በመደናገጣቸው መናገር ሁላ አቅቷቸው እንደነበር በወቅቱ በቦታው የነበሩት መርማሪዎች ተናግረዋል። በመሆኑም ሚኒስትሩ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማሪያም ሳይቀደሙ ለመቅደም ተነሱ። ጄኔራል ፋንታ ከሁለት ወር የእስር ቆይታ በኋላ ከነሚስጢራቸው ተገደሉ። ሀምሌ 13/1981 ከቀኑ ስድስት ሰዓት ላይ የኢትዮጵያ ድምጽ ብሔራዊ አገልግሎት እንዲህ የሚል ዜና አስተላለፈ።

“በግንቦት 8/1981 ተካሂዶ የከሸፈውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ያቀናበሩት ከሀዲው ጄኔራል ፋንታ በላይ ጠባቂያቸውን በካራቴ መትተው ለማምለጥ ሲሞክሩ በሌሎች ዘቦች ተገደሉ”
     ******************************************
አፈንዲ ሙተቂ
ግንቦት 7/2005
ሀረር
http://www.youtube.com/watch?v=GDjRkfq-toM

Monday, May 12, 2014

የሀያኛውን ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ፖለቲካ የቀየሩ አነስተኛ ሰነዶች- (በብዙዎች ጥያቄ የተደገመ)





አፈንዲ ሙተቂ

---
ይህንን አነስተኛ መጣጥፍ ከዚህ በፊት (በታህሳስ ወር 2006) ለጥፌው ነበር፡፡ ነገር ግን በርካታ ወዳጆቼ “ከፌስቡክ ግድግዳህ ላይ ልናገኘው አልቻልንም” ስላሉኝ እንደገና መድገሙ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ 

እነዚህ ሰነዶች በ20ኛው ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ አሳርፈዋል በማለት በዝርዝሩ ውስጥ የያዝኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ዝርዝሩ በሌሎች ምሁራንም ሆነ የጥናት ተቋማት እውቅና አልተሰጠውም፡፡ ማንም ሰው የክፍለ ዘመኑን የኢትዮጵያ የፖለቲካ አካሄድ ገምግሞ ከፍተኛ ተጽእኖ አሳድረዋል ያላቸውን ሰነዶች ሊጠቁም ይችላል፡፡ እኔም ይህንኑ ነው ያደረግኩት፡፡
---
ሰነዶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

1. አዕምሮ ጋዜጣ- 1904
2. የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ህገ-መንግሥት- 1923
3. የኤርትራ ፌዴሬሽን ህገ-መንግሥት 1944
4. የተሻሻለው የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ህገ-መንግሥት- 1948
5. የጀብሃ ቻርተር- 1954
6. የሜጫና ቱለማ ማህበር መተዳደሪያ ደንብ-1955
7. የብሄር ጥያቄ በኢትዮጵያ (በዋለልኝ መኮንን የተጻፈ ጽሑፍ)-1961
8. “ንህናን ዓላማናን”(እኛና ዓላማችን)- ሻዕቢያ ከጀብሃ የተገነጠለበት አነስተኛ ጥራዝ-1964
9. ደርግ ስልጣን የያዘበት አዋጅ- መስከረም 2/1967
10. የገጠር መሬትን ለህዝብ ያደረገው አዋጅ- የካቲት 25/1967
11. ዲሞክራሲያ ጋዜጣ (የኢህአፓ መመስረት ይፋ የሆነበት የፓርቲው ህቡዕ ጋዜጣ)- ነሐሴ 27/1967
12. የተሓሕት/ህወሐት ማኒፌስቶ- የካቲት 1968
13. የብሄራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት ፕሮግራም አዋጅ- ታህሳስ 1968
14. የህዝብ ድርጅት ጉዳይ /ቤት የተመሰረተበት አዋጅ- ሚያዚያ 1968
15. የኦነግ የፖለቲካ ፕሮግራም- ሰኔ 1968
16. ኢሰፓአኮ የተቋቋመበት አዋጅ-ሰኔ 1971
17. ኢሰፓ የተመሰረተበት አዋጅ- መስከረም 1977
18. የኢህዲሪ ህገ-መንግሥት-ጳጉሜ 1979
19. የኢትዮጵያ የሽግግር መንግሥት ቻርተር- ሀምሌ 1983
20. የፕሬስ አዋጅ- የካቲት 1984
21. የክልሎች ማቋቋሚያ አዋጅ- ጥቅምት 1985
22. ኢትዮጵያ ለኤርትራ ነጻነት እውቅና የሰጠችበት ደብዳቤ (በአቶ መለስ ዜናዊ የተጻፈ)-ሚያዚያ 1985
23. የኢፌዴሪ ህገ-መንግሥት- ህዳር 29/1987
24. የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ያበቃበት የአልጀርስ ስምምነት -ታህሣስ 1993
25. አብዮታዊ ዲሞክራሲና ቦናፓርቲስታዊ የመበስበስ አደጋዎች (በአቶ መለስ ዜናዊ የተጻፈ ጥራዝ)- ጥር 1993
26. የቅንጅት ማኒፌስቶ-1997

ከላይ የተዘረዘሩት ሰነዶች በኔ እይታ 100 ዓመት (1900-2000 በነበረው) የኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ አድርሰዋል፡፡ እያንዳንዱን ሰነድ ልብ ብላችሁ ካያችሁት የፖለቲካ ሚናው ከፍተኛ እንደነበረ በቀላሉ መረዳት ትችላላችሁ፡፡ ለምሳሌ አቶ መለስቦናፓርቲዝምበሚል ርዕስ የጻፉት ጽሑፍ 1993-95 የነበረውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ በከፍተኛ ጡዘት ውስጥ የጨመረ ነው፡፡ እነ ስዬ አብርሃን ከማባረር ጀምሮ የክልሎችን አስተዳደራዊ መዋቅር እስከመቀየር እና የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ለመሳሰሉት ፐሮግራሞች ትግበራ ጥርጊያ ጎዳና ያመቻቸ ነው (የጸረ-ሙስና ኮሚሽንም የርሱ ውልድ ነው)፡፡ የህዝብ ድርጅት /ቤት ማቋቋሚያ አዋጅምቀበሌየሚለውን የአስተዳደር አከፋፈል ከማስተዋወቅ ጀምሮ በቀይ ሽብር ውስጥ ከፍተኛ ሚና የነበራቸውን የጥበቃ ጓዶች እስከ ማስታጠቅ ድረስ ላሉት ታላላቅ ክስተቶች መፈጠር እንደ እርሾ ሆኖ አገልግሏል፡፡

በናንተ በኩል በዚህ ዝርዝር ውስጥ መካተት አለባቸው የምትሏቸው ሰነዶች የትኞቹ ናቸው? በናንተ ሚዛን ፖለቲካዊ ሚናቸው ሀይለኛ የሆኑትን መጠቆምና በኔ ያቀረብኩትን ዝርዝር መተቸት ትችላላችሁ (የኤርትራ ሰነዶች በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ተጽእኖ ስለነበራቸው ነው)፡፡
ሰላም
-----------------------
አፈንዲ ሙተቂ
ግንቦት 4/2006