Thursday, December 4, 2014

በአማርኛ የተተረጎሙ ታላላቅ መጻሕፍት



 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
የውጪ ደራሲያን የጻፏቸውን መጻሕፍት ወደ አማርኛ መተርጎሙን ማን እንደጀመረው በትክክል አላውቅም፡፡ ሆኖም የዶ/ር ሳሙኤል ጆንሰን ድርሰት የሆነው “ራሴላስ” በአማርኛ የተተረጎመ የመጀመሪያው የውጪ መጽሐፍ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ ከዚያም ክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል የትርጉም ስራዎችን በስፋት ተያይዘውት ነበር፡፡ ለምሳሌ ከበደ ሚካኤል የሼክስፒርን ሮሚዮና ጁሌት በ1940ዎቹ ተርጉመውት ነበር፡፡ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህንም በርካታ የሼክስፒር ስራዎችን በ1960ዎቹ ተርጉመዋል፡፡
  
  የአማርኛ የትርጉም ስራዎች እንደ አሸን የፈሉት ግን “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት” በ1970ዎቹ ከተቋቋመ በኋላ ነው፡፡ በዚያ ዘመን በተለይም ዘመን አይሽሬ የሚባሉ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ ስራዎች በብዛት ወደ አማርኛ ተመልሰዋል፡፡ ኢ-ልቦለድ ከሆኑትም መካከል የካርል ማርክስን “ዳስ ካፒታል”ን ጨምሮ በርከት ያሉ መጻሕፍት ተተርጉመዋል፡፡

በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ ደግሞ የትርጉም ስራው የዳኒኤላ ስቴልን፣ የሲድኒ ሸልደንንና የአርቪንግ ዋላስን ስራዎች ወደ አማርኛ በመመለሱ ላይ ነበር ያተኮረው፡፡ እስከ 1990ዎቹ መጀመሪያ ድረስ በብዛት ሲተረጎሙ የነበሩት ደግሞ የጃኪ ኮሊንስ ድርሰቶች ናቸው፡፡ አሁን ግን የትርጉም ስራው ቀዝቅዟል፡፡

   ለመሆኑ እስከ ዛሬ ድረስ በአማርኛ የተተረጎሙ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ በረከቶች የትኞቹ ናቸው? ይህንን ጥያቄ መመለስ ይከብዳል፡፡ ቢሆንም የቻልኩትን ያህል ለመዘርዘር እሞክራለሁ፡፡ ታዲያ በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት በመላው ዓለም ዝነኛ ለመሆን የበቁ ስራዎች ብቻ ናቸው፡፡ ለምሳሌ የነ ዳንኤላ ስቴል፣ ሲድኒ ሸልደንና ጃኪ ኮሊንስ ስራዎች በሀገራችን በብዛት ቢተረጎሙም በዓለም ዙሪያ ያላቸው ተነባቢነት እምብዛም ነው፡፡

    መጻሕፍቱን የምጠራቸው በአማርኛው ርዕሳቸው ነው፡፡ የዋናውን ደራሲ ስም እና የተርጓሚውንም ስም እጠቅሳለሁ፡፡ በአንዳንድ የተርጓሚዎችን ማንነት ለማወቅ ስቸገር ግን ዝም ብዬ አልፌአቸዋለሁ፡፡
(ማስታወሻ፡ ይህ ዝርዝር የሃይማኖት መጻሕፍትን አይመለከትም)፡፡

==== ዘመን አይሽሬ የልብወለድ መጻሕፍት (Classical Fictions)===

1.      “ነገም ሌላ ቀን ነው”፣ ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል፣ ተርጓሚ ነቢይ መኮንን
2.     “መከረኞች”፣ ደራሲ ቪክቶር ሁጎ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም (በህይወቴ ያነበብኩት ምርጥ የአማርኛ ትርጉም ስራ ይህኛው ነው)፡፡
3.     “የሁለት ከተሞች ወግ”፣ ደራሲ ቻርለስ ዲከንስ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም
4.     “የአገር ልጅ”፣ ደራሲ ሪቻርድ ራይት፣ ተርጓሚ ሳህለሥላሤ ብርሃነማሪያም
5.     “ዶን ኪኾቴ”፣ ደራሲ ሚጉኤል ሰርቫንቴስ፣ ተርጓሚ ