Friday, September 13, 2013

“ዓሊ ሸቦ” እና “ፍለጋው”


ጸሓፊ፡- አፈንዲ ሙተቂ
----------
ባልሳሳት ዘመኑ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር 1978 ይመስለኛል፡፡ በዚሁ ዓመት ነበር አንድ አንጋፋ አርቲስት አስደናቂ ዜማውን የለቀቀው፡፡ ይህ ሰው ፍቅረኛው ስለጠፋችበት በዘፈኑ እየተመራ በእግር በፈረስ ይፈልጋት ጀመር፡፡ በቆላውና በደጋው ሁሉ ሲንከራተትላት ከረመ፡፡ በመጨረሻም አጥቷት ልቡ እንደተሰበረ ወደቤቱ ሊገባ ሲል በአንድ ከተማ ውስጥ አገኛትና በደስታ ፈነጠዘ፡፡ ከዚያም የልቡን አደረሰ፡፡
   ለመሆኑ እርሱ ማን ነው? ጉዞውን እንዴት ፈጸመው? እስቲ አብረን እንየው
  *****  *****  *****
   ዓሊ ሸቦን ለኦሮምኛ ተናጋሪዎች ለማስተዋወቅ አልቃጣም፡፡ አማርኛ ከሚናገሩት ውስጥ ግን እርሱን የማያውቁት እንደሚበዙ ይታወቀኛል፡፡ ስለዚህ ትንሽ ማብራሪያ ቢጤ እነሆ!
 
“ዓሊ ቢራን ለሙዚቃ እድገትህ አርአያ የሆነህ ማን ነው?” ብላችሁ ብትጠይቁት “ዓሊ ሸቦ” በማለት ነው የሚመልስላችሁ፡፡ ትንሹ ዓሊ (ቢራ) ትልቁን ዓሊ (ሸቦ) ስላየ ነው ወደ ከያኒነት የገባው፡፡ ጊታር ከመጫወት ጀምሮ በህዝብ ፊት ቆሞ እስከ መዝፈን ያሉትን እውቀቶች ሁሉ የቀሰመው ከዓሊ ሸቦ ነው፡፡

   በርግጥም ዓሊ ሸቦ በጣም አንጋፋ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት እድሜው ወደ ሰባ ገደማ እንደሆነ ይገመታል፡፡ በ1950ዎቹ መጀመሪያ ላይ በድሬዳዋ ከተማ “አፍረን ቀሎ” የሚባለውን የኪነት ቡድን ከመሰረቱትና በቡድኑ አባልነት ከተመዘገቡት የመጀመሪያቹ ሰዎች አንዱ ነው፡፡ ወደ ስልሳ ዓመታት በሚጠጋው የሙዚቃ ህይወቱ የተጫወታቸው ዘፈኖች እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ ከነርሱ ውስጥ “ዱምቡሼ ገላ”፣ “አማሌሌ”፣ “ኢስፖርቲ” (ስፖርት)፣ “ሹፌራ”፤ “ቢዮ አደሬ” ወዘተ… ሊጠቀሱ ይችላሉ (የዓሊ ሸቦን “ዱምቡሼ ገላ” ለማየት ይህንን ሊንክ “ነካ” አድርጉት http://www.youtube.com/watch?v=WRb7ze724ww )፡፡






   ከዓሊ ሸቦ ኋላ የተነሱት እነ ዓሊ ቢራ፣ ሂሜ ዩሱፍ፣ ማህዲ ጃፖን፤ ሀመልማል አባተ፣ ወዘተ.. የርሱን ዘፈን ተጫውተዋል፡፡ የሶማሊያዋ ፋጡማ ቃሲምም “ሜ ማሉፊን ኦፊቱ በራ” የሚለውን የዓሊ ሸቦ ዜማ ባማረ ሁኔታ ተጫውተዋለች፡፡ የሱዳኑ መሐመድ ወርዲ “ሱድፋ” የሚባለውን ዘፈኑን ከዓሊ ሸቦ የኦሮምኛ ግጥም ጋር እየቀላቀለው ዘፍኖታል፡፡ በሌላ በኩል ዓሊ ሸቦ በጊታር ተጫዋችነቱ የበርካታ ከያኒያንን ዘፈን በሙዚቃ አጅቧል፡፡ የነ አደም ሐሩን፣ ሐሎ፣ ዳዌ፣ አልማዝ ተፈራና ከዲር ሰዒድን የድሮ ካሴቶች ስትከፍቱ ከውስጡ የምትሰሙትን ጊታር የሚጫወተው ዓሊ ሸቦ ነው፡፡
    
ስለዓሊ ሸቦ ይህንን ያህል ካልኳችሁ ይበቃል፡፡ አሁን ወደ ዋናው ጉዳይ እንለፍ፡፡
    *****  *****  *****
ከመግቢያዬ እንዳልኩት ዓሊ ሸቦ ወዳጁ ጠፋችበት፡፡ እናም በ1978 በለቀቀው ዜማው እንዲህ ሲል ፍለጋውን ጀመረ (በቅንፍ ውስጥ ያለው ተቀራራቢ የአማርኛ ትርጉም ነው)፡፡

 Diimtuu too bareedduu tannin yaadu halkuu (የኔ ቀይ ዳማ ጉብል ሁሌ እምናፍቃት)
Obsu waa hindandayuu bikka isin jirtuu (እንዲህ ጠፍታብኝስ እኔስ አልታገሳት)
Hamman deemee arku ( ካለችበት ፈልጌ እስከማገኛት)

ትንሽ ወረድ ብሎም እንዲህ በማለት ጨመረበት፡፡
Teeyso isidhaa hinbeyne bikka itti argamtu (አድራሻዋን አላውቅ የተደበቀችበትን)
Mee nin iyyaafadha oliifi gadittuu (እኔስ ላስሳት ነው ሄጄ ታቹን ላዩን)
Barbaadu waa hindhabu Haraguma haataatu (ከሀረርጌ ምድር አገኛት እንደሆን)

  ታዲያ ዓሊ ፍለጋውን ከየት የጀመረ ይመስላችኋል? ከሀረር ነው፡፡ በጥንታዊቷ የአባድር ከተማ ላይ ከትሞ ነው እንዲህ በማለት ለፍለጋዋ መቁረጡን ያሰማው፡፡ ከዚያስ ወዴት ቀጠለ? እንዲህ ይለናል፡፡
 Dirree Dhawaas bu’ee mana gaggaafadhe (ድሬ ዳዋ ወርጄ ጠያይቄ አድራሻዋን)
Tanin shakke cufa suuta akheekadhe (በጥንቃቄ አይቼ እርሷ ትሆን ያልኳቸውን)
Dhiiroo barbaada isii oow’i waan nagodhe (ወበቅ ብቻ ተረፈኝ ወይ እኔን ወይ እኔን)

   ዓሊ ፍለጋውን በተስፋ ከድሬ ዳዋ መጀመሩ ልክ ነበር፡፡ በርግጥም ድሬ ከምስራቁ ክፍል ልዩ ልዩ መንደሮች የተሰባሰቡ ሰዎች መኖሪያ ናት፡፡ የዚያ ዘመን ወጣት በድሬ የተጧጧፈው የኮንትሮባንድ ንግድ ስለሚያስጎመጀው እንደምንም ብሎ በከተማዋ ላይ  ከትሞ እየሸቀለ ኑሮውን መሙላት ይፈልጋል፡፡ በአነስተኛ ከተሞች የከበረው ነጋዴ የመጨረሻው ዓላማው ድሬዳዋ ገብቶ ስሙን እነ ሐሰን ፎርሳ፣ ባሻንፈር፣ ሐምዳኢል፣ ሙሐመድ አብዱላሂ ኦግሰዴን ከመሳሰሉ የዘመኑ ዲታዎች ተርታ ማሰለፍ ነው፡፡ በድሬ ዘመድ ያላቸው ኮረዳዎችም “ቫኬሽን”ን እያሳበቡ ከቤተሰቦቻቸው ያፈተልኩና ክረምቱን በዚያች ውብ ከተማ ለማሳለፍ ወደዚያው ያቀናሉ፡፡ ታዳጊዎችም የሐሺሚን ሓላዋና ባቅላዋ በዝናው ስለሚያዉቁት እዚያ ሄደው ካልበሉት የሚረኩ አይመስላቸውም፡፡ ስለዚህ ቤተሰቦቻቸው ወደ ድሬዳዋ የሚሄዱ ከናንተ ጋር ካልሄድን ብለው ያስቸግራሉ፡፡

   በአንጻሩ ደግሞ ከሀረርጌ ወደ ሌሎች ቦታዎች መጥፋት የሚፈልግ ሰው ለመነሻው ድሬዳዋን ነው የሚመርጣት፡፡ ምክንያቱም በባቡር ወደ ጅቡቲ፣ በአውሮፕላን ወደ አዲስ አበባና ወደ ሌላም ቦታ ሊጠፋ ይችላልና፡፡ የሀገር አቋራጭ አውቶቡስም ቢሆንም በብዛት ከድሬዳዋ ነበር የሚነሳው፡፡ ለዚህ ለዚህ ድሬ በጣም ምቹ ነበረች፡፡

    በዚህ ስሌት መሰረት ነው እንግዲህ ዓሊ ሸቦ ፍቅረኛውን ለማሰስ ወደ ድሬ የወረደው፡፡ ከዚያም ሄዶ ፈለጋት! አስፈለጋት፡፡ የጠረጠራቸውን ቦታዎች ሁሉ ፈተሸ፡፡ ነገር ግን ትርፉ የድሬ ዳዋ ሀሩርና ወበቅ ሆነና አረፈው፡፡ ከዚያስ ወዴት አመራ? እንዲህ ይለናል ዓሊ ሸቦ፡፡

  Jijjiga Hindabartu kharaa Gursum khana (ከጅጅጋስ አታልፍ ከዚያም ከጉርሱም)
  Xuuxxisaa dhagayeetin itti-fufe amna (እያልኩ በጥርጣሬ ተይዤ ብሄድም)
 Way garaa jalalaa laalaa laala gowwomina ( እዩት የኔን ፍቅር ሞኝነቴን ሲያስቀድም)

  አዎን! ልጅቷ ከድሬ ከጠፋች በቀጥታ ወደ ጅጅጋ ልታመራ ትችላለች ብሎ ማሰብ ደግ ነው፡፡ ጅጅጋ የድሬን ያህል ባትሆንም በንግድና በስራ ሰበብ ብዙ ሰው ይጎርፍባታል፡፡ ደግሞም ለሶማሊያ ድንበር ቅርብ ስለሆነች በሀገር ውስጥ መኖር ያስመረረው ሰው ወደርሷ  ይሄድና ለውጪ ጉዞው መንደርደሪያ ያደርጋታል፡፡

   ዓሊ ሸቦም ፍቅረኛው ከሀገሬ ሳትጠፋብኝ ቶሎ ልድረስባት ብሎ  ወደዚያ በማቅናቱ ጥሩ መላ ዘይዷል፡፡ ነገር ግን ትርፉ ድካም ብቻ ሆነበትና ሆደ ባሻነቱን አባባሰበት፡፡ “ለመጽናኛዬ ወደ ጉርሱም ጎራ ብዬ ልፈልጋለት” ቢልም አልተሳካለትም፡፡ ታዲያ እንዲያ ለፍቶ ቢያጣት ጊዜ ምነው አይከፋ? ማልቀስ እንኳ ሲያንሰው ነው! ግን ምን በጀው? ወዴትስ ይሂድ? እንዲህ በማለት ይናገረዋል፡፡

 Kharaa baddaa Khanaa hindhabamtu Laata (ከወደ ደጋው በኩልስ ምናልባት አትጠፋም)
Je’e numan dhaqe ani Gaara Mul’ataa (እያልኩኝ በጉጉት ጋራሙለታ ብወጣም)
Arkuu waa hindandeenyee waan isii fakkaataa (እርሷን የምትመስል ጭራሽ አልታየችም)

 አሁን ዓሊ ሸቦ በአዕምሮው ተደናበረ፡፡ “ምን ይውጠኛል?” ማለትን አመጣ፡፡ ስለዚህ ጀርባውን አዙሮ ሸመጠጠ፡፡ መቼም “ፍቅረኛዬ ከሀረርጌ ውስጥ አትውጣ እንጂ ፈልጌ አላጣትም” ብሎ የለ? ስለዚህ ጀርባውን ሰጥቶ ያለፋቸውን ቦታዎች ማሰስ ነበረበት፡፡ በዚህም መሰረት ነው እንግዲህ ወደ ደጋማው የጋራሙለታ አውራጃ የወጣው፡፡ ነገር ግን በለስ ሊቀናው አልቻለም፡፡ እርሷን የምትመስል ሴት በጭራሽ አልታየችውም፡፡ በመሆኑም ለፍቶ መና ሆኖ ተመለሰ (እርሱ ባይገልጸውም የግራዋ ብርድ በሀይለኛው እንደጠለዘው ይታየኛል)፡፡
    *****  *****  *****
   ዓሊ ትንፋሽ ወስዶ እንደመቆዘም አለ፡፡ ፍቅረኛው የት ገባችበት? ሰማይ ላይ ወጣች? ወይንስ ወደ ምድር ሰረገች? ብቻ አሁንም መንገዱን አላቆመም፡፡ እናም እንዲህ አለ፡፡

Oborraa fi Ciroo hunda kehysa dhaqe (ኦቦራና ጭሮን በአካል አሰስኩት)
Miilaa fi makinaan barbaadeetin dhabe (በእግር በመኪና ሁሉን አዳረስኩት)
Argu koo waa hin oolu je’etin of sobe ( “ጭራሽ አላጣትም” ለሆዴ እያልኩት)

 ከጋራ ሙለታ አውራጃ ያጣትን ፍቅረኛውን ለማግኘት ፍጥነት ጨመረ፡፡ ወደ ምዕራብ ገስግሶ “ኦቦራ” (ወበራ) እና ጭሮን (ጨርጨርን) በፍለጋ አዳረሰ፡፡ ነገር ግን ሊያገኛት አልቻለም፡፡ እንዲያውም እርሷን ሳያገኛት የሀረርጌ ምድር ሊያልቅበት ሆነ፡፡ ቢሆንም ተስፋ አልቆረጠም፡፡ ከዚያስ ምን ተከተለ? እንዲህ በማለት ያስረዳል፡፡

Sa eedaan qalbiin tuni wahayyuma beyti ( ለካስ ይህቺ ቀልቤ የፊቱን ትገምታለች)
Baddeeysa ol kunnaan khate gammachutti (በዴሳን ሳልፈው በደስታ ተብከነከነች)
Jaalalleen tiyya tun intala Habrootii (ፍቅረኛዬ ለካንስ የሀብሮ ልጅ ነች)

    አዎን! ዋናው ተስፋ አለመቁረጥ ነው፡፡ ችግር መከራውን ከታገሱት ያሰቡትን ያሳካሉ፡፡ ተስፋን ይዞ ሲባዝን የከረመው ዓሊ ሸቦም ድካሙን ሁሉ ቻለው፡፡ እናም ከውስጡ የተስፋ እንጥፍጣፊ ሳያልቅ የደስታው መዓዛ አወደው፡፡ ከጭሮ ታጥፎ በዴሳን እልፍ እንዳለ ፍቅረኛው ከሩቅ ሸተተችው፡፡ ለካስ ውቃቢው ነው ዝም ብሎ ፈልግ ያሰኘው እንጂ ልጅቱ ቀድሞውንም ቢሆን አልጠፋችበትም? እንደተፈጠረች እትብቷ ከተቀበረባት ቦታ ሆና ትጠብቀው ነበር፡፡ “የት?” ብትሉ “ሀብሮ” ነው መልሱ!

  የዓሊ ሸቦ ፍቅረኛ የሀብሮ ልጅ ሆና ተገኘች፡፡ ታዲያ “ሀብሮ” ሰፊ አውራጃ ነው እንጂ አንድ ከተማ ወይንም መንደር አይደለም፡፡ ከቁኒ እስከ ባሌ ጠረፍ ድረስ ያለው ተራራማ ምድር ሁሉ የሚካተትበት ክልል ነው፡፡ ስለዚህ የልጅቱ ትክክለኛ አድራሻ መታወቅ አለበት፡፡ ዓሊ ሸቦ የመጨረሻውን ውጤት እንዲህ በማለት ያበስረናል፡፡

 Jaalallen gar meeqaan barbaadaan of rakkee (ስንት ሀገር በፍለጋ ያዳረስኩላት ፍቅረኛዬን)
Tanin deemee dhabe baakkan itti shakkee (ከሁሉም ቦታዎች ያጣኋት ጉብልዬን)
 Walkkaa magaalaa Galamsottiin arke (ገለምሶ መሀል ላይ አገኘኋት ወዳጄን)

 እንዲህ ነው ዓሊ ሸቦ! ብራቮ ዓሊ ሸቦ! እርሱ ከቆላ ደጋ የተንከራተተላት ጉብል የገለምሶ ልጅ ሆና ተገኘች! የወንዜ ልጅ! ግዳዩም በድል ተጠናቀቀ! ዓሌ ሸቦ በሐሴት ባህር ዋኘ፡፡ ነፍሲያውም በደስታ ረካች! በመጨረሻም ዓሊ እንዲህ አለና አጠቃለለ፡፡

 Arkadhe qal’o too diimtuu too bareedduu (አገኘሁ የኔን አለንጋ ያላት የደስ ደስ)
Isii barnootarra kharaa gala deemtu (ከትምህርት ቤት ወደ ቤቷ ስትመለስ)
 Gamdeen bahaa mee ree dheebuu tootuu (ዛሬ ጥማቴን ልወጣው የልቤ እንዲደርስ)

    *****  *****  *****
አንድ የሚነደኝ ነገር ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? በሸዋ ከተሞች (አዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ቢሾፍቱ ወዘተ..) “የገለምሶ ልጅ ነኝ” ከተባለ በሳቅ የሚያውካኩ ሰዎች አሉ፡፡ ምክንያቱ ለምን ይመስላችኋል? አንዳንድ “ውሪ ውሪ” ነጋዴዎች የከተማዬን ስም ከዚያ ዘመነኛ “ቅጠል” ጋር በማያያዛቸው ነው፡፡ በመሆኑም ገለምሶ ሲባል ብዙዎቹ የሚታያቸው ያ ጫት የሚባለው “ጨረንጉላ” ቅጠል ነው፡፡ ደግሞ እኮ የሚያሳዝነው ቅጠሉ ከዚያ አይደለም የሚጫነው፡፡ አብዛኛው “ከራ ዱለቻ”፤ “ዴፎ”፣ “ቢዮ”፤ “ሚሊሎ” እና “ዳሎ” ከሚባሉ ትንንሽ የገጠር ከተሞች ነው የሚጫነው፡፡ ነጋዴዎቹ ጫቱ “ዳሎ” ወይንም “ሚሊሎ” ቢባል የማይታወቅ ሰለመሰላቸው ነው በከተማዬ ስም የጠሩት፡፡ እነዚህ ከይሲዎች! ጂንኒ ጀቡቲ ሁላ!

