Tuesday, September 3, 2013

==የእብድ ወሬዎች==




ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----------
ብዙ እብዶች አሉን አይደል? እስቲ ለዛሬ ደግሞ ከእብዶቻችን መንደር ያገኘኋቸውን አስደሳች ወሬዎች በጥቂቱ ጀባ ልበላችሁ::
------
ሼኽ ሙሐመድ ሻንቆ ሀይለኛ ቃሚ ነበር፡፡ ጫት በወስላ (መቶ ኪሎ የሚይዝ ዝርግ ኬሻ) ቢቀርብለት እንኳ እጨርሰዋለሁ ባይ ነበር፡፡ አንድ ቀን ሐዘን ቤት ሳለን ሼኽ ሙሐመድ ሽንቱን በድንኳኑ ውስጥ ለቀቀው፡፡ ሰው ደነገጠና “ሼኸ መሀመድ ምን ሆንክ” ቢለው
 
 “ሰዓት የለንም እኮ፤ አንዱ ሰዓት የሰለዋት ነው፤ አንዱ የመቃሚያ ነው፤ ታዲያ ጊዜ ከየት አግኝተን ነው ውጪ ወጥተን የምንጸዳዳው?”
------
“ሹቡሹብ” በጣም ቀብራራ ነው፡፡ የሰውነቱ ንጽህናና የልብሱ ጽዳት ሌላ ነው፡፡ አይኑን እንደ ሴት ይኳላል፡፡ በእጁ በርከት ያሉ አበባዎች፣ ቄጤማ፣ ጠጅ ሳር፣ ልዩ ልዩ ባለመዓዛ ቅጠሎች ወዘተ… ይዞ ነው የሚዞረው፡፡ በዚህም የተነሳ አዲስ ሰው እብድ መሆኑን ለማወቅ ይቸግረዋል፡፡

ታዲያ “ሹቡሹብ” ጉራው አይጣል ነው፡፡ በተለይ ጉራውን የሚያሳየው ግን ወደ ማክሰኞ ገበያ በሚመጡ ሴቶች ላይ ነው፡፡ አቤት ሲሰድባቸው! ደግነቱ “እናትሽን…ቅብጥርሴ…ጂንኒ ጀቡቲ” የመሳሰሉ መጥፎ ስድቦችን አይደለም የሚሳደበው ፡፡ የሴቲቱን ንጽህናና ስንፍና ነው በሚገባት ቋንቋ የሚነግራት (ሴቲቱን ቢያውቃት ባያውቃት ጉዳዩ አይደለም)፡፡ አንድ ቀን የገዛ አክስቴን እንዲህ ብሎአት እንደነበር አስታውሳለሁ!
Yaa bada ta buusaa sooggida hinqabne nyaattu (ይህች ጨው የሌለው ወጥ የምትበላ)
Yaa bada ta kurumbaa ajaawaa nyaattu  (ይህቺ የገማ ጥቅል ጎመን የምትበላ)
Yaa bada ta faxiiraa killee hinqabne nyaattu (ይህቺ እንቁላል የሌለው ፈጢራ የምትበላ)

 “ሹቡሹብ” ለከተማ ሴቶችና ከገጠር ለሚመጡ ሴቶች የሚወረውራቸው ስድቦች ይለያያሉ፡፡ ለከተማ ሴቶች የሚወረውራቸው ብዙም ሀይለ ቃል የለባቸውም፡፡ ከገጠር በሚመጡት ላይ ግን ይጨክናል፡፡ ለምሳሌ ከገጠር የሚመጡትን በግጥም ዘይቤ እንዲህ ብሎ ይሰድባቸው ነበር፡፡

Hin hinnattu (በሂና አትዋብ)
Hin hallattu (አትነቀስ)
Hin qayyattu (“ቀያ” አታድርግ”፤ እንዲህ ሲል የሀረርጌ ሴቶች  መጥፎ ጠረን እንዳይኖራቸው በልዩ ልዩ መዓዛማ ጭሳጭስ ሰውነታቸውን የሚያጥኑበትን ባህላዊ ድርጊት መግለጹ ነው፡፡ በአማርኛ ምን ይባላል? እስቲ ንገሩን?)
Hin dhiqattu (አትታጠብ)
Hin miiccattu (ልብሶቿን አታጥብ)
Hin kuullattu (አይኗን አትኳል)
Dhadhaa matarra hin kaayyattu (በቅቤ ጸጉሯን አታርስ)

   ሹብሹብ እንዲህ ብሎ ሲሳደብ መላው ገበያተኛ በሳቅና በሆይታ ነው የሚያጅበው፡፡ አዳዲስ ሴቶች ግን የሰውዬው ንጽህና ስለሚያደናግራቸው ፍዝዝ ብለው ነው የሚያዩት፡፡

ሹብሹብ አንድ ጊዜ “አሪፍ” ቢዝነስ ጀምሮ ነበር፡፡ ከምሽቱ ሶስት ሰዓት ገደማ በከተማው ጎዳና ላይ የሚመላለሱ በጎችና ፍየሎችን ይይዛቸውና “Namni Hoolaan irraa bade! Namni re’een irraa bade” (በግ የጠፋው! ፍየል የጠፋው) እያለ ይለፍፋል፡፡ የፍየሎቹ/በጎቹ ባለቤቶች ሲመጡ “Afaan waraabeessa fidi” ይላቸዋል፡፡ “ከጅብ ያስተረፍኩበትን ዋጋ አምጣ” ማለቱ ነው፡፡ የፍየሎቹ/በጎቹ ባለቤቶችም “ምን ገዶኝ! እንካ ይኸው” ይሉና ሽልንግ ወይም ብር ይሰጡታል፡፡

ታዲያ ሹብሹብ ቢዝነሱ በጣም ስለጣመው ብሩ በርከት እንዲልለት ፈለገ፡፡ በመሆኑም በጸሐይ መግቢያ ገደማ ብዙ በጎችን/ፍየሎችን እያባረረ ከሰው አይን በመሰወር በሶስት ሰዓት ገደማ ወደ ዋናው መንገድ እያወጣቸው “በግ የጠፋበት! ፍየል የጠፋው” እያለ መለፈፍ ያዘ፡፡ በዚህም ብዙ ብር ማግኘት ጀመረ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን ነገሩ ተነቃበት፡፡ የከተማው ሰዎች ፍየሎቻቸውን/በጎቻቸውን ከጅብ ማስተረፋቸው ቀረና ትግሎ ከሹብሹብ ጋር ሆነ፡፡ በተለይ ብዙ ፍየሉችና በጎች የመበራቸው ከተሜዎች ለሹብሹብ ብር መገበሩ አንገሸገሻቸው፡፡ ሹብሹብን ራሱን እንደ ጅብ ፈሩት፡፡ በዚህም የተነሳ በርካታ ቤተሰቦች ልጆቻቸውን “ፍየላችንን ጅብ እንዳይበላው ቶሎ አስገባው” ማለታቸው ቀርቶ “ፍየላችንን ሹብሹብ ሳይይዝብን ቶሎ አስገባው” ማለት ጀመሩ፡፡
 
 “ሹብሹብ”ም በዚህ መንገድ ከዚያ ጣፋጭ ቢዝነስ ጋር ተቆራረጠ፡፡ እስከ እኩለ ሌሊት ፍየሎቻቸውን ከመንገድ ላይ ማስገባት የማያውቁ በርካታ ሰዎች ለሹብሹብ የሚከፍሉትን ብር ለመሸሽ ሲሉ ጸባያቸውን አስተካከሉ፡፡ የቤት እንስሳትን በጊዜ ከመንገድ ላይ ማስገባትም ተለመደ፡፡
-------
ለዛሬ በዚህ ይብቃኝ፡፡ ቀሪውን በሚቀጥለው ክፍል እለጥፈዋለሁ፡፡ ታዲያ እናንተም የምታውቁትን ማዋጣቱን እንዳትረሱ፡፡
በወዳጅነታችን እንሰንብት፡፡
አፈንዲ ሙተቂ

No comments:

Post a Comment