Friday, August 30, 2013

==“የጂንኒ” ወግ==



ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
ክፍል አንድ
-------
በዚህች ጽሑፍ ከሰዎች ዓለም ወጥተን ወደ “ጂንኒ” ዓለም ልንገባ ነው፡፡ ሀይለኛ የፍርሃት ስሜት (phobia) የሚፈታተናችሁ በቀን እንጂ በጨለማ ባታነቡት ይመረጣል፡፡ በልጅነታችሁ “አንድ ሺህ አንድ ሌሊት” (The Arabian Nights) የሚባለውን ዝነኛ የተረት መጽሐፍ ያነበባችሁ ሰዎች ግን ስለ“ጅንኒ” በቂ ተመክሮ ያላችሁ በመሆኑ ምንም የሚያስፈራችሁ ነገር የለም፡፡ እንደኔ “ጂንኒ”ን ሳትተናኮሉ ከርሷ ጋር እየተያያችሁና አንዳንዴም እየተጋፋችሁ የመተላለፍ ልምድ ያላችሁ ሰዎችም በፈለጋችሁት ጊዜ ልታነቡት ትችላላችሁ፡፡
 -------
“ጂንኒ”ን አማርኛው “ጋኔን” በማለት የሚጠራት ይመስለኛል፡፡ የብዙ ቁጥር ስሟ ደግሞ “አጋንንት” ነው፡፡ ዐረብኛው “ጂንኒይ” ወይንም “ጂንን” ይላታል (አንዷ “ን” ለማጥበቅ ነው የገባችው- ስለዚህ ሁለቱንም እንደ አንድ ፊደል በማድረግ አንብቧቸው)፡፡ ኦሮምኛና የሀረሪ ቋንቋ ከዐረብኛ የወረሱትን ስም ቤተኛ በማድረግ “ጂንኒ” ይሏታል፡፡

  የጅንኒ ትውፊት መሰረቱ ዐረቢያ ነው፡፡ እዚያ ዘንድ በእስልምና በኩል ከመጣው የጂንኒ አስተምህሮ በተጨማሪ የዐረቦች መጠነ ሰፊ ልማድ ታክሎበት ራሱን  የቻለ ትልቅ ስነ-ቃል ሆኗል፡፡ በምስራቅ ኢትዮጵያ የሚነገረው የጅንኒ ወግም መሰረቱ ይኸው ነው፡፡ ሆኖም ቤተኛው አቅላችንና ኑሮአችን ትውፊቱን እያደለበው በጣም አዳብሮት ራሱን የቻለ ሀገርኛ ስነ-ቃል አድርጎታል፡፡  

    ይህ የጅንኒ ትውፊት በስፋት የሚታወቀው በኦሮሞ እና በሀረሪ ህዝቦች ዘንድ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በምስራቅ ኢትዮጵያ የተወለደ ማንኛውም “ጅንኒ”ን በደንብ ያውቃታል፡፡ አማራም ሆነ ትግሬ፣ ጉራጌም ሆነ ወላይታ ልደቱ በሀረርጌ ክፍለ ሀገር ከሆነ የ“ጅንኒ”ን ማንነት በደንብ ይነግራችኋል፡፡

   በርግጥም በዚህ ጽሑፍ የማወጋችሁ በምስራቅ ኢትዮጵያ የማውቃትን “ጂንኒ” ነው፡፡ ስለዚህ በሌላ አካባቢ የሚታወቁ “ጂንኒ” ቀመስ ወሬዎችን አልቀላቅልበትም፡፡ በተጨማሪም በምስራቁ ትውፊት “ጅንኒ” እንደ ሴት “እርሷ” እየተባለች የምትጠራ በመሆኑ እኔም ይህንኑ ፈለግ እከተላለሁ፡፡

  የእስከ አሁኑ እንደ መግቢያ ይሁንልኝ፡፡ ከዚህ በኋላ ግን አካሄዴን እቀይራለሁ፡፡ ስለ “ጅንኒ” ሳወጋችሁ “እንዲህ ይባላል”፣ “እንዲህ ተብሎ ይነገራል” የሚሉ አነጋገሮች ከአሁን በኋላ አያስፈልጉኝም፡፡ ምክንያቱም የማወጋችሁ ስላነበብኩትና ስለሰማሁት ነገር ሳይሆን በህይወቴ ያለፍኩበትን ነገር ነውና፡፡ “እንዲህ ይባላል”፣ “እንዲህ ይነገራል” ካልኩማ ምኑን ስለ “ጂንኒ” ተጫወትነው? “ጅንኒ”  እንዲህ ናት” ስል ከርሜ አሁን ልገልበጥ እንዴ? ይህማ ደግ አይደለም፡፡ ስለዚህ ልክ እንደ ልጅነቴ ዘመን ነው የምጽፍላችሁ! ያሻው ሰው “እውነት ነው” ይበል፤ ያልፈለገውም እንደፍላጎቱ ይሁንለት፤ የፈለገው በሳይንስ ይፈትነው፡፡ ወጋችን ይመርልን እንጂ ለሌላ ሌላው እኛ ምን አገባን?
                   *****  *****  *****
በአማርኛ “ጋኔን” የሚባለው ነገር ምንጊዜም ቢሆን እርኩስ ነው፡፡ ደግሞም በሌሎች ላይ የሚያድር “መንፈስ” ነው እንጂ ከሌሎች ተለይቶ የሚኖር ፍጡር አይደለም፡፡ ጋኔንን የሚገፋው ሰይጣን ነው፡፡ በሰይጣን ጦር የተወጋ ሰው ነው የ“አጋንንት” መንፈስ የሚያድርበት፡፡

   “ጂንኒ” ግን ራሷን የቻለች ፍጥረት ናት፡፡ የራሷ አካልና ንቅናቄም አላት፡፡ እንደ ሰው ትበላለች፤ ትጠጣለችም፡፡ ግብርና ውሎዋም እርኩስ ብቻ አይደለም፡፡ በጎ ምግባር ያላቸውና በጎ የሚሰሩ “ጂንኒዎች” በብዛት አሉ፡፡ እርኩስ የሆኑና ክፋትን ብቻ በምድር ላይ የሚዘሩ ጂንኒዎችም ሞልተዋል፡፡

  “ጂንኒ” ማሰብ ከሚችሉ ሶስት ፍጥረቶችም መካከልም ናት (ቀሪዎቹ ሁለቱ መላእክትና የሰው ልጅ ናቸው)፡፡ የራሷ መንግሥትና ሀገርም አላት፡፡ የምትኖረው በምድር ላይ ብቻ ሳይሆን በባህርም ጭምር ነው፡፡ በተራራ፣ በጫካ፣ በዛፍ ስንጥቆች መሀል፣ በወንዝ፣ በኩሬ ወዘተ… መኖር ትችላለች፡፡

“ጅንኒ” እንደ ሰው በሁለት እግሯ ነው የምትራመደው፡፡ ነገር ግን የታችኛው ቅልጥሟ ከአህያ እግር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ የእግሯ ኮቴም ቢሆን ከከብት እና ከአህያ ሽኮና ጋር ነው የሚመሳሰለው፡፡ ከዚህ ሌላ መላው የጂንኒ አካል ጸጉራም ነው፡፡ ከእግር እስከራሷ ድረስ በጸጉር ተሸፍናለች፡፡ ይህ ጸጉሯም ከቀበሮ ወይም ከውሻ ጸጉር ጋር ይመሳሰላል፡፡ መልኩ ግን እንደ አህያ ቆዳ ዳለቻ ነው፡፡ መላው አካሏም ዳለቻ መልክ ነው ያለው፡፡  

   ጅንኒ እንዲህ ሆና የምትታየው በተፈጥሮ አካሏ ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ የተፈጥሮ ገላዋ ሁልጊዜ አትገኝም፡፡ አካልና ገላዋን እንደፈለገች መቀያየር ትችላለች፡፡ በአንድ ጊዜ ግዙፍ ሆና ከዛፍ ቁመት ጋር ልትስተካከል ይቻላታል፡፡ ብትፈልግ ላም፣ ካሻትም በሬ፣ ከፈቀደችም ድመት መሆን ትችላለች፡፡ ባህሪዋንም ቢሆን እንደፈለገች የመቀያየር ችሎታ አላት፡፡ አንድ ጊዜ “ደግ”፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ክፉ ትሆናለች፡፡

  “ጂንኒ” በጥበብም ሆነ በችሎታዋ ከሰዎች ትበልጣለች፡፡ ሰዎች ያላቸው እውቀት ቢደመር የርሷን ዕውቀት ሩቡን እንኳ አይሆንም፡፡ ለምሳሌ የከበሩ ማዕድናት የሚገኙባቸውን ቦታዎች በቀላሉ ማወቅ ስለሚቻላት ማዕድናቱን እንዳሻት እያወጣች ትጠቀምበታለች፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ባህሪዎቿ ከእንስሳ እንኳ አትሻልም፡፡ ለምሳሌ ከንጹህ ቦታ ይልቅ ቆሻሻ ቦታዎችን ትመርጣለች፡፡ ከየቤቱ የሚጣለውን ቆሻሻ እንደ ምግብ የመብላት መጥፎ አመልም አላት፡፡ ደምና ፈርስ ከሚደፋበት ቦታ ትመላለሳለች፡፡ በነዚህ ቦታዎች ያየችውን እርጥበትና ፍሳሽ አትምርም፡፡ ከመሬቱ ላይ እየላሰች ትጨርሰዋለች፡፡

  “ጂንኒ” አመድንም እንደ ምግብ ትበላለች፡፡ ከዳቦ ቤቶች (ዳቦ በባትራ የሚያግሩትን የድሮ ዳቦ ቤቶች ማለቴ ነው) የሚወጣው አመድ የነፍስ ምግቧ ነው፡፡ ከዚህ ሻል የሚሉት ጅንኒዎች ግን “ቅቤ” መጠጣትን ያዘወትራሉ፡፡ በጣም የሚጀነኑትና የሚኩራሩት ጂንኒዎች ደግሞ ልክ እንደ “ቡዳ” ሰዎችን ይበላሉ፡፡ በተለይ ቆንጆ ሴቶች፣ ወንዳወንድ ቁመና ያላቸው ወንዶች እና ህጻናትን አይምሩም፡፡
                *****  *****  *****
 “ጅንኒ” ሀይለኛ ናት፡፡ በእጇ የነካችውን ነገር ወደ አፈር መቀየር ትችላለች፡፡ ከዐይኗ በምታፈልቀው ጨረር የወጋችው ዛፍም ሆነ እንስሳ ድርቅ ብሎ ይቀራል፡፡ ነፋስን እያሽከረከረች ከፍተኛ አደጋ መፍጠር ትችላለች፡፡ በርሷ የሚፈጠሩት አደጋዎችና  በርሷ እየተወጉ ሚጠወልጉ ፍጥረታት ከብዛቷ ጋር ሲነጻጻሩ ግን በጣም አነስተኛ ናቸው፡፡ በተለይ ጂንኒ በዚህ ዩኒቨርስ ውስጥ ስትኖር ሆን ብላ ሰዎችን የምትተናኮለው አልፎ አልፎ ነው፡፡ በአንድ መንደርና በአንድ ከተማ እንኳ ከሰዎች ጋር እየኖረች ከነርሱ ጋር ብዙም አትጋጭም፡፡ ደግሞም አልፎ አልፎ (rarely) ካልሆነ በቀር አብዛኛውን ጊዜ ለሰዎች በግልጽ ስለማትታይ ግጭቱ የሚፈጠርበት እድል በጣም የመነመነ ነው፡፡

   ነገር ግን “ጂንኒ” በጣም በሚርባት ጊዜ ለሰዎች በግልጽ ልትታይ ትችላለች፡፡ በዚያን ጊዜ በመንገዷ ላይ የምታገኘውን ሰው ያለ ርህራሄ በመርዛማ ፍላጻዋ ወግታ “ፓራላይዝ” ልታደርገው ትችላለች፡፡ አንዳንዴ ደግሞ ሰውየውን ወግታ ደም ከአፍና ከአፍንጫው ታስወጣዋለች፡፡

 እንደ “ቡዳ” ሰዎችን የሚበሉት “ጂንኒዎች” ደግሞ ይህንንም አያደርጉም፡፡ በወጉት ሰው ላይ ለዘላለም ተለጥፈው አሳሩን ያሳዩታል፡፡ ከላይ እንዳወሳሁትም የነዚህኛዎቹ ጂንኒዎች ዋነኛ ዒላማ ቆንጆ ሴቶች (በተለይ ረጃጅም ጸጉር ያላቸውና ዐይናቸው እንደ ኮከብ የሚያበራ)፣ ቆንጆ ወንዶችና ህጻናት ናቸው፡፡ ጂንነዋ እነርሱ ውስጥ ከገባች በኋላ መንፈሷን በሰውነታቸው ውስጥ ትተውና ሰዎቹ የሚበሉትን ትጋራለች፡፡ ደማቸውንም ትመጣለች፡፡ በዚህም የተነሳ ጅንኒ የወጋችው “ቆንጆ” ሰው በሀይለኛ የደም ማነስ በሽታና በልብ ህመም ይሰቃያል፡፡ “ያሲን” እና “ተባረክ” ካልተቀራበትና “ወዳጃ” ተቀምጦ በዱዓ አላህን ካልለመነለት በስተቀር ጂንነዋ ከሰውዬው ውስጥ አትወጣም፡፡

  በሌላም በኩል አራት ዓይነት ሰው በጅንኒ ሊጠቃ ይችላል፡፡ አንደኛው “ጅንኒዎች” ለምግብ ፍለጋ በሚያዘወትሩት ቦታ ላይ የሚመላለስ ክልፍልፍ ሰው ነው፡፡ ጂንኒዎች እንዲህ አይነቱ ሰው ለነገር ፍለጋ የመጣባቸው ስለሚመስላቸው ዋጋውን ይሰጡታል፡፡ ቆሻሻ የሚደፋ ሰውን ግን በጭራሽ አይነኩትም፡፡ ሁለተኛው ጅንኒዎች እንደ የእዝ ማዕከል (command post) በሚገለገሉበትና እንደ ግምጃ ቤት (treasury) በሚጠቀሙበት ቦታ ላይ መመላለስ የሚያበዛ ሰው ነው፡፡ ጂንኒዎች ይህንን ሰው ሰላይ ነው ብለው ስለሚጠረጥሩት (ወይንም “በኛ እውቀት መክበር የሚፈልግ ነው” ብለው ስለሚያስቡ) በቀስታና በጨረር ይወጉታል፡፡ ከዚህ ሌላ በነዚህ ስፍራዎች ላይ ጅንኒዎች የማይፈልጉትን ነገር የሚያደርግ ሰውም የጥቃቱ ሰለባ ሊሆን ይችላል፡፡ ሰውየው በስፍራዎቹና በአቅራቢያቸው እሳት ማቀጣጠል ወይንም ጩኸት ማብዛት የለበትም፡፡ በስፍራዎቹ ላይ አዘውትሮ መመላለስ የሚያበዛ ሰውም ከጥቃት አይድንም፡፡ እነዚህ ስፍራዎች በጣም ጸጥ ብሎ የሚፈስና ጥልቀት ያለው ወራጅ ወንዝ (በኦሮምኛ ቱጂ ይባላል)፤ ረግረግ፣ ጥልቀት ያለው የውሃ ጉድጓድ፣ ወና የሆነ ትልቅ አዳራሽ፣ ግዙፍ የዋርካ ዛፍ፣ ግዙፍ ቋጥኝ ፣ ሰፊ እና ጥልቅ ገደል… የመሳሰሉት ናቸው፡፡
     በሶስተኛ ደረጃ ለጂንኒ ጥቃት የሚጋለጠው ጅኒንዎች ለስምሪት በሚወጡባቸው ጊዜያት ምላሱንና እንቅስቃሴዎቹን ለአደብ ያላስገዛ ሰው ነው፡፡ ጅንኒዎች በብዛት የሚሰማሩት ጧት፣ ቀን በጠራራ ጸሐይ (ጸሐይዋ የሰው አናት ልትበሳ በምትደርስበት ጊዜ)፣ እና በጸሐይ መግቢያ ወቅት (“ሚስቲጃብ” ወይም “መግሪብ”) ነው፡፡ በነዚህ ጊዜያት በቢሊዮኖች የሚቆጠር የጂንኒ ሰራዊት ሰለሚሰማራ በምድር ላይ የጅንኒ ቁጥር ከሰዎች በብዙ እጥፍ ይበልጣል፡፡ ስለዚህ ሰዎች በነዚህ ጊዜያት እንቅስቃሴ ማብዛት የለባቸውም፡፡ መሳደብና መራገምም ይለባቸውም-ጅንኒ እርሷ የተሰደበች መስሏት ተሳዳቢዉን ሰውዬ በጥፊ አጠናግራ ፊቱን ለዘልዓለሙ ወደ አንድ ጎን ልታጣምመው ትችላለችና፡፡ በአራተኛ ደረጃ ለጂንኒ ጥቃት የሚጋለጠው በውድቀት ሌሊት መሄድ የሚያበዛ ሰው ነው፡፡ በተለይ ሌሊት በተራራማና ጸጥተኛ በሆነ ሜዳማ ስፍራ የተገኘ ሰው የጂንኒ ጦርና ፍላፃ  ይወረወርበታል፡፡

   አንዳንድ ተንኮለኛ ጅንኒዎች ግን ሰዎችን ለማጥቃት ምንም ምክንያት አይፈልጉም፡፡ ሰዎች ባልጠበቁት ስፍራና አጋጣሚ ሁሉ እነዚህ ተንኮለኛ ጂንኒዎች መርዛማ ቀስታቸውንና ጨረራቸውን ሊወረውሩ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ አንዲት ጅንኒ እናንተ ሳታዩዋት “እገሌ” ብላ ልትጠራችሁ ትችላለች፡፡ በተለይ ሰው በሌለበት ምድረ በዳ፣ በተራራ ላይ፣ በደንና በማሳ ውስጥ ወዘተ ተንኮለኛ ጅንኒዎች ስንቱን ሚስኪን ሰው እየጠሩ ጉድ አድርገውታል፡፡ ከእንደዚህ ዓይነት ጅንኒ ራሱን መጠበቅ የሚፈልግ ሰው የተጣሪውን ማንነት ሳያጣራ “አቤት” ማለት የለበትም፡፡ “አቤት” ካለ ግን እድሉ ያውጣው! እርሱን የጠራው ፍጡር የሰው ልጅ ከሆነ በርግጥም ቀኑ አልደረሰም ማለት ነው፡፡ “ጅንኒ” የጠራችው እንደሆነ ግን ሰውየው ከዓለም ላይ መሰናበቱን ይወቅ! ቢበዛ ሶስት ቀን ብቻ በህይወት ቢቆይ ነው፡፡

   እንዲህ አይነት ነገር የገጠመው ሰው በ“ጅንኒ” መጠራቱንና በሰው ልጅ መጠራቱን እንዴት መለየት እንደሚችል አውቃችኋል? ቀላል ነው፡፡ የጥሪው ድምጽ ወደ መጣበት አቅጣጫ ዞር ብሎ ማየትን ብቻ ነው የሚጠይቀው፡፡ በዚያ አቅጣጫ ሰው ከሌለ “ጅንኒ” ናት ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሰውየው ከቻለ “ያሲን” እና “ተባረክ” እየቀራ፣ ካልቻለም “አዑዚ ቢላሂ ሚነ-ሼይጣኒ ረጅም” ብሎ ከአካባቢው በቀስታ መልቀቅ አለበት፡፡ በሌላ  በኩል ሰውየው የሰማው የወንድ ድምጽ ሆኖ ሳለ ወደ ድምጹ አቅጣጫ ሲዞር ሴት ካጋጠመው፣ ወይንም የህጻን ድምጽ ሰምቶ ሽማግሌ ከታየው በርግጥም እርሱን የጠራችው “ጅንኒ” ናት ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ሰው ህይወቱን ማትረፍ ከፈለገ በቶሎ “አዑዙ ቢላሂ” ይበልና ከአካባቢው ላፍ ብሎ ያምልጥ፡፡ እምቢ ካለ ቁርጡን ይወቅ! እኛ የለንበትም፡፡
                *****  *****  *****
የጅንኒ ወጋችን ተጀመረ እንጂ አላለቀም፡፡ የጂንኒ የሌብነት ጉዞ፣ የጅብና የጂንኒ ጦርነት፣ የጂንኒ እና የምስጥ ውል፣ የቀለበቷ ሚስጢር፣ የጂንኒ ሸጎዬ ጨዋታ፣ የአስማእና የኢፍሪት ወግ.፣ የልዩ ልዩ ሰዎች የጂንኒ ገጠመኝ ወዘተ… ገና ይቀሩናል፡፡ በሚቀጥለው ሌሊት እንመለስባቸዋለን፡፡

  በነገራችን ላይ የምስራቅ ኢትዮጵያ ልጆች “ወዘተ” ለማለት ሲፈልጉ እንዴት እንደሚሉ በደንብ ታውቁታላችሁ አይደል? “ጅንኒ ጃንካ”፣ “ጂንኒ ቁልቋል”፣ “ጂንኒ ጀቡቲ”፤ “ጂንኒ ጡጡሩቅ”… ከተሰኙት ሐረጎች አንዱን መምረጥ ነው፡፡ እኛ “ወዘተ”ን የተማርናት በትምህርት ቤት ነው፡፡
   “ጅንኒ” ለዛሬ እንዲህ ናት፡፡ በሉ አሁን “አዑዙ ቢላሂ” በሉ፡፡
---
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 25/2005

Wednesday, August 28, 2013

ዓሊ ቢራ፣ የሸዋሉል መንግሥቱ እና “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ”


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-------
ዛሬ ስለምን የማወጋችሁ ይመስላችኋል? ስለ“ፈስ” ነው የምንጨዋወተው፡፡ አዎን ስለ “ፈስ” ነው! ስለርሱ መጻፍ አይቻልም እንዴ? ስለርሱ ብንወያይ ነውረኛ እንሆናለን? የፈለጋችሁን በሉኝ! ስለ “ፈስ” ልጽፍ አሐዱ ብያለሁ፡፡ የጀመርኩትንም ሳልጨርስ አላቆመም፡፡
  
  ደግነቱ ስለሚገማ “ፈስ” አይደለም የማወጋችሁ (ስለዚህ አፍንጫችሁን አትያዙ! ቂቂቂቂቂ….)፡፡ ስለማይገማ “ፈስ” ነው የምጽፍላችሁ፡፡ እንዲያውም ይህ “ፈስ” ባለመልካም መዓዛ ነው፡፡ ሽታው እንደ ሉባንጃ (ሊባንጃው) እና እንደ “ሊባን ፎህ” መዓዛ ያውዳል፡፡
  
   ወዳጆቼ! እየዘባረቅኩኝ አይደለም፡፡ እውነት ነው፡፡ መዓዛው እንደ “እጣን” የሚያውድ ፈስ አለ፡፡ እንዲህ አይነቱን “ፈስ” የሚለቅ ሰው የሚበላው ምግብ በ“ቱራበል ሚስክ” የታሸ፣ በ“አንበር” የዋጀ፣ የፓሪስ ሽቶ የተርከፈከፈበት ወዘተ… ሳይሆን ይቀራል ግን?    
   
   ምንም አትጠራጠሩ! መዓዛማውን “ፈስ” የሚለቀው ሰውዬ እንደኛው ዓይነት ምግብ ነው የሚበላው፡፡ እንደኛው ውሃ ነው የሚጠጣው፡፡ እንደኛው አትክልትና ፍራፍሬ ይመገባል፡፡ ታዲያ “ፈሱ”ን ባለመዓዛ የሚያደርገው ምን ይሆን? እስቲ አብረን እንየው፡፡
  *****  *****  *****
  መለያየት ህመም ነው፡፡ ትልቅ ስቃይ ነው፡፡ ከምትወዱት ወዳጅና ዘመድ መለየት ደግሞ የሞት ታናሽ ወንድም ነው፡፡ አብሮ አደግ ጓደኛችሁን ወይም የምትወዱትን የቤት እመቤታችሁን በህይወት እያላችሁ ከተለያችኋቸው ስቃይና መከራው በቁም ይገድላችኋል፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹን ወዳጆችና ዘመዶቻችሁን በምን ቋንቋ ነው የምትገልጹት? በሌላ አነጋገር ለርሱ/ለርሷ ያላችሁን ገደብ የለሽ ፍቅር እንዴት ብላችሁ ነው የምታስረዱት?፡
   
   የናንተን እንጃ! ለዚህ ጽሑፍ መሰረት የሆነውን ትውፊት ያፈለቁት የሀረርጌ ኦሮሞ ልጃገረዶች ግን ለእኩያቸው ያላቸውን ፍቅር ሲገልጹ “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” ነው የሚሉት፡፡ ምን ማለት መሰላችሁ? “ውዴ/ጓዴ! አንቺ ባለእጣን መዓዛ ፈስ” እንደማለት ነው፡፡ በሙሉ ዐረፍተ ነገር ሲጻፍ ደግሞ “አንቺ የኔ ውድ ጓደኛዬ፣ እህቴ፣ ነፍሴ! ሌላው ቆርቶ ፈስሽ እኮ ለኔ እንደ እጣን ነው” እንደማለት ይሆናል፡፡
   
    ጥቅሉን ሐረግ ስንዝረዝረው ፍቺው የትየለሌ ነው የሚሆንብን፡፡ ለአሁኑ ግን “የኔ ውድ ባልንጀራዬ! አንቺ አብሮ አደጌ! የኔና ያንቺ መውደድ እኮ ገደብ የለውም፡፡ የመውደዳችን ጥልቀት ጥላቻን ከመሀከላችን ሰርዞታል፡፡ ሌላው ነገር ይቅርና ሰዎች ይገማል ብለው አፍንጫቸውን የሚይዙለት “ፈስ” በኔና ባንቺ መሀል ቢከሰት እንደ ሽቶና እንደ እጣን ነው የምንቆጥረው፤ ፍቅሬ! ሄዴ! ውዴ! እወድሻለሁ…” ወዘተ… እያልን ልንፈስረው (ልንፈታው) እንችላለን፡፡

   “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” እያሉ ለጓደኛቸው ፍቅራቸውን የሚገልጹት የሀረርጌ ኦሮሞ ኮረዳዎች ናቸው- ከላይ እንደገለጽኩት፡፡ ይሁንና ኮረዳዎቹ በ“ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” አንጀቱን የሚበሉትና ልቡን የሚያብሰለስሉት ሰው ወንድ አይደለም፡፡ ሴት አብሮ አደግ  ጓደኛቸውን ነው እንዲህ የሚፈታተኑት፡፡ ይህን ግን ለሁልጊዜ እንዳይመስላችሁ፡፡ ለአንድ ቀን ብቻ የሚቆይ ትእይንት ነው፡፡ ይኸውም ባልንጀራቸው በምታገባበት ዕለት ነው፡፡
  
  በዚህ ዕለት ጓደኛቸው ከነርሱ ተነጥላ ከባሏ ጋር መኖር ትጀምራለች፡፡ በዚህ ዕለት በልጅነቷ አብሯት አፈር እየፈጩ የተጫወቱ፣ ወንዝ ሄደው ውሃ የቀዱ፣ ጋራ ወጥተው እንጨት የቆረጡና በታዛ ስር ስፌድ የሰፉ ጓደኞቿን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ትሰናበታለች፡፡ “የእገሌ ልጅ” መባሏ ቀርቶ “የእገሌ ሚስት” እየተባለች መጠራት ትጀምራለች፡፡ ጓደኞቿም ከርሷ ጋር እንዳሻቸው የሚሆኑበት እድል ለወደፊቱ ተመልሶ እንደማይመጣ የሚያረጋግጡት በዚህ እለት ነው፡፡ ስለዚህ በዚህች ታሪካዊ ዕለት የመልካሙን ጊዜ ፍጻሜ  እያማረሩ በእንባ ይሸኟታል፡፡ እነዚህ ኮረዳዎች ለጓደኛቸው የነበራቸውን ፍቅር ለመግለጽና የወዳጅነታቸውን ግዝፈት ለማሳየት ከ“ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” የተሻለ ሐረግ የላቸውም፡፡ ይህንን ሐረግ እየደጋገሙ በመምዘዝ “በኔና ባንቺ መሀል መጥፎ ነገር የለም፤ አለ ቢባል እንኳ እኔ ሁሉንም በጎ አድርጌ ነው የምመለከተው” እያሉ ይሰናበቷታል፡፡ 
 