 እርግጥ ጫት በገለምሶም አለ፡፡ ግን ብዙዎች እንደሚያስቡት ገለምሶ በጫት የናወዘች ከተማ አይደለችም፡፡ የዛሬን አያድርገውና ዓሊ ሸቦን እንዲህ በፍለጋ ያንከራተተች “ቀሽቲ” ከተማ ነበረች፡፡ በሀረርጌ ምድር ከሀረርና ከጉርሱም (ፉኛን ቢራ) በስተቀር በእድሜ የሚቀድማት ከተማ የለም፡፡ አሁን እነ “በዘበዛ” አደከሟት እንጂ፡፡ ግድ የለም! አንድ ቀን ትነሳለች፡፡ አንድ ቀን ገለምሶም፣ ሀረርም፤ ድሬዳዋም፣ አዲስ አበባም፣ ኢትዮጵያም ሁሉም ይነሳሉ፡፡ ዋናው ተስፋ አለመቁረጥ ነው፡፡ 
    *****  *****  *****
አሁን ወደ ወጋችን እንመለስ፡፡

  ዓሊ ሸቦ እንዴት ይህንን ዘፈን ሊዘፍን ቻለ? ከጀርባው ታሪክ አለው፡፡ መሐመድ አሕመድ (መሐመድ ቆጴ) የሚባል የዚያ ዘመን ታዋቂ ጋዜጠኛ የከተማችንን ጉብል ወደዳት፡፡ ሆኖም ፍቅሩ በምን ይውጣለት? በምን ያቅርባት?
  ምናልባት በዘፈን ብጠራት እሺ ትለኝ ይሆናል ብሎ ይህንን ድርሰት ጻፈላት፡፡ ዓሊ ሸቦም ተጫወተው፡፡ ግን ልጅቷና መሐመድ ቆጴ ለጥቂት ተላለፉ፡፡ መሐመድ በዘመኑ ደንብ መሰረት የልጅቷን ቤተሰቦች ለጋብቻ ሊጠይቃቸው ሲሰናዳ አንድ የአዲስ አበባ ሰው ቀደመውና ወሰዳት፡፡ ግን ገለምሶና የዓሊ ሸቦ ዘፈን እንደተጣመሩ ቀሩ፡፡

በመጨረሻም!
የዘፈኑን ግጥሞች በደንብ አያችኋቸው?… ሁሉም ባለ ሶስት መስመር ናቸው… በዚያ ዘመን በአማርኛም ሆነ በኦሮምኛ እንደዚህ ይገጠም ነበር፡፡ የዚያ ዘመን ደራሲዎች እንዲህ እየደረሱ ሰውን አጃዒብ ያስብሉ ነበር፡፡ ይህም ዘፈን የመሐመድ ቆጴን ችሎታ ካገነኑት ስራዎች መካከል አንዱ ሆኖ እስከ አሁን ድረስ ይዘከራል፡፡
   በነገራችን ላይ ሙሐመድ ቆጴን አወቃችሁት? ሐመልማል አባተ የምትዘፍናቸውን የኦሮምኛ ዘፈኖች በሙሉ የገጠመው ደራሲ ነው፡፡ መሐመድ አሁንም በህይወት አለ፡፡
----
አፈንዲ ሙተቂ
መስከረም 3/2006
 
Afendi Muteki is a researcher of ethnography and history of the peoples of east Ethiopia. He is an author of “Harar Gey”, an ethnography book about the historical city of Harar. You can read some of his articles on his facebook page and his blog.

1 comment:

  1. Always loved this song, and tried to sing along even though i don't know the meaning of the song. Thank you for this!

    ReplyDelete