Thursday, January 11, 2018

ከ“ሁለት ዶክተሮች ወግ” ጀርባ ያለ እውነታ


(አፈንዲ ሙተቂ)
-----
   መካከለኛው ምስራቅን የሚያምሰው የፍልስጥኤም-እስራኤል ችግር ረጅም ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ የዚህ ችግር መነሻ በ1948 የተመሠረተችው እስራኤል አንድ ዓመት እንኳ ሳይሞላት ፍልስጥኤማዊያን የወደፊት ሀገራቸውን እንዲመሠርቱበት የተመደበላቸውን ግዛት መውረሯ ነው፡፡ የእስራኤል ጎረቤት የሆኑ የዐረብ ሀገራት እርምጃውን በመቃወም ሶስት ጊዜ ጦርነት ያወጁባት ቢሆንም እስራኤል በሶስቱም ድል አድርጋለች፡፡

   ታዲያ እስራኤል የድሉን ብስራት ያከበረችው በወታደራዊ ሰልፍና በርችት ሳይሆን ፍልስጥኤምን ሙሉ በሙሉ ወደ ግዛቷ በማካተት ነው፡፡ የሀገሩ ባለቤት ከሆኑት ፍልስጥኤማዊያን ደግሞ ከፊሉን እየገደለች አብዛኛውን ከመሬቱ አባርራለች፡፡ ዛሬ በሀገራቸው ላይ የቀሩት ፍልስጥኤማዊያን ከመላው የፍልስጥኤም ህዝብ ሃያ በመቶ ያህል ብቻ ናቸው፡፡

    አብዛኛው የዓለም ህዝብ የእስራኤልን ወረራ አውግዞአል፡፡ እስራኤልም  ፍልስጥኤምን ለቃ እንድትወጣ በተደጋጋሚ ጊዜያት ውሳኔ ተላልፎባታል፡፡ ሀገራችንም ባለፉት አርባ ዓመታት ይህንን አቋም በማራመድ ላይ ትገኛለች፡፡

    “ታዲያ ለመገናኛ ብዙኃን፣ ለቢሮክራሲውና ለትምህርቱ ዓለም ቅርብ የሆነው የሀገራችን ማኅበረሰብ የፍልስጥኤማዊያንን ትግል የሚመለከተው በአንድ ወጥ ሁኔታ አይደለም፡፡ ይህም ከፍተኛ የሆነ ግራ መጋባትን ፈጥሮአል፡፡
    በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን መንግሥት እና ለገዥው መደብ የቀረቡ ኃይሎች  የእስራኤል ደጋፊ የነበሩ ሲሆን የተማረው ክፍል (ኢንተሌጀንሲያው) ደግሞ በአብዛኛው የፍልስጥኤሞችን ትግል ይደግፍ ነበር፡፡ በደርግ ዘመን ደግሞ የሀገራችን መንግሥት የፍልስጥኤማዊያን ትግል ደጋፊ ከመሆኑም በላይ በስደት ለተቋቋመው የፍልስጥኤማዊያን መንግሥት በኦፊሴል እውቅና በመስጠት ኤምባሲውን በአዲስ አበባ እንዲከፍት ፈቅዶለታል፡፡ የኢንተሌጀንሲያው ክፍልም በአመዛኙ የፍልስጥኤምን ትግል ይደግፍ ነበር፡፡
  
“ከደርግ ውድቀት በኋላ ግን ነገሩ ሁሉ ተገለባብጦ ማኅበረሰባችን በሃይማኖት እየተከፋፈለ ለፍልስጥኤም-እስራኤል ግጭት ድጋፉን የሚያሳይበት/ተቃውሞውን የሚገልጽበት አካሄድ ተከስቷል፡፡ በዚህም መሠረት “ሀማስ እስራኤል ላይ ሮኬት ተኮሰ” ወይንም “እስራኤል የጋዛ ከተማን በአውሮፕላን ደበደበች” የሚል ዜና የተላለፈ እንደሆነ ክርስቲያን የሆኑ የሚዲያ ተከታታዮች በአብዛኛው የእስራኤል ደጋፊ ሆነው ይሰለፋሉ፡፡ እስራኤል የክርስቲያን ሀገር ሆና ከሙስሊሞች ጋር ጦርነት የገጠመችም ይመስላቸዋል፡፡ ሙስሊሞቹ ደግሞ በተቃራኒው የፍልስጥኤም ደጋፊ ይሆናሉ፡፡ ፍልስጥኤማዊያን ክርስቲያኖች የሌሉና ትግሉ ሁሉ በሙስሊሞች ብቻ የሚካሄድ ይመስላቸዋል፡፡

   እንዲህ ዓይነት አሰላለፍ የተከሰተው የእስራኤል ፕሮፓጋንዲስቶች ለረጅም ዓመታት ግጭቱ የሃይማኖት ጦርነት እንደሆነ በማስመሰል ሲያናፍሱት በነበረው በውዥንብር የተሞላ ትርክት የተነሳ ነው፡፡ ይህ አሰላለፍ በውጪው ዓለም አልፎ አልፎ ነው የሚታየው፡፡ በሀገራችን ውስጥም ቢሆን በቀድሞ ዘመናት እንዲህ ዓይነት አረዳድ አልነበረም”

    የዐፄ ኃይለሥላሴ መንግሥት የእስራኤል ደጋፊ የሆነው ከጂኦ-ፖለቲካዊ ሁኔታዎች በመነሳት ነው፡፡ ለምሳሌ የዐጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት የግብፁ መሪ ጀማል ዐብዱናስር የሚያካሄዱት “የፓን ዐረቢዝም ንቅናቄ” ስላሰጋው የእንቅስቃሴው ዋነኛ ተቃዋሚ ከነበሩት የኢራን፣ የእስራኤልና የቱርክ መንግስታት ጋር በወዳጅነት ቃል ኪዳን ተሳስሮ ነበር፡፡ በሌላ በኩል የፍልስጥኤም ነፃ አውጪ ድርጅቶች የኤርትራ ንቅናቄዎችን (ጀብሃን እና ሻዕቢያን) በመደገፋቸው የኃይለሥላሴ መንግሥትም በአፀፋው ከእስራኤል ጋር ወግኗል፡፡

   የደርግ መንግሥት ለፍልስጥኤም ትግል አጋርነቱን ለመግለጽ የወሰነበት ዋነኛ ምክንያት የሚከተለው የሶሻሊስት ርእዮተ ዓለም የብሄራዊ አርነት ንቅናቄዎችን እንዲደግፍ የሚያስገድደው መሆኑ ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ የዓለም ሀገራት በፍልስጥኤም ጥያቄ ፍትሐዊነት ላይ የጋራ መግባባት የነበራቸው በመሆኑ የደርግ መንግሥትም ተመሳሳይ አቋም አንፀባርቋል፡፡

   በሌላ በኩል የደርግ መንግሥት በርካታ የዐረብ ሀገራት የኤርትራ ንቅናቄዎች ደጋፊ በመሆናቸው ብቻ ተበሳጭቶ ፍልስጥኤማዊያን ድርጅቶችን አልገፋቸውም፡፡ የፍልስጥኤም ነፃ አውጪ ድርጅት በአፍሪቃ አንድነት ድርጅት የታዛቢነት ወንበር እንዲያገኝም ታግሏል፡፡ እነዚህም ዘወትር ከሚደነቁለት ተግባሮቹ መካከል ይቆጠራሉ (እርግጥ የኩባው ፊደል ካስትሮ እና ደቡብ የመን በዚህ ላይ ሚና እንደነበራቸው ይታመናል)፡፡

   በቅርብ ዘመናት የምናየው የእስራኤል-ፍልስጥኤምን ግጭት በሃይማኖት መስመር የመረዳት አባዜ ግን ድሮ ያልነበረ እና አንዳች የርእዮተ ዓለም፣ የታሪክና የጂኦ-ፖለቲካ ትንተና መሠረት የሌለው የድንቁርና እሳቤ ነው፡፡ ስለዚህ ይህ የኋላቀርነት አስተሳሰብ በአጭሩ መገታት አለበት፡፡ በርግጥም የፍልስጥኤማዊያን ትግል መደገፍ ያለበት ፍትሐዊና ህጋዊ መሠረት ያለው ተጋድሎ  በመሆኑ ብቻ ነው፡፡

   ታዲያ የተጠቀሰው የድንቁርና አመለካከት እይታችንን በእጅጉ የጋረደ መሆኑን የማስረዳት አጋጣሚ ቢኖረኝ ኖሮ እያልኩ ስመኝ ኖሬአለሁ፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለሁም አጋጣሚው ዘንድሮ ተከሰተልኝና ይህንን አነስተኛ ድርሳን በመጻፍ በትንሹም ቢሆን የልቤን ለማድረስ ቻልኩ፡፡

አፈንዲ ሙተቂ
January 2018



1 comment:

  1. MOHEGAN: $1B lottery jackpot goes live in Maryland
    of the winning $14.5 million 안양 출장샵 MOHEGAN Powerball 경주 출장샵 jackpot 천안 출장샵 in Baltimore 아산 출장안마 County 인천광역 출장안마 will be played on Nov.

    ReplyDelete