Saturday, January 27, 2018

“ቡኻራ” እና “ቡኻሪ”


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
------
“ቡኻራ” በዛሬው ዘመን “ኡዝቤኪስታን” በሚባለው ሀገር የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ ይህቺ ከተማ በጥንታዊነታቸው ከሚጠቀሱት የዓለማችን ከተሞችም ትመደባለች፡፡ ከተማዋ ጥንታዊት በመሆኗም ብዙዎችን አፍርታለች፡፡ ታዲያ በእቅፏ ተወልደው ካደጉት ሰዎች ሁሉ ስማቸው በጣም ገንኖ የሚታይ አንድ ሰው አለ፡፡


  የዚህ ሰው የልደት ስም ሙሐመድ ኢብን ዒስማኢል ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ የሚታወቀው ግን “ቡኻሪ” ወይንም አል-ቡኻሪ በተሰኘው ስም ነው፡፡ የሁለቱም ፍቺ የቡኻራው ሰውዬ እንደማለት ነው፡፡ በዚህ አጭር ጽሑፍ “የቡኻራው ሰውዬ” የሚታወቅበትን ዋነኛ ስራ እና የቡኻራን ተጠቃሽ ገጽታዎች በጥቂቱ እንቃኛለን፡፡
-----
አል-ቡኻሪ በርግጥም በኡዝቤኪስታኗ የቡኻራ ከተማ ነው የተወለዱት፡፡ ትምህርታቸውን አሐዱ ብለው መማር የጀመሩትም በዚህችው የልደት ቀዬአቸው ነው፡፡ በጉርስምና ዘመናቸው ግን የዕውቀት ጥማታቸው በጣም ጨመረ፡፡ በመሆኑም በዘመኑ የነበሩትን የዒልም መዲናዎች ማሰስ ጀመሩ፡፡ ወደ ኒሻፑር፣ መካ፣ መዲና፣ አል-ፉስጣጥ (ግብጽ) ጠብሪዝ፣ በስራ፣ ኩፋ፣ በግዳድ፣ ደማስቆ፣ ወዘተ እየሄዱ እንደ አሕመድ ኢብን ሀንበልን በመሳሰሉት ስመ-ገና ሊቃውንት ስር እውቀትን ተመገቡ፡፡
  አል-ቡኻሪ በትምህርታቸው ላይ እያሉ የነቢዩን (ሰዐወ) ሐዲሶች በአንድ መጽሐፍ የማጠናቀር ጉጉት አደረባቸው፡፡ በዚህም መሠረት ከካይሮ እስከ ሜርቭ (ቱርክሜኒስታን) ድረስ እየሄዱ በሰው አንደበት የሚነገሩትን ሐዲሶች መሰብሰብ ጀመሩ፡፡ ከአስራ ስድስት ዓመታት አድካሚ ጥረት በኋላም በነቢዩ (ሰዐወ) ስም የሚነገሩ 600,000 ሐዲሶችን ሰበሰቡ፡፡
  “አል-ቡኻሪ” ከዚያ ለጥቆም የተለያዩ መመዘኛዎችን በማስቀመጥ የሰበሰቧቸውን ሐዲሶች እውነተኛነት በጥልቀት ፈተሹ፡፡ ከሰበሰቧቸው ሐዲሶች መካከል አብዛኞቹ ከአጠራጣሪ ምንጮች የተገኙ መሆናቸውን ተረዱ፡፡ 7275 የሚሆኑት ግን መቶ በመቶ አስተማማኝ (ሰሐሕ) እንደሆኑ ደመደሙ፡፡ በዚህ መደምደሚያ መሠረትም የማይሻር ክብርና ሞገስ ያስገኘላቸውን ጃሚዑል ሰሒሕ (በብዙዎች ዘንድ በሚታወቅበት ስሙ ሰሒሕ አል-ቡኻሪ) የተሰኘ ዝነኛ የሐዲስ መጽሐፍ አጠናቀሩ፡፡ ለዚህ ድካማቸው ከሙስሊም ዓለም “ኢማም” የተሰኘውን ማዕረግ አገኙ፡፡
  አዎን! ኢማም ቡኻሪ የአላህ ፈቃድ ሆኖ ለኛ ያበረከቱት ትልቁ ገጸ-በረከት “ሰሒሕ አል-ቡኻሪ” ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ በእስልምና ሊቃውንት ዘንድ ከሐዲስ መጻሕፍት ሁሉ የመጀመሪያ ደረጃ ተሰጥቶታል፡፡ በእስልምና ደንብ ከቅዱስ ቁርኣን በማስከተል ዋነኛ የስነ-መለኮትና የሸሪዓ ህግጋት ምንጭ ተደርጎ የሚወሰደው እርሱ ነው፡፡
  በኢማም ቡኻሪ የተጠናቀረው “ሰሒሕ አል-ቡኻሪ” ተደናቂ የሆነበት አንደኛው ምክንያት “ቡኻሪ” ሐዲሶቹን ያገኙባቸውን ሰዎችና ሐዲሱ ከነቢዩ (ሰዐወ) ሲወርድ ሲዋረድ የመጣበትን ሐረግ (በዐረብኛ ስሙ “ሰነድ”) በተመለከተ የተሟላ መረጃ የያዘውን “ታሪኽ አል-ከቢር” የተሰኘ መጻፍ ለማጠናቀር መቻላቸው ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ በቅድሚያ እያንዳንዱ ሰሒሕ ሐዲስ በነቢዩ (ሰዐወ) አንደበት የተነገረበትን ቦታና ጊዜ፣ እንዲሁም ሐዲሱ ከሰሐባ ትውልድ በኋላ በተከታታይ በመጡ ትውልዶች እየተወራረሰ እስከ ቡኻሪ ዘመን የደረሰበትን “የዘገባ ሐረግ” (Chain of Transmission) ያሳያል፡፡ በማስከተል ደግሞ በእያንዳንዱ የዘገባ ሐረግ ውስጥ የተጠቀሱት ሰዎች የልደት ቦታ፣ ጎሳ፣ የዕውቀት ደረጃ፣ የኢማን ሁኔታ፣ ስለእስልምና የነበረው አመለካከት፣ የጤና ሁኔታ፣ ሰውዬው በማኅበረሰቡ ዘንድ የነበረው ተኣማኒነት ወዘተ… በዝርዝር ተመዘግቧል፡፡
  ኢማም ቡኻሪ አንድን ሐዲስ “ሰሒሕ” (authentic) በማለት የሚመዘግቡት በዘገባው ሐረግ ውስጥ የተጠቀሱት ግለሰቦች በሁሉም መለኪያዎች “positive” የሚል ምስክርነት ካገኙ ብቻ ነው፡፡ ለምሳሌ አንዱን ሐዲስ ያስተላለፈ ሰው እብለት ያልታየበት (የማይዋሽ) መሆኑ ተረጋግጦ ሳለ ሰውዬው የአዕምሮ ጤና እንዳልነበረው የሚጠቅስ መረጃ ከተገኘበት ቡኻሪ ሐዲሱን ውድቅ ያደረጉት ነበር፡፡
   በሌላ በኩል ደግሞ በአንዱ የዘገባ ሐረግ (ሰነድ) ውስጥ የተጠቀሰው ሰው በጣም ጃጅቶ የሚናገረውን መለየትና ሰገራውን መቆጣጠር ባልቻለበት ዕድሜው ሐዲሱን አውርቶት ከሆነም ሐዲሱ በቡኻሪ መመዘኛ ውድቅ ይደረግ ነበር፡፡ ሰውዬው ሐዲሱን ያወራበት የተለየ የፖለቲካ ተልዕኮ ያለው መሆኑ ከታወቀም ቡኻሪ ለሐዲሱ “ሰሒሕ” የሚለውን ደረጃ ይነፍጉታል (ለምሳሌ “የፖለቲካ ስልጣን በዓሊና በፋጢማ ዝሪያዎች ብቻ መያዝ አለበት” የሚሉት በርካታ የሺዓ ሐዲሶች በቡኻሪ መጽሐፍ ላይ ያልተመዘገቡት ሐዲሶቹ ፖለቲካዊ ግብ ባላቸው ሰዎች የተወሩ ፈጠራዎች መሆናቸው ስለታወቀ ነው)፡፡ ከእንደዚህ ዓይነት ጉድለቶች በጠሩ ሰዎች አንደበት የተላለፉ ሐዲስ ብቻ ናቸው በቡኻሪ መጽሐፍ ውስጥ “ሰሒሕ” ተብለው የተመዘገቡት፡፡
---
ከላይ እንደገለጽኩት “ሰሒሕ አል-ቡኻሪ” ከቅዱስ ቁርኣን ቀጥሎ ሁለተኛው የእስልምና ህግጋት ምንጭ ነው፡፡ ይሁን እንጂ መጽሐፉ በይዘቱ ሸሪዓዊ ብቻ አይደለም፡፡ የነቢዩ ሙሐመድን (ሰዐወ) እና የቀደምት ባልደቦቻቸውን የህይወት ታሪክ በተመለከተም ዋነኛ የሰነድ ምንጭ ሆኖ ያገለግላል፡፡ እስልምና በቀዳሚዎቹ ዓመታት የተተገበረበትን አኳኋን መረዳት በሚፈልጉ ተመራማሪዎች ዘንድም የመጀመሪያ ደረጃ የታሪክ ምንጭ ሆኖ ይወሰዳል፡፡
   ኢማም ቡኻሪ ከጃሚዑ-ሰሒሕ (ሰሒሕ አል-ቡኻሪ) በተጨማሪ በርካታ መጻሕፍትን ጽፈዋል፡፡ የበርካታ ታላላቅ ዑለማ አስተማሪም ነበሩ፡፡ ከተማሪዎቻቸው መካከልም አንዱ ሰሒሕ ሙስሊም የተሰኘውን ታዋቂ የሐዲስ መጽሐፍ ያጠናቀሩት ሙስሊም ኢብን ሐጃጅ ናቸው፡፡ አል-ቡኻሪ በመጨረሻ የህይወት ዘመናቸው ወደ ተወለዱባት የቡኻራ ከተማ ተመልሰው መኖር ጀመሩ፡፡ ይሁንና በዘመኑ ከነበረው የቡኻራ ገዥ ጋር ስላልተስማሙ ኸርታንክ ወደተባለች ከተማ ሄዱ፡፡ እዚያ ጥቂት ከኖሩ በኋላም በስልሳ ዓመታቸው አረፉ፡፡ አላሕ ይርሐማቸው፡፡ መልካም ስራቸውን ይቀበላቸው፡፡
---
አል-ቡኻሪን ያፈራችው ቡኻራ በመካከለኛው እስያ ቀደምት ከሆኑት ሁለት ከተሞች አንዷ ናት (ሌላኛዋ ሰመርቀንድ ናት)፡፡ በዓለም ታሪክ ውስጥ የሐር መንገድ (Silk Road) እየተባለ የሚጠራው የንግድ መስመር ከሚያቋርጣቸው ዋና ዋና ከተሞች መካከልም አንዷ ነበረች፡፡ ከክርስቶስ ልደት በኋላ 709 የኡመያድ ኸሊፋዎች ግዛት አካል ስትሆን ነዋሪዎቿ እስልምናን ተቀብለዋል፡፡
  ቡኻራ ለረጅም ዘመናት የእስልምና የትምህርትና የባህል ማዕከል በመሆን ነው የምትታወቀው፡፡ በዚህ ረጅም ዘመኗ የተገነቡላት በርካታ መስጊዶችና መድረሳዎች አሏት፡፡ ከነርሱም መካከል አንዳንዶቹ በኸሊፋ ሐሩን አል-ረሺድ ዘመን የተሰሩ ናቸው፡፡ ይህም ከዛሬ አንድ ሺህ ሁለት መቶ ዓመታት በፊት ማለት ነው፡፡ በነዚህ ጥንታዊ ግንባታዎች ላይ የሚታየው ውበት በመካከለኛው ዘመን የነበረውን እስላማዊ የኪነ-ህንጻ ጥበብን (Islamic Architecture) ይወክላል፡፡ እነዚህ ቅርሶች በደንብ መጠበቅ ያለባቸው መሆኑን ለማስገንዘብ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (UNESCO) ቅርሶቹ የሚገኙበትን የቡኻራ ከተማን ጥንታዊ ክፍል (Old Quarter) በዓለም ቅርስነት መዝግቦታል፡፡
----
አፈንዲ ሙተቂ
መጀመሪያ ህዳር 2/2007 በገለምሶ ከተማ ተጻፈ፡፡
እንደገና ተሻሽሎ ጥር 19/2010 በሸገር ተጻፈ፡፡


No comments:

Post a Comment