*****  *****  *****
እዚህ ዘንድ አንድ አስገራሚ ነገር ላጫውታችሁ፡፡

“ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” የኦሮምኛ ሐረግ ነው ብያችኋለሁ፡፡ በቀጥተኛ አገላለጽ “ያንቺ ፈስ ለኔ እንደ እጣን ነው እኮ” የሚል ፍቺ እንዳለውም ተናግሬአለሁ፡፡ ታዲያ “በኦሮሞ ባህል እንዲህ ተብሎ ይዘፈናልን?” የሚል ጥያቄ ሊቀርብልኝ ይችላል፡፡ መልሱ “አይቻልም” ነው፡፡ በአማርኛው ዘይቤ “ፈስ መጣብኝ” ወይንም “ፈሴን ለቀቅኩት” የሚሉት አነጋገሮች “ነውር” ተደርገው እንደሚታዩት ሁሉ በኦሮሞ ባህልም “ፈሴን ፈሳሁት” የሚለው አነጋገር የጨዋ ደንብ አይደለም፡፡ የኦሮሞ ባህል እንዲህ አይነቱን ንግግር “ሰፉ” (taboo) ይለዋል፡፡ “ሰፉ” የሆነ አነጋገር ህዝብ በተሰበሰበበት ቦታ ቀርቶ በቤት እንኳ ይከለከላል፡፡ ይሁንና የሀረርጌ ኮረዶች በግልጽ “ሐደሶ ሊባነታ” እያሉ ይዘፍናሉ! ለዚያውም በሰርግ ቤት!! ማን ፈቅዶላቸው ነው ግን?
    
   ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ኮረዶቹ (ልጃገረዶቹ) የተጠቀሙበት ቃል የኦሮምኛው “ዹፉ” አይደለም (በአማርኛ “ፈስ” ማለት ነው፤ “መፍሳት” ማለትም ይሆናል)፡፡ “ፈስ”ን ለመግለጽ የገባው ቃል የዐረብኛው “ሐደስ” ነው፡፡ በሀረርጌ ኦሮሞ ባህል በህዝብ ፊት ወይንም በአደባባይ ቢጠሩ እንደ ነውር የሚቆጠሩ ነገሮችን ሳንሸማቀቅ ለመግለጽ ከፈለግን በዐረብኛ ስማቸው ነው የምንጠራቸው፡፡ ለምሳሌ “የወንድ ብልት” ለማለት ካሻን “ዘከር” እንላለን፡፡ የሴት ብልትንም “ሐሸፋ” ብለን ብንጠራው እንደ ነውር አይቆጠርብንም፡፡ ሽንት ቤት ለማለትም “ኸላ” ማለት ይቻላል፡፡ ሰገራንም በኦሮምኛ ስሙ ሳይሆን በዐረብኛው ስም “ቦውሊ” በማለት እንጠራዋለን፡፡ (የባውሎጂ አስተማሪዎቻችን የሰው ልጅ የመራቢያ አካላትን በአማርኛ ለመግለጽ እያፈሩ፤ በእንግሊዝኛ ግን ያለምንም ፍርሃት “Penis”, “Vagina”, “Urethra”, “Testicle”, እያሉ የሚጠሩበትን ብሂል አስታውሱ)፡፡

 *****  *****  *****
  ወደ “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” እንመለስ፡፡ “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” አንድ ሐረግ ብቻ ነው ያለው፡፡ ነገር ግን በሰርግ ቤት “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” ብቻውን አይባልም፡፡ እርሱን የሚያጅቡ ሌሎች ግጥሞች ታክለውበት በቡድን የሚዘፈን ዜማ ሆኗል፡፡
    
“ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” እያሉ መዝፈኑን ማን እንደጀመረው አይታወቅም፡፡ የዘፈኑ ግጥሞችም ከቦታ ቦታ ይለያያሉ፡፡ ዜማውም ሊለያይ ይችላል፡፡ ነገር ግን አዝማቹ ምንጊዜም ቢሆን አንድ አይነት ነው፡፡ እርሱም ባለሁለት መስመር ነው፡፡ እንዲህ ይሄዳል፡፡

    “ዮቢ ዮቢ ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ
     ወይ ነገየቲ ናን ጄኢ ሂሪዮ አማነታ”

     ግጥሙን ከነነፍሱ ወደ አማርኛ መመለስ በጣም ይከብዳል፡፡ ነገር ግን እንዲህ ሊባል ይችላል፡፡
 
“ውዴ ጓዴ የሌለብሽ እንከን
  ያንቺ “ሐደስ” እኮ ነው የኔ እጣን
 ደህና ሁኚ በይኝ ውዴ አደራሽን”
 (“ሐደስ”ን ሳንፈታው እንዳለ ብንወስደው ይሻላል)

ይህ ምትሐታዊው “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” በሀረርጌ ገጠሮች ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ እጅግ ውብ ጣዕም ባለው ዜማ ተቀምሮ ለኢትዮጵያ ህዝብ በካሴት ቀርቧል፡፡ ለዚያውም ከ30 ዓመታት በፊት! የሚገርመው ታዲያ ያኔ “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” እያለ የዘፈነው ሴት አይደለም፡፡ አንጋፋው አርቲስት ዶ/ር ዓሊ ቢራ ነው! ይህ ትንግርት እንዴት ሊፈጠር ቻለ?
    
    መልሱን ለማወቅ ካሻችሁ ከሁለት ቀናት በፊት (ሰኞ ነሐሴ 19/2005) በጻፍኩት ጽሑፍ ስራዋን በመጠኑ ያስተዋወቅኳችሁን ጋዜጠኛና ደራሲ የሸዋሉል መንግሥቱን የግዴታ ማንሳት ይኖርብናል፡፡ ምክንያቱም “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ”ን ዓሊ ቢራ በዘፈነው መልኩ አቀናብራ ዘፈን እንዲሆን ያደረገችው እርሷ ናትና!
 
   የሸዋሉል መንግሥቱ የሀረርጌ ተወላጅ ናት፡፡ በምስራቁ የኦሮሞ ባህል ውስጥ ነው ያደገችው፡፡ በሀረርጌ ገጠሮች ሴቶች “ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ”ን ሲዘፍኑ አይታለች፡፡ እነዚያ ኮረዳዎች ጓደኛቸው በትዳር ስትለያቸው “እስከ ወዲያኛው ተለያየን” እያሉ በእንባ እንደሚሸኟት ታውቃለች፡፡ ዘፈኑን ለዓሊ ቢራ የሰጠችበትን መነሻ ለጊዜው በትክክል ባናውቀውም ድርሰቱን ስትጽፈው የነዚያ ኮረዳዎች እንባ እየታያትና የመለያየትን ክፉ እጣ እያሰበች እንደሆነ ለመረዳት አይከብደንም፡፡ በዚህም የመለያየትን አስከፊነት በሚገባ ለመግለጽ ችላለች፡፡ ለዚህ ቀላሉ አብነት በዘፈኑ ግጥም ውስጥ የሚታየው የእንጉርጉሮ ሀቅታና የሐዘን ድባብ ነው፡፡ እስቲ ሙሉ ግጥሙን ከአማርኛው ትርጉም ጋር ልጻፍላችሁ (በነገራችን ላይ የሸዋሉል ባለ ሁለት መስመሩን አዝማች ይበልጥ በማስፋት ባለ አራት መስመር አድርገዋለች፤ ስለዚህ ቀጥዬ የምጽፍላችሁ ባህላዊውን ግጥም ሳይሆን እርሷ የጻፈችውን ባለ አራት መስመሩን ግጥም ነው)፡፡
--------
አዝማቹ

Way yoobi yoobi yoobi hadasoo libaanta (ውዴ ጓዴ ባለ መዓዛማው “ሐደስ”)
Way yoobi yoobi bal’oo hiriyoo imaanta (ውዴ ጓዴ አደራችን አይገሰስ)
Wa nagayatti nan je’i hiriyoo ta dhaammata (እስቲ ለስንብትሽ ደህና ሁን በይኝ)
Way eenyu eenyu eenyu hiriyoo nayaadata  (አንቺ ከሄድሽማ ማን ነው የሚያስታውሰኝ)
Hiriyoo nagaafata (ማን ነው የሚጠይቀኝ)
----------
Guyyaan naaf hindhihu halkan naaf hinbarihu (አይነጋልኝም ሌቱ ቀኑም አይመሽልኝ)
Koottu mee yaa boontuu simalee naaf hintahu (እስቲ ነይ የኔ ውድ ያላንቺም አይሆንልኝ)
Si laalu si hin’argu siyaamu hin awwaatu (በዐይኔ አላይሽም ብጠራሽም አትሰሚኝ)
Naduraa fagaatte iddoon ati jirtu (ያለሽበት ቦታ እንደዚህ ርቆኝ)
Osonin si eegu nin seena ninbaha (አንቺን እያየሁ እገባና እወጣለሁ)
Yaadni kee narakke ani akkamin taha (ናፍቆትሽ አስጨነቀኝ እንዴት ነው የምሆነው?)
   
 *****  *****  *****
ዓሊ ቢራ ከዛሬ ስምንት ዓመት በፊት በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 የቅዳሜ ጨዋታ ፕሮግራም ከመዓዛ ብሩ ጋር ባደረገው ቃለ-ምልልስ ስለዘፈኑና ስለደራሲዋ ማውሳቱ ትዝ ይለኛል፡፡ ነገር ግን ያኔ እርሱ የጠቀሳት የግጥሙ ደራሲ የሸዋሉል መንግሥቱ መሆኗን ልብ አላልኩትም፡፡ ነገሩን በቅርብ ጊዜ ባደረግኩት ምርመራ ነው የደረስኩበት፡፡ ያቺ ውድ ደራሲና ጋዜጠኛ ከዓሊ ቢራ ጋር ብቻ ሳይሆን ከበርካቶች ጋር በመሆን ዘመን አይሽሬ የጥበብ ስራዎችን ሰርታለች፡፡ ይሁንና በዘመነ ቀይ ሽብር የመኢሶን አባል ሆና በመገኘቷ የጥይት እራት ሆነች፡፡ የርሷን ሞት ተከትሎ የተነዛው የአንድ ወገን ወሬም የጥበብ ስራዋን ሸፈነው፡፡ ይህ ትውልድ ግን ለጥበብ ውሎዋ ተገቢውን እውቅና የመስጠት ሀገራዊ ግዴታ አለበት፡፡ ስራዋን ማውሳትና ድንቅ ብዕሯን ማወደስ አለበት፡፡ እንደዚያ ካደረግን የዛሬዎቹ ጠቢባንም ለነገው መዘክራቸው ዋስትና አገኙ ማለት ነው፡፡ ታሪክም ትክክለኛ ሚናውን የሚጫወተው ያኔ ነው፡፡ 
------

አሁን አበቃሁ፡፡ ከላይ በመግቢያዬ ስለዚያ ነገር (“ፈስ”) ሳወራ አብሽቄአችሁ ከሆነ በይቅርታ እለፉኝ፡፡ ግን እኮ አጨራረሴ ጥሩ ነው! አይደለም እንዴ? ጥሩ ነው ካላችሁ ይሁን! ጥሩ ካልሆነም ለወደፊቱ እናሻሽላለን፡፡

 ለማንኛውም በወዳጅነታችን እንሰንብት!  
 አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 22/2005

Sunday, August 25, 2013

“የሸዋሉል መንግሥቱ” እና የጥላሁን ገሠሠ “Akkam Nagumaa”




ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----------
   አሁንም ወደ ዘፈን ልወስዳችሁ ነው፡፡ ስለወጋየው ደግነቱ “አርኬ ሁማ” ሳወጋችሁ እንደተናገርኩት በአንድ ዘመን በኢትዮጵያ ደራሲያን ሲጻፉ የነበሩት ዘፈኖች “ዘፈን” ተብለው ብቻ የሚታለፉ አይደለም፡፡ አንዳንዶቹ በመልዕክታቸው ሀያልነት፤ ከፊሎቹ ደግሞ በዜማና ግጥማቸው ህብርነትና የረቀቀ መስተጋብር ዘመን አይሽሬ የሚባሉ ዓይነት ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ በሁለተኛው ዘርፍ ከሚመደቡት ዘመን አይሽሬ ዘፈኖች መካከል አንዱን አስቃኛችኋለሁ፡፡
   ዘፈኑ “አከም ነጉማ” ይሰኛል፡፡ ታዲያ ይህንን ዘፈን “ዘፈን” በመሆኑ ብቻ ልዳስሰው የተነሳሁ እንዳይመስላችሁ፡፡ ከጀርባው ያለውን አስገራሚ ታሪክ ላካፍላችሁ በመሻቴ ነው ለቅኝቴ የመረጥኩት (እንጂ እኔ በበኩሌ በአሁኑ ጊዜ ለዘፈን ብዙም “ሀጃ” የለኝም)፡፡
  *****  *****  *****
   የዘፈኑ ርዕስ “Akkam Nagumaa” ነው-ከላይ እንደገለጽኩት፡፡ በኦሮምኛ “እንዴት ነሽ ሰላም ነሽ” እንደማለት ነው፡፡ ዘፋኙ አንጋፋው ኮከብ ጥላሁን ገሠሠ ነው፡፡ በኔ የዕድሜ ክልል ውስጥ ያላችሁ ሰዎች  (ከ30 ዓመት በላይ የሆናችሁ) ዘፈኑን በደንብ እንደምታስታውሱት ይታወቀኛል፡፡ ከኔ የምታንሱትም ብትሆኑ ጥላሁን በ1987 በለቀቀው አልበም ውስጥ በድጋሚ በዘፈነው ጊዜ እንደ አዲስ አጣጥማችሁታል (ለዘፈን ባይተዋር ካልሆናችሁ በቀር)፡፡
   “አከም ነጉማ” የፍቅር ዘፈን ነው፡፡ ጥላሁን ከአጠገቡ የተለየችውን አፍቃሪውን ነው “እንዴት ነሽ? ነሽ አማን ነሽ?” እያለ የሩቅ ሰላምታ የሚያቀርብላት፡፡ በዘፈኑ ውስጥ በናፍቆት ብስልስል ብሎ እንደተቃጠለላት ያወሳል፡፡ “እንቅልፍ አጥቻለሁ ቶሎ ነይልኝ” እያለም ይለማምናታል፡፡ እስቲ የዘፈኑን ግጥም ከአማርኛ ትርጓሜው ጋር ልጋብዛችሁ (ቃል በቃል ለመፍታት ቢከብድም እንደሚሆን አድርጌ ጽፌዋለሁ)፡፡
------
አዝማቹ
Akkam nagumaa Fayyuumaa (እንዴት? ነሽ አማን ነሽ? ደህና ነሽልኝ?)
Hiriyaa hinqabuu kophumaa (ሌላ ጓደኛ የለኝም እኔ ብቻዬን ነኝ)
Dhuftee na laaltus gaarumaa (እጅግ መልካም ነበር መጥተሸ ብታይኝ)
Akkam nagumaa fayyumaa (እንዴት? ነሽ አማን ነሽ? ደህና ነሽልኝ?)
----------
Eessattin si arga garamin harkisaa (የት ነው የማገኝሽ ወዴትስ ልጓዘው?)
Mee nama naaf dhaami bakki jirtu eessa (እስቲ ሰው ላኪብኝ ቦታሽን ልወቀው)  
Yaa damme yaa dammee yaa dammee bulbulaa (የኔ ማር የኔ ማር የኔ ወለላ ማር )
Ani hirriiba dhabe suman yaadaa bulaa (እንቅልፍ አጥቻለሁ ካንቺ ሓሳብ በቀር የለኝም አዳር)
---------
Namni na ilaalee karaa na ceesisaa (ሰዎች ያዩኝና መንገድ ያሻግሩኛል)
Gidiraan jaalalaa sihi na feesisaa (የፍቅር ውቃቢው አንቺን ያሰኘኛል)
Garaan nurakinnaan sabbataan hidhannee (ሆድ ቢያስቸግር እንኳ በመቀነት ያስሩታል)
Ijaa ammo akkam goona tan ilaaltee hin obsine (አይታ የማትታገሰውን ዐይን በምን ያባብሏታል?)
--------
Bakka ati jirtu qalbiin koo na yaadee (ያለሽበትን ቦታ በልቤ እያሰብኩት)
Numan ciisa malee hirriibni na dide (ተጋደምኩት እንጂ ምኑን ነው የተኛሁት) 
Nagaatti, nagaatti nagaatti jiraadhu (በሰላም በአማን በደህና ኑሪልኝ)
Guyyaa tokko dhufee hamman sidhungadhuu (አንድ ቀን መጥቼ ስሜሽ እስኪወጣልኝ)
------
ዘፈኑን ከነዜማው መስማት የሚፈልግ ካለ ይህንን የዩቲዩብ ሊንክ ይከተል፡፡
http://www.youtube.com/watch?v=QNfu_1TEQXk
------
  ይህ “አከም ነጉማ” የተሰኘው ዘፈን “የጠላሽ ይጠላ ብድሩ ይድረሰው” በሚለው የጥላሁን አልበም ላይ ነው የሚገኘው፡፡ በካሴት የታተመበት ጊዜ በ1973/1974 ይመስለኛል፡፡ ዘፈኑ በተለቀቀበት ጊዜ በሙዚቃ ያጀበውን ባንድ የማህሙድ አህመድን “እንቺ ልቤ እኮ ነው-ስንቅሽ ይሁን ያዥው” ያጀበው ባንድ እንደሆነ በትክክል ያስታውቃል፡፡ በመሆኑም ባንዱ በዘመኑ ገናና የነበረው አይቤክስ ባንድ ነው ማለት ነው፡፡ ዘፈኑ በ1973/74 ቢለቀቅም እስከ ሰማኒያዎቹ መግቢያ ድረስ ይሰማ ነበር፡፡ እኔም እርሱን በደንብ ለመስማት የታደልኩት በዚሁ ምክንያት ነው፡፡

 “አከም ነጉማ”ን በፊት ሳውቀው እንደ ማንም ተራ ዘፈን ነበር የምመለከተው፡፡ ክቡር ዶ/ር ጥላሁን ገሠሠ ባረፈበት ዕለት የአሜሪካ ድምፅ ሬድዮ የኦሮምኛ ፕሮግራም ለቃለ-ምልልስ የጋበዘው አርቲስት ዶ/ር ዓሊ ቢራ “ከጥላሁን ዜማዎች መካከል የትኛውን ታስበልጣለህ?” የሚል ጥያቄ ቀርቦለት “አከም ነጉማ” የሚል ምላሽ ከሰጠ በኋላ ግን በስስት ዐይን አየው ጀመር፡፡ ይሁንና ዘፈኑን ጠለቅ ብዬ የመመርመርና እንደ ቅርስ የማየት አባዜ የመጣብኝ ባለፈው የመስከረም ወር ነው፡፡
    
   በወቅቱ (መስከረም/2005) ዩቲዩብ በሚባለው ዝነኛ የኢንተርኔት ቻናል ቆየት ያሉ ቪዲዮዎችን እበረብር ነበር፡፡ በተለይ በዚያ ወር የኮሎኔል መንግሥቱን መጽሐፍ አንብቤ ስለነበረ የሳቸውን ንግግሮች የያዙ ቪዲዮዎችን ዳውንሎድ ለማድረግ ከፍተኛ ፍተሻ አደርግ ነበር፡፡ ታዲያ በመንጌ ቪዲዮዎች መካከል በተሸጎጠ አንድ ፋይል ላይ “Tilahun Gessesse’s Akkam Neguma” የሚል ርዕስ በማየቴ ተደነቅኩና ከፈትኩት፡፡ ዘፈኑን ከመስማቴ በፊት ግን ስለዘፈኑ በተጻፈ መጠነኛ ማብራሪያ ውስጥ “Written by Yeshewalul Mengistu”  የሚል ሐረግ ታየኝና አድናቆቴ ይበልጥ ጨመረ፡፡ እስከዚያን ጊዜ ድረስ ይህንን መረጃ ባለማወቄም በእጅጉ አዘንኩ፡፡
  *****  *****  *****
   ይገርማል! ታሪካችን ይገርማል! የታሪክ አጻጻፋችንም ይገርማል፡፡ የምንጠላውን ሰው የሰይጣን ቁራጭ እያደረግን የአጋንንት መልክና የጋንጩር ቁመና እንሰጠዋለን፡፡ የምንወደውንም ሰው የመንግሥተ ሰማያት ሙሽራ እናስመስለውና ከመላእክት ተርታ እናሰልፈዋለን፡፡ በዚህ መሀል መታወቅ የነበረበት ሐቅ ይደበቅና አድናቆትና ጥላቻ የታሪክ አጸቆች ሆነው ቁጭ ይላሉ፡፡ ይሁንና ዛሬ የተደበቀው ሐቅ ትክክለኛ ጊዜውን ጠብቆ አንገቱን ቀና ያደርጋል፡፡ ያኔ ተረትን በታሪክ ቦታ ያነገሡ የጥላቻ ደቀ-መዛሙርት አንገታቸውን ይደፋሉ፡፡ እውነት ኮራ ብላ መራመድ ትጀምራለች፡፡፡፡

   “አከም ነጉማ”ን በውብ ብዕሩ ከሽኖ ለሀገር ቅርስነት ያበቃው ደራሲም የነዚህ የጥላቻ ደቀ-መዛሙርት የጥቃት ሰለባ ሆኖ ታሪኩ ሲበላሽበት ኖሯል፡፡ ሀገርና ትውልድ ሲያጠፋ እንጂ ለሀገር አንዳች ጠቃሚ ነገር ጠብ እንዳላደረገ ሲጻፍበት ሰንብቷል፡፡ ሆኖም በአንድ ወቅት የተነሳው የጥላቻ አቧራ ብንን ብሎ ሲጠፋለት ደራሲው እጅግ መልካም የሆኑ ቁምነገሮች እንደነበሩት ታሪክ ይመሰክርለት ይዟል፡፡ የዚያ ደራሲ ስም የሸዋሉል መንግሥቱ ይባላል፡፡ ደራሲውን በወንዴ ጾታ ስጠራው ግን ወንድ እንዳይመስላችሁ፡፡ “ሴት” ናት፡፡ 

 “የሸዋሉል መንግሥቱ” የሚለውን ስም ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት “አጥፍቶ መጥፋት” በሚለው የሙሉጌታ ሉሌ ድርሰት ውስጥ ይመስለኛል፡፡ በማስከተልም በባቢሌ ቶላ “የትውልድ እልቂት”፣ በክፍሉ ታደሰ “ያ ትውልድ” እና በሌሎችም ኢህአፓ-ቀመስ ድርሰቶች.. ውስጥ ስሙን አይቼዋለሁ፡፡ በዚህ ስም የምትጠራው ሴት በየመጻሕፍቱ ውስጥ ጨካኝ፣ አረመኔ፣ ገዳይ፣ ገራፊ፣ ዘራፊ፣ ለወጣት የማትራራ ወዘተ… በሚሉ ቃላት ተገልጻለች፡፡ በተለይ አንደኛው መጽሐፍ “እንደ ወንድ የታጠቀ ስኳድ እየመራች ከየቤቱ ወጣቶችን እያደነች የምትገድልና የምትገርፍ የሴት አረመኔ” ብሎ እንደገለጻት እስከ አሁን ድረስ ይታወሰኛል (በዚያ ዘመን ካለርሷ በስተቀር እንዲያ አይነት ጭካኔ የፈጸመች ሴት አልነበረችም ለማለት ይመስላል)፡፡

  የሸዋሉል የኖረችው በዘመነ ቀይ ሽብር ነው-ከአያያዜ እንደምትረዱት፡፡ ይህቺ ሴት በ1969/1970 በኢህአፓ ገዳይ ስኳዶች “ሰባራ ባቡር” በሚባለው ሰፈር ከነበረው ቤቷ በራፍ ላይ ተገድላለች፡፡ ኢህአፓዎች የግድያዋን ምክንያት ሲያስረዱ “በንጹሐን ደም እጇን ያጨቀየች ቀንደኛ የመኢሶን ገራፊ እና የገዳይ ጓድ መሪ ነበረች” ነው የሚሉት፡፡ ሴትዮዋ የኢትዮጵያ ሬድዮ ጋዜጠኛ እና የፕሮግራም መሪ ሆና ሳለ እንዲያ ዓይነት ወራዳ ተግባር ውስጥ የገባችበትን ምክንያት በትክክል መረዳት ቢከብደኝም በኢህአፓ አባላትና ደጋፊዎች የተጻፈውን ገለጻ የማስተባብልበት መንገድ ስላልነበረኝ “ታሪኩ እውነት ነው” በማለት ተቀብየው ኖሬአለሁ፡፡ ስለርሷ በጎውን የሚናገሩ ጽሁፎችንና ቃለ ምልልሶችን አልፎ አልፎ ባነብም ሙያዋንና ችሎታዋን በዝርዝር ያስረዳኝ ሰው ስላልነበር በጨካኝነቷና በገራፊነቷ መዝግቤአት ቆይቻለሁ፡፡ “የአከም ነጉማ” ደራሲ እርሷ መሆኗን ከተረዳሁበት ዕለት ጀምሮ ግን አቋሜን ሙሉ በሙሉ ለመቀየር ተገድጃለሁ፡፡
 
  አዎን! የሸዋሉል ከዕድሜዋ በፊት የተቀጨች ባለ ልዩ ችሎታ እመቤት ነበረች፡፡ ከጥላሁን “አከም ነጉማ” ሌላ በርካታ የኦሮምኛ እና የአማርኛ ዘፈኖች ግጥምና ዜማ ደራሲ ናት፡፡ ለምሳሌም በቅርብ ጊዜ ካገኘሁት መረጃ እንደተረዳሁት “ወይ ዮቢ ዮቢ ሐደሶ ሊባነታ” የሚለውን የዓሊ ቢራ ዘፈን የደረሰችው እርሷ ናት፡፡ የሸዋሉል በጋዜጠኝነቱም ቢሆን ወደር አልነበራትም፡፡ አድናቂዋ እና የሙያ ባለደረባዋ የነበረው አንጋፋው ደራሲና ጋዜጠኛ አበራ ለማ ኢትኦጵ ከሚባል መጽሔት ጋር ባደረገው ቃለ-ምልልስ “ትንታግ” በሚል ቃል ገልጾአት እንደነበር ይታወሰኛል (በወቅቱ የርሱ ቃለ ምልልስ ዘርዘር ያለ ስላልነበር ስለርሷ በጎውን እንዳስብ ሊያነሳሳኝ አልቻለም እንጂ)፡፡  ነገር ግን የዚያ ዘመን የደም ትርኢት ይህችን የመሰለች ውብ የኪነት እመቤት ምንጭቅ አደርጎ በላት፡፡ ሚስኪን!
    
   ስለሸዋሉል እውነተኛ ታሪክ ለመመርመር ጉዞ ጀምሬአለሁ፡፡ በተለይ በርሷ ስራዎች ዙሪያ አንድ መጣጥፍ የማጠናቀር ሃሳብ አለኝ፡፡ ሴትዮዋ ኢህአፓዎች እንደሚሉት ገራፊ እና ገዳይ ከሆነች እርሱንም ለወደፊቱ ላስነብባችሁ ቃል እገባለሁ፡፡ ይሁንና ይህ አስቀያሚ ታሪኳ (በእውነትም እንደዚያ አይነት ታሪክ ካላት) መልካም ታሪኳን በምንም መልኩ ሊያስቀረው እንደማይችል መታወቅ አለበት፡፡ ስለርሷ ገራፊነት ስትነግሩን የኖራችሁ ወገኖችም የሸዋሉል “አከም ነጉማ”ን የጻፈችበት ውብ ብዕርና ምትሃታዊውን ዜማ ያፈለቀችበት ውብ አዕምሮ እንደነበራት ልታወጉን ወኔው ይኑራችሁ፡፡ እንዲያ ካልሆነ እውነት ለመናገራችሁ አናምናችሁም፡፡
   
   እኔ ጸሓፊው ከሁለቱም ወገን አይደለሁም፡፡ የኢህአፓም ሆነ የመኢሶን አድናቂ አይደለሁም፡፡ በመሆኑም የኢህአፓዋን ወይዘሮ ዳሮ ነጋሽን “ነፍሰ ጡሯ ሰማዕት” እያልኩ የማሞግስበትና የመኢሶኗን የሸዋሉል መንግሥቱን “ዮዲት ጉዲት ናት” ብዬ የምራገምበት ምክንያት የለም፡፡ ለኔ ቀይ ሽብርም ሆነ ነጭ ሽብር ውጉዝ የሆነ የታሪክ እዳ ነው፡፡ ያንን እዳ ማወራረድ ያለበት ግን ያኛው ትውልድ ራሱ እንጂ ይህኛው ትውልድ አይደለም፡፡ ከያኔው ጥላቻ ጋር የሰዎችን ስብዕና እያጎደፉ መበከል በዚህ ትውልድ መቀጠል የለበትም፡፡ ውቢቷ የብዕር ገበሬና ጠንካራ ጋዜጠኛ የነበረችው የሸዋሉል መንግሥቱም በታሪክ ተገቢ ስፋራዋ ሊሰጣት ይገባል፡፡
  
 “አከም ነጉማ ፈዩማ
   ሂሪያ ሂንቀቡ ኮጱማ
   ዱፍቴ ነላልቱስ ጋሩማ
   አከም ነጉማ ፈዩማ”
   ------
ሰላም ሁኑልኝ
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 19/2005