Saturday, December 6, 2014

ዋለልኝ መኮንን-አፈና ያልገታው የአመጽ ድምጽ



ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
  ተነገወዲያ ህዳር ህዳር 29/2007 ዘጠነኛው የብሄርና ብሄረሰቦች ቀን ሊከበር ነው፡፡ ይህ ቀን ለበዓሉ አከባበር የተመረጠው የኢፌዴሪ ህገ-መንግሥት የጸደቀበት ስለሆነ ነው ተብሏል፡፡ ታዲያ በዚሁ ቀን አንድ ታላቅ አብዮታዊ ተገድሎ ነበር፡፡ የሚገርመው ደግሞ በዚያች ቀን የሞተው ሰውዬ በኢትዮጵያ ውስጥ የብሄርና ብሄረሰቦች መብት መከበር አለበት በማለት ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ የጻፈ ሰው መሆኑ ነው፡፡
                                                                          *****
      ህዳር 29/1964፡፡ ረፋዱ ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ቦይንግ 708 ጄት አውሮፕላን ከአዲስ አበባ በአስመራ በኩል ወደ አቴንስ ሊበር ነው፡፡ በአውሮፕላኑ የሚጓዙ መንገደኞች ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል፡፡ ሰባት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችም ከአውሮፕላኑ ውስጥ ተሳፍረዋል፡፡ የበረራው ሰዓት ሲደርስ አውሮፕላኑ ከመሬት ተነሳ፡፡ ከሰማዩ ገብቶ መብረር ሲጀምር ግን ያልታሰበ ሁኔታ ተከሰተ፡፡ እነዚያ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አውሮፕላኑን በቁጥጥራቸው ስር ማዋላቸውን አስታወቁ፡፡  እነርሱ ወደሚፈልጉት ሀገር እንዲበሩም አብራሪዎቹን አዘዟቸው፡፡ ተማሪዎቹ የጠለፋ እወጃውን ካሰሙ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ሌላ ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡ አውሮፕላኑን ከጠለፋ እንዲታደጉ የታዘዙ ኮማንዶዎች በቀጥታ በጠላፊዎቹ ላይ በማነጣጠር ተኮሱባቸው፡፡ ስድስት ጠላፊዎች ተገደሉ፡፡ አንዲት ጓደኛቸው ደግሞ በከባድ ሁኔታ ቆሰለች፡፡ የአውሮፕላኑ ወለል በሙታኑ ደም ታጠበ፡፡

Walelign Mekoneen

                                                                          *****
    በዚያች ዕለት የሞተው ታዋቂው የተማሪዎች ንቅናቄ መሪ ዋለልኝ መኮንን ነበር፡፡ ከርሱ ጋር የተገደሉትም ማርታ መብራህቱ፣ ጌታቸው ሀብቴ፣ ተስፋዬ ቢረጋ፣ ዮሐንስ በፈቃዱ እና አማኑኤል ዮሐንስ ናቸው፡፡ እነዚያ ወጣቶች አውሮፕላኑን ለመጥለፍ የሞከሩት የስርዓቱ ክትትል መፈናፈኛ ስላሳጣቸው ነው፡፡ ዓላማቸው ወደ ውጪ ከኮበለሉት ጓደኞቻቸው ጋር በመቀላቀል ለስር-ነቀል ለውጥ የሚታገል ድርጅት መመስረት ነበር፡፡ ከድርጅቱ ምስረታ በኋላም ወደ ሀገር ቤት ተመልሰው ትግሉን በየአቅጣጫው ለማፋፋም አስበዋል፡፡ ሆኖም እንደተመኙት አልሆነላቸውም፡፡ አውሮፕላን ለመጥለፍ ማቀዳቸው ቀደም ብሎ ተጠቁሞ ስለነበር የጸጥታው ክፍል በአየር ላይ አፍኖ አስቀራቸው፡፡
                                                                          *****
     ከላይ በተገለጸው አሳዛኝ ገቢር (ትራጄዲ) ህይወቱ የተቋጨው ዋለልኝ መኮንን በወሎ ክፍለ ሀገር የሳይንት (ቦረና) አውራጃ ተወላጅ ነው፡፡ የአንደኛና ደረጃ ትምህርቱን በደሴው ንጉሥ ሚካኤል ትምህርት ቤት አጠናቀቀ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱንም እስከ አስረኛ ክፍል ድረስ ደሴ ከተማ በሚገኘው ታሪካዊው ወይዘሮ ስሒን ት/ቤት ተከታለለ፡፡ አስራ አንደኛና አስራ ሁለተኛ ክፍልን ደግሞ የዘመኑ ምርጥ ተማሪዎች መማሪያ በነበረው በአዲስ አበባው በዕደማሪያም ትምህርት ቤት አገባደደ፡፡ በ1958 ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከገባ በኋላም እጅግ የተለየ አብዮታዊ ሆነ፡፡

ዋለልኝ በ1959 በዩኒቨርሲቲው በተደረገው የግጥም ውድድር “ሙት ወቃሽህ መጣው” በሚለው ግጥም አንደኛ ወጥቷል፡፡  በዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ህብረት ይዘጋጅ በነበረው የታገል መጽሔት ከማንም በላይ የነቃ ተሳትፎ ያደርግ ነበር፡፡ በህቡዕ የሚዘጋጁ ጽሑፎችንም እያዘጋጀ ያሰራጭም ነበር፡፡ በተለይ “አዞዎቹ” የሚባለው የስር-ነቀል ለውጥ ደጋፊ የተማሪዎች ስብስብ በአቋም ደረጃ የተስማማባቸውን ሀሳቦች በጽሑፍ እያቀናበረ የሚያዘጋጀው እርሱ እንደነበር በያኔው እንቅስቃሴ የተሳተፉትም ሆነ የዘመኑን ታሪክ ያጠኑ ምሁራን ይመሰክራሉ፡፡
 
   ከዋለልኝ ጽሑፎች መካከል  ዝነኛ የሆኑት ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው ከላይ የጠቀስኩትና ህዳር 10/1961 በታተመው “ታገል መጽሔት” ላይ የወጣው “የብሄረሰቦች ጥያቄ በኢትዮጵያ” የሚል ርዕስ ያለው ጽሑፍ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ1962 የተማሪዎች ህብረት ፕሬዚዳንት የነበረው ጥላሁን ግዛው ሲገደል የአጼው ስርዓት በተማሪዎቹ ላይ ያደረገውን ዛቻ በመቃወም “ለአዋጁ አዋጅ” በሚል ርዕስ በህቡዕ ጽፎ የበተነው ጽሑፍ ነው፡፡ ዋለልኝ በጽሑፎቹ ሳቢያ በተደጋጋሚ ጊዜያት ታስሯል፡፡ በተለይ “ለአዋጁ አዋጅ”ን የጻፈው እርሱ መሆኑ ሲታወቅ በችሎት ፊት ቀርቦ አምስት ዓመት እስራት ተፈርዶበታል (ሆኖም ተማሪዎች ባደረጉት ከፍተኛ የተቃውሞ ጫና ከዓመት በኋላ ተፈትቷል)፡፡

     ከ1962 በኋላ ሁለት ክስተቶች የተማሪውን ንቅናቄ አቅጣጫ ቀይረውታል፡፡ እነዚህም በስርዓቱ የሚደረገው አፈና መጠናከር እና የድርጅት ምስረታ ጥያቄ መቀስቀስ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደ ቀድሞው ጊዜ የተቃውሞ ሰልፍ ከማድረግ ይልቅ የጥናት ክበቦችን እየመሰረቱ መወያየቱን መረጡ (የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በተቃውሞ ቀጠሉ)፡፡ ዋለልኝም በውይይት ክበቡ በሚያደርገው ጥናት ላይ አተኮረ፡፡ ከሀገር ተሰደው በአልጄሪያ ከሚገኙት እነ ብርሀነ መስቀል ረዳ ጋር በሚያደርገው የደብዳቤ ልውውጥ አማካኝነትም ሰፊ መሰረት ያለው ድርጅት ለመመስረት በሚደረገው ውይይትም ውስጥ ይሳተፍ ነበር፡፡ ህዳር 29/1964 በውጪ ካሉት ጓደኞቹ ጋር ለመቀላቀል ሲል አውሮፕላን ጠለፈ፡፡ ሆኖም ካሰበው ስፍራ ሳይደርስ በአውሮፕላኑ ውስጥ ተገደለ፡፡
                                                                          *****
     ከያኔው የተማሪዎች ንቅናቄ መሪዎች መካከል ዋለልኝ መኮንን ልዩ የሚያደርገው አንድ ነገር አለ፡፡ ይኸውም የተለያየ አመለካከት ባላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች እንደ ታላቅ ሰማዕት የሚታይ መሆኑ ነው፡፡ ደርግ፣ ኢህአፓ፣ ህወሐት፣ ኦነግ፣ ሻዕቢያ፣ መኢሶን፣ ወዘተ… ሁሉም ለርሱ በጎ አመለካከት ነው ያላቸው፡፡ ታዲያ በዋለልኝ ታሪክ ላይ የሚደረገው ሽሚያም በጣም የጠነከረ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ታሪኩን ከራሳቸው ድርጅት ጋር ለማቆራኘት ይሞክራሉ፡፡ በወቅቱ የነበረው የርሱና የጓደኞቹ አሰላለፍ ሲገመገም ግን ዋለልኝ ኢህአፓን ከመሰረቱ ወጣቶች ጋር ተመሳሳይ የፖለቲካ መስመር የነበረው ሆኖ ነው የሚታየው፡፡ ኢህአፓን የመሰረቱትም የርሱ የቅርብ ጓደኞች ናቸው፡፡ በመሆኑም ዋለልኝ በህይወት ቢሰነብት ኖሮ የዚሁ ድርጅት አባል ይሆን ነበር ተብሎ ነው የሚገመተው፡፡
                                                                          *****
ዋለልኝ መኮንን ከብዙ በጥቂቱ ይህ ነበር፡፡ ወደፊት ሰፋ ባለ ሁኔታ ስለርሱ እጽፋለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ እናንተም በበኩላችሁ የምታውቁትን እንድታጋሩን በአክብሮት እንጠይቃችኋለን፡፡
------                                                        
ሰላም
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 29/2006

Friday, December 5, 2014

ሼርሎክ ሆምዝ




(አፈንዲ ሙተቂ)
------
  በ19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ ነው፡፡ በታላቋ ብሪታኒያ ዋና ከተማ፡፡ በጊዜው አንድን አስገራሚ ገጸ-ባህሪ ያማከለ ተከታታይ የምርመራ ልብ ወለድ የሚጽፍ ወጣት ደራሲ ነበር፡፡፡ ታዲያ ይህ ደራሲ በዚያ ገጸ-ባህሪው ላይ ለአስር ዓመታት ከጻፈ በኋላ “ኤጭ! ይሄ ሰውዬ አሁንስ እጅ እጅ አለኝ፡፡ ስራ አስፈታኝ እኮ አቦ!… ከዚህ በኋላ ገድዬው ልረፍና ሌላ ድርሰት ልጻፍ” በማለት እራሱ የፈጠረውን ገጸ ባህሪ ይገድለዋል፡፡
 
     ይሁንና ገጸ-ባህሪውን የገደለው ደራሲ እንደተመኘው ሌሎች ድርሰቶችን በሰላም ሊጽፍ አልቻለም፡፡ ሺህ ምንተሺህ ደብዳቤዎች ከየአቅጣጨው ጎረፉለት፡፡ “አንተ ቀፋፊ፣ የማትረባ ወስላታ፣ አረመኔ ነህ” እየተባለ ተወቀሰ፤ ተወገዘ፡፡  “እኛ የምንወደውን ሰውዬ ገድለህ በሰላም መኖር አትችልም! አንተም ዋጋህን ታገኛታለህ” የሚሉ ማስፈራሪያዎችም እየተከታተሉ ደረሱት፡፡ በማስከተልም በሺህ የሚቆጠሩ አንባቢያን በለንደን ጎዳናዎች ላይ ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ደራሲው የገደለውን ገጸ-ባህሪ ከሞት እንዲያስነሳው ጠየቁት፡፡

  ደራሲው በዚህ ጉዳይ ተጨነቀ፡፡ ተጠበበ፡፡ የህዝቡን ፍላጎት ካላሟላ አደጋ ሊከተለው እንደሚችል ገመተ፡፡ ስለዚህ ሳይፈልግ በግዴታ በራሱ ብዕር የገደለውን ገጸ-ባህሪ ነፍስ ዘርቶበት እንደገና ወደ ስነ-ጽሑፍ ዓለም መለሰው፡፡ ህዝቡም የተመኘውን በማግኘቱ “እፎይ!” አለ፡፡
                                                     *****
  ያ ሰላማዊ ሰልፍ የተወጣለት ገጸ-ባህሪ “ሼርሎክ ሆምዝ” (Sherlock Holmes) ይባላል፡፡ በስነ-ጽሑፍ ዓለም ምንጊዜም ከማይረሱ ልዩ ገጸ-ባህሪያት አንዱ ነው፡፡ ሼርሎክ ሆምዝ የግል ወንጀል መርማሪ ነው፡፡ የመንግሥት ባለስልጣናትም ሆኑ ግለሰቦች አዕምሮአቸውን ያስጨነቀ ወንጀል-ነክ ጉዳይ ሲያጋጥማቸው ወደ ቢሮው እየሄዱ ጉዳያቸውን ያዋዩታል፡፡ እርሱም ልዩ ልዩ ፍንጮችን እየተከተለ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ ውጤቱን ለባለጉዳዮቹ ያሳውቃል፡፡ በዚህም መሰረት ወንጀሉ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀለኛው ርቆ ሳይሄድ በቁጥጥር ስር እንዲውል ይደረጋል፡፡ ወንጀሉ ወደፊት ሊፈጸም የታቀደ ከሆነ ደግሞ ሼርሎክ ሆምዝ ወንጀሉ ከመፈጸሙ በፊት ወንጀለኛውን በቁጥጥር ስር ያውለውና ከነማስረጃው ለፖሊስ ያስረክባል፡፡

  ታዲያ ሸርሎክ ሆምዝ የሚፈጽማቸውን ጀብዱዎች የምንሰማው ከርሱ አንደበት አይደለም፡፡ የዕለት ተዕለት ውሎውን እየተከታተለ ለኛ የሚዘግብልን ዶ/ር ጆን ኤች ዋትሰን የሚባል ጓደኛው ነው፡፡ ዶ/ር ዋትሰን የሼርሎክ ሆምዝ የልብ ጓደኛ እና ሚስጢረኛው ነው፡፡ ሁለቱ ሰዎች ለብዙ ጊዜ አይለያዩም፡፡ አንድ ልዩ ኦፕሬሽን የሚካሄድ ከሆነ ሼርሎክ ሆምዝ ጓደኛው ዶ/ር ዋትሰን እንዲሳተፍበት ያደርጋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ዋትሰን ከሎንዶን ወደ አውሮጳ እየተላከ ሼርሎክ ሆምዝ የሚፈልጋቸውን መረጃዎች እንዲያሰባስብ ይደረጋል፡፡
 
    በዶ/ር ዋትሰን ገለጻ መሰረት ሼርሎክ ሆምዝ ቀጠን ዘለግ ያለ እንግሊዛዊ ነው፡፡ ቢሮው በደቡብ ለንደን በሚገኘው የቤከር ጎዳና ነው፡፡ አንዲት የነተበች ባርኔጣ ይለብሳል፡፡ አጭር ከዘራም ከእጁ አያጣም፡፡ ሼርሎክ ሆምዝ በጣም አጫሽ ነው፡፡ ፒፓውን ከአፉ የማይነጥል የትምባሆ ሱሰኛ! ደግሞ ግማሽ ጭልፋ የምታክል ሌንስ (አጉሊ መነጽር) ከኪሱ አትጠፋም፡፡ በርሷ ብዙ ነገሮችን ይመረምራል፡፡ በተለይም የሰው ዱካ የሚመረምረው በዚህች ሌንስ ነው፡፡ 
 
    የሼርሎክ ሆምዝ ወንጀል መርማሪነት እንዲህ ቀለል ያለ አይደለም፡፡ ኬሚካሎችንና ቅመማ ቅመሞችን በደንብ ለይቶ ያውቃል፡፡ የሲጋራዎችን አመድ በማየት ብቻ አንድ ሰው ምን ዓይነት ሲጋራ እንደሚያጨስ ለይቶ ያውቃል፡፡ ደግሞም ሼርሎክ ሆምዝ የጁዶ ጥበበኛ ነው፡፡ ወንጀለኞች ሊያጠቁት ከመጡ በጁዶ ይዘርራቸዋል፡፡ በመላው ለንደን በርካታ ሰላዮች አሉት፡፡ ሊስትሮዎች፣ ለማኞች፣ ጎዳና ተዳዳሪዎች፣ ሴተኛ አዳሪዎች፣ የባንክ ሰራተኞች ወዘተ… ልዩ ልዩ መረጃዎች እንዲያመጡለት ይቀጥራቸዋል፡፡ ከነዚህ ምንጮች በሚያገኛቸው መረጃዎች ላይ የራሱን የምርመራ ጥበብ እያከለ አስደናቂ ውጤቶችን ያገኛል፡፡
                                                     *****
    ሼርሎክ ሆምዝን የፈጠረው ደራሲ ሰር አርተር ኮናን ዶይል ይባላል፡፡ በዓለም የስነ-ጽሑፍ ታሪክ ዘወትር ከሚታወሱ ድንቅ ደራሲዎች አንዱ ነው፡፡ ኮናን ዶይል የስኮትላንድ ተወላጅ ነው፡፡ በጉርምስናው ዕድሜ ላይ ህክምናን ሊያጠና ኤዲንበርግ ዩኒቨርሲቲ ይገባል፡፡ ታዲያ እዚያ እያለ ፕሮፌሰር ጆሴፍ ቤል ከሚባሉት አስተማሪው ላይ ባየው ነገር በጣም ይመሰጣል፡፡ እኝህ ፕሮፌሰር ሀኪም ጭምር ናቸው፡፡ የህመምተኞችን በሽታ በትክክል ለማወቅ የሚጠቀሙበት የተጠየቅ (logic) አካሄድና ጥቃቅን የሆነችውን ነገር ሁሉ ለማወቅ የሚያደርጉት ጥረት በወጣቱ ተማሪ አርተር ኮናን ዶይል ላይ የማይረሳ ትውስታ ጥሎ ያልፋል፡፡
   
  ኮናን ዶይል ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ የራሱን ክሊኒክ ከፍቶ መስራት ይጀምራል፡፡ ነገር ግን ጀማሪ በመሆኑ የሚመጣለት በሽተኛ በጣም ትንሽ ነበር፡፡ ታዲያ ኮናን ዶይል አልሰነፈም፡፡ የመጡለትን በሽተኞች ካከመ በኋላ በሚኖረው ትርፍ ጊዜ ቁም-ነገር ለመስራት ወሰነ፡፡  በመሆኑም የዩኒቨርሲቲ አስተማሪውን ሁኔታ እያሰበ የሚመጣለትን ሃሳብ በወረቅ ጫር ጫር ማድረግ ጀመረ፡፡ የጻፈውንም The Study in the Scarlet የሚል ርዕስ ሰጠውና Beeton’s Christmas Annual  በተሰኘ መጽሔት ላይ አሳተመው፡፡

     ጽሑፉ “ሼርሎክ ሆምዝ” የተባለ ወንጀል መርማሪ በአስገራሚ የተጠየቅ ዘዴ ወንጀሎችን እንዴት እንደሚመረምር የሚተርክ አጭር ልብ ወለድ ነው፡፡ አንባቢያን ጽሑፉን ስለወደዱት The Strand የሚባል መጽሔት በቋሚነት የሼርሎክ ሆምዝን ታሪክ እንዲጽፍለት ቀጠረው፡፡ ደራሲው ኮናን ዶይልም ለአምስት ዓመታት ያለመሰልቸት የሼርሎክ ሆምዝን ታሪክ ጻፈ፡፡ በአምስተኛው ዓመት በታተመው አንድ ጽሑፍ ላይ ግን “ሼርሎክ ሆምዝ ሌሎች የልብ ወለድ ስራዎችን እንዳልጽፍ እያደረገኝ ነው” በማለት ገድሎት ሊገላገለው ወሰነ፡፡ The Final Problem የሚል ርዕስ የተሰጠው አጭር ልብ ወለድ ጻፈና ሼርሎክ ሆምዝን  በብዕሩ ገደለው፡፡ ደራሲው እንዲህ ሲያደርግ “ሼርሎክ ሆምዝ ሞቷል፤ ከእንግዲህ ታሪኩን አትጠብቁ” ማለቱ ነው፡፡

    ይሁንና ከላይ እንደገለጽኩት ህዝቡ በጄ አላለውም፡፡ “ሼርሎክ ሆምዝን ገድለህ አንተም በሰላም አትኖራትም!” በማለት ማስጠንቀቂያና ዛቻ ላከለት፡፡ ከዚህ ሌላም  ሃያ ሺህ የስትራንድ መጽሄት ቋሚ ደንበኞች (Subscribers) ደንበኝነታቸውን አቋረጡ፡፡ የእንግሊዝ ንጉሣዊያን ቤተሰብ ንዴቱንና ብስጭቱን ለደራሲው ገለጸለት፡፡ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ ኮናን ዶይልን ክሊኒኩ ድረስ ሄዶ ለመነው፡፡ “መጽሔታችን በኪሳራ ሊዘጋ ነው፤ ያ እንዳይሆን እባክህ ሼርሎክ ሆምዝን ከሞት ቀስቅሰውና ታሪኩን ጻፍልን” አለው፡፡

   ኮናን ዶይል የመጽሔቱ አዘጋጅ ቢሮው ድረስ ሲመጣበት ይሉኝታ ያዘውና “እምቢ!” ማለት አቃተው፡፡ ስለዚህ በዘዴ ላባርረው በማለት “በወር ሃያ አምስት ፓውንድ የምትከፍሉኝ ከሆነ እጽፋለሁ” በማለት በዘመኑ ተሰምቶ የማይታወቅ ከፍተኛ ክፍያ ጠየቀ፡፡ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ “አሳምሬ እከፍላለሁ! አንተ ብቻ ጻፍልኝ እንጂ” አለው፡፡ ኮናን ዶይል ከዚያ በፊትም ከህዝቡ የመጣበትን ዛቻ ፈርቶ ሼርሎክ ሆምዝን ሊቀሰቅሰው ወስኖ ስለነበረ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ ክፍያውን ሲጨምርበት አዲስ ጉልበት አገኘ፡፡ በመሆኑም ሼርሎክ ሆምዝን ከሞት ሊያስነሳው ወሰነ፡፡ እናም "The Adventure of the Empty House" የሚል ርዕስ የሰጠውን ልብ ወለድ ጻፈና ዝነኛውን ገጸ-ባህሪ እንደገና ከሞት ቀሰቀሰው፡፡ አንባቢዎቹም ሼርሎክ ሆምዝ አለመሞቱን ሲረዱ በደስታ ፈነደቁ፡፡

      ታዲያ ኮናን ዶይል ሼርሎክ ሆምዝን የቀሰቀሰው እንዴት መሰላችሁ?….. ጓደኛው ዶ/ር ዋትሰን ቢሮው ውስጥ ሆኖ ሲተክዝ ቆፍጣናው ሼርሎክ ሆምዝ በድንገት ወደ ቢሮው ይገባል፡፡ ዋትሰን ዐይኑን ማመን አቃተው፡፡ ካለበት በደስታ ተነስቶ አቀፈው፡፡ ከናፍቆት ሰላምታ በኋላ ዋትሰን “ሞተሃል ተብሎ አልነበረም እንዴ?…” ይለዋል፡፡ ሼርሎክ ሆምዝም “ሆን ብዬ ያስወራሁት ወሬ ነው፡፡ በጋዜጣም ማስታወቂያ እንዲነገር ያደረግኩት እኔ ነኝ፡፡ አየህ! አንድ የምከታተለው አደገኛ ወንጀለኛ አለ፡፡ ያ ወንጀለኛ አልያዝ ብሎ አስቸግሮኛል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዱካው ጠፍቶብኝ ነበር፡፡ ስለዚህ መሞቴን በጋዜጣ አሳወቅኩ፡፡ እንደዚያ ያደረግኩት ወንጀለኛው መሞቴን ሲረዳ ከተደበቀበት እንደሚወጣ ስለማውቅ ነው” በማለት ትረካውን ይጀምርለታል፡፡ ከዚያም ዝርዝሩን አንድ በአንድ ለዶክተር ዋትሰን ያጫውተዋል፡፡ ከዚያች አጭር ልብ ወለድ በኋላም ሼርሎክ ሆምዝ እንደ አዲስ መነበብ ይጀምራል፡፡
                                                      *****
    አርተር ኮናን ዶይል የሼርሎክ ሆምዝን ድንቅ ምርመራዎች የሚተርኩ 56 አጫጭር ታሪኮችንና አራት ሙሉ ልብ ወለዶችን ጽፏል፡፡ እርሱ ከሞተ በኋላ ደግሞ ሼርሎክ ሆምዝ በሺህ በሚቆጠሩ ፊልሞች፣ ቲያትሮችና ልዩ ልዩ የጽሑፍ ውጤቶች ውስጥ ለጥበብ ታዳሚዎች ቀርቧል፡፡ በዓለም ዙሪያ በርካታ የሼርሎክ ሆምዝ ቡድኖች አሉ፡፡ በለንደን ከተማ በየዓመቱ ሁለት ጊዜ የሼርሎክ ሆምዝ ፌስቲቫል ይካሄዳል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ በሺህ የሚቆጠሩ ቱሪስቶች ሼርሎክ ሆምዝ ይኖርበታል ተብሎ የተጠቀሰውንና በቤከር ጎዳና የሚገኘውን የቤት ቁጥሩ 212B የሆነውን ህንጻ በየዓመቱ ይጎበኙታል፡፡ በህንጻው ውስጥ በሼርሎክ ሆምዝ አምሳል የተሰራ አዳፋ ኮፍያ የያዘ፣ ከዘራ ያነገተና ፒፓውን በአፉ የጎረሰ አርቲፊሻል ሰው ቆሞበታል፡፡
 
  ይህ ሁሉ ክብርና ፍቅር የሚሰጠው በምናብ ለተፈጠረ ገጸ-ባህሪ ነው፡፡ ክላሲክ የሚባሉት ጸሐፍት እንደ ሼርሎክ ሆምዝ ያሉትን ከሰው ልብ የማይጠፉ ልዩ ገጸ-ባህሪያትን የመፍጠር ብቃት ነበራቸው፡፡ ዣንቫልዣ፣ ዶን ኪኾቴ፣ አንክል ቶም፣ ራስኩልኒኮቭ፣ ሐምሌት፣ ኦቴሎ፣ ወዘተ የመሳሰሉ ገጸ-ባህሪያትን የሚያውቁ የስነ-ጽሑፍ አፍቃሪዎች ሼርሎክ ሆምዝንም ዘወትር ያስታውሱታል፡፡ እኛም ዘወትር እናስታውሰለዋን፡፡
ሰላም!
  ----
መጋቢት 26/2006
አፈንዲ ሙተቂ

Thursday, December 4, 2014

በአማርኛ የተተረጎሙ ታላላቅ መጻሕፍት



 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
የውጪ ደራሲያን የጻፏቸውን መጻሕፍት ወደ አማርኛ መተርጎሙን ማን እንደጀመረው በትክክል አላውቅም፡፡ ሆኖም የዶ/ር ሳሙኤል ጆንሰን ድርሰት የሆነው “ራሴላስ” በአማርኛ የተተረጎመ የመጀመሪያው የውጪ መጽሐፍ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ ከዚያም ክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል የትርጉም ስራዎችን በስፋት ተያይዘውት ነበር፡፡ ለምሳሌ ከበደ ሚካኤል የሼክስፒርን ሮሚዮና ጁሌት በ1940ዎቹ ተርጉመውት ነበር፡፡ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህንም በርካታ የሼክስፒር ስራዎችን በ1960ዎቹ ተርጉመዋል፡፡
  
  የአማርኛ የትርጉም ስራዎች እንደ አሸን የፈሉት ግን “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት” በ1970ዎቹ ከተቋቋመ በኋላ ነው፡፡ በዚያ ዘመን በተለይም ዘመን አይሽሬ የሚባሉ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ ስራዎች በብዛት ወደ አማርኛ ተመልሰዋል፡፡ ኢ-ልቦለድ ከሆኑትም መካከል የካርል ማርክስን “ዳስ ካፒታል”ን ጨምሮ በርከት ያሉ መጻሕፍት ተተርጉመዋል፡፡

በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ ደግሞ የትርጉም ስራው የዳኒኤላ ስቴልን፣ የሲድኒ ሸልደንንና የአርቪንግ ዋላስን ስራዎች ወደ አማርኛ በመመለሱ ላይ ነበር ያተኮረው፡፡ እስከ 1990ዎቹ መጀመሪያ ድረስ በብዛት ሲተረጎሙ የነበሩት ደግሞ የጃኪ ኮሊንስ ድርሰቶች ናቸው፡፡ አሁን ግን የትርጉም ስራው ቀዝቅዟል፡፡

   ለመሆኑ እስከ ዛሬ ድረስ በአማርኛ የተተረጎሙ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ በረከቶች የትኞቹ ናቸው? ይህንን ጥያቄ መመለስ ይከብዳል፡፡ ቢሆንም የቻልኩትን ያህል ለመዘርዘር እሞክራለሁ፡፡ ታዲያ በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት በመላው ዓለም ዝነኛ ለመሆን የበቁ ስራዎች ብቻ ናቸው፡፡ ለምሳሌ የነ ዳንኤላ ስቴል፣ ሲድኒ ሸልደንና ጃኪ ኮሊንስ ስራዎች በሀገራችን በብዛት ቢተረጎሙም በዓለም ዙሪያ ያላቸው ተነባቢነት እምብዛም ነው፡፡

    መጻሕፍቱን የምጠራቸው በአማርኛው ርዕሳቸው ነው፡፡ የዋናውን ደራሲ ስም እና የተርጓሚውንም ስም እጠቅሳለሁ፡፡ በአንዳንድ የተርጓሚዎችን ማንነት ለማወቅ ስቸገር ግን ዝም ብዬ አልፌአቸዋለሁ፡፡
(ማስታወሻ፡ ይህ ዝርዝር የሃይማኖት መጻሕፍትን አይመለከትም)፡፡

==== ዘመን አይሽሬ የልብወለድ መጻሕፍት (Classical Fictions)===

1.      “ነገም ሌላ ቀን ነው”፣ ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል፣ ተርጓሚ ነቢይ መኮንን
2.     “መከረኞች”፣ ደራሲ ቪክቶር ሁጎ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም (በህይወቴ ያነበብኩት ምርጥ የአማርኛ ትርጉም ስራ ይህኛው ነው)፡፡
3.     “የሁለት ከተሞች ወግ”፣ ደራሲ ቻርለስ ዲከንስ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም
4.     “የአገር ልጅ”፣ ደራሲ ሪቻርድ ራይት፣ ተርጓሚ ሳህለሥላሤ ብርሃነማሪያም
5.     “ዶን ኪኾቴ”፣ ደራሲ ሚጉኤል ሰርቫንቴስ፣ ተርጓሚ ዳምጤ አሰማኽኝ (ሌላ ሰው ይህንኑ መጽሐፍ “ዶን ኪሾት” በሚል ርዕስ ተርጉሞት ነበር፤ ይሁን እንጂ ያኛው ትርጉም ብዙም አይጥምም)
6.     “ሳቤላ”፣ ደራሲ ሄንሪ ውድ፣ ተርጓሚ ሀይለ ሥላሤ መሓሪ
7.     “እናት”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
8.     “ዩኒቨርሲቲዎቼ”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
9.     “አጎቴ ቫኒያ”፣ አንቶን ቼኾቭ
10.    “ሼርሎክ ሆምዝ”፣ ደራሲ ሰር አርተር ኮናን ዶይል፣ ተርጓሚ ዳኛቸው ተፈራ
11.     “ውቢት”፣ ደራሲ አልቤርቶ ሞራቪያ፣ ትርጉም ሺፈራው ጂሶ
12.    የካፒቴኑ ሴት ልጅ፡ ደራሲ አሌክሳንደር ፑሽኪን
13.    “ካፖርቱ”፣ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
14.    እንደ ሰው በምድር እንደ አሳ በባህር፡ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
15.    “ወንጀልና ቅጣት”፣ ደራሲ ፊዮዶር ዶስቶየቪስኪ፣ ተርጓሚ ካሳ ገብረህይወት እና ፋንቱ ሳህሌ
16.    “እንዲህ ሆነላችሁ”፣ ደራሲ ሩድያርድ ኪፕሊንግ፣ ተርጓሚ አረፈዐይኔ ሐጎስ
17.    “አሳረኛው”፣ ደራሲ ነጂብ ማህፉዝ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
18.    ሌባውና ውሾቹ፣ ደራሲ ነጂብ ማሕፉዝ፤
19.    “እፎይታ”፣ ደራሲ አሌክሳንደር ዱማስ ፔሬ፣
20.   “ጃኩሊን”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ
21.    “የደም ጎጆ”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ፣ ተርጓሚ ሌ/ኮሎኔል ጌታቸው መኮንን ሐሰን
22.   “አና ካሬኒና”፣ ደራሲ ሊዮ ቶልስቶይ፣
23.    “ሽማግሌውና ባህሩ”፣ ደራሲ አርነስት ሄሚንግዌይ፣
24.    “እሪ በይ አገሬ”፣ ደራሲ አላን ፒተን፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
25.    “የስዕሉ ሚስጢር”፣ ደራሲ ኦስካር ዋይልድ፣ ተርጓሚ ፋሲል ተካልኝ አደሬ
26.   “ጠልፎ በኪሴ”፣ ደራሲ ተውፊቅ አልሃኪም፣ ተርጓሚ መንግሥቱ ለማ
27.   “የእንስሳት እድር”፣ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል፣ ተርጓሚ ለማ ፈይሳ

===ዓለም አቀፍ የተረት መጻሕፍት===

1.       “ተረበኛው ነስሩዲን”፣ ደራሲ ኢድሪስ ሻህ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
2.     “አንድ ሺህ አንድ ሌሊት”፣ ወደ እንግሊዝኛ ተርጓሚ ሪቻርድ በርተን፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተፈሪ ገዳሙ
3.     “ጥንቸሉ ጴጥሮስ፣ ደራሲ ቤትሪክስ ፖተር፣
4.     “የኤዞፕ ተረቶች”፣ ደራሲ ኤዞፕ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
5.     “የግሪም ተረቶች”፣ ደራሲ የግሪም ወንድማማቾች፣ ተርጓሚ ዓለም እሸቱ

====ዘመን አይሽሬ የግጥም ስብስቦች====

1.      “ነቢዩ”፣ ገጣሚ ካህሊል ጂብራን
2.     የአሌክሳንደር ፑሽኪን ግጥሞች፣ ተርጓሚ አያልነህ ሙላቱ
3.     የዑመር ኸያም ሩባያቶች፣ ወደ እንግሊዝኛ ትርጉም በኤድዋርድ ፊዝጂራልድ፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተስፋዬ ገሠሠ
4.     ኢሊያድ እና ኦዲሴይ፣ ገጣሚ ሆሜር፣ ተርጓሚ ታደለ ገድሌ

==== ወቅታዊ የሽያጭ ሪከርድ ያስመዘገቡ መጻሕፍት (Best Sellers)====
1.      “የጡት አባት”፣ ደራሲ ማሪዮ ፑዞ
2.     “የሚስጢሩ ቁልፍ”፣ ደራሲ ኬን ፎሌት፣ ተርጓሚ ኤፍሬም እንዳለ
3.     “የዳቪንቺ ኮድ”፣ ደራሲ ዳን ብራውን፣
4.     “ሃሪ ፖተር እና የፈላስፋው ጠጠር”፣ ደራሲ ጄ.ኬ. ሬውሊንግስ፣
5.      “ሳዳም ሑሴን እና የባህረ ሰላጤው ቀውስ”፣ ደራሲ ባሪ ሩቢን፣
6.     “ሞገድ”፣ ደራሲ አርቪንግ ዋላስ፣
7.     “የኦዴሳ ፋይል”፣ ደራሲ ፍሬድሪክ ፎርስይዝ፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
8.     “ዘጠና ደቂቃ በኢንቴቤ”፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     አስራ አንዱ ውልዶች፣ ደራሲ ጄፍሪ አርቸር፤

=== ዓለም አቀፍ ተጽእኖን የፈጠሩ የፖለቲካና የፍልስፍና መጻሕፍት===

1.      “ካፒታል”፣ ደራሲ ካርል ማርክስ፣ (በቡድን ነው የተተረጎመው፡፡ የጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም አስተርጓሚ የነበሩት አቶ ግርማ በሻህ እና ደራሲ ስብሐት ገብረ እግዚአብሄር በተርጓሚዎቹ ውስጥ ይገኛሉ)፡፡
2.     “የኮሚኒስት ፓርቲ ማኒፌስቶ”፣ ደራሲ ካርል ማርክስና ፍሬድሪክ ኤንግልስ፣ ተርጓሚ “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት”
3.     “የሌኒን ምርጥ ስራዎች”፣ ደራሲ ቪላድሚር ሌኒን፣ ተርጓሚ “ኩራዝ”

=== ታዋቂ ግለ-ታሪኮችና የታሪክ ማስታወሻዎች===

4.     “ትንሿ መሬት”፣ ደራሲ ሊዮኒድ ብሬዥኔቭ፣ ተርጓሚ “ፕሮግሬስ የመጻሕፍት ማዘጋጃ ድርጅት”
5.     “የኦሽዊትዝ ሚስጥር”
6.     የአና ማስታወሻ፤ ደራሲ “አና ፍራንክ”፣ ተርጓሚ “አዶኒስ”
7.     “ፓፒዮ”፣ ደራሲ ሄንሪ ቻሬሬ
8.     “በረመዳን ዋዜማ”፣ ደራሲ ሙሐመድ ሀይከል፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     “የጽናት አብነት”፣ ሄለን ከለር

=== ሌሎች ኢ-ልብወለድ መጻሕፍት===
1.      “ጠብታ ማር”፣ ደራሲ ዴል ካርኒጌ፣ ተርጓሚ ባሴ ሀብቴና ደምሴ ጽጌ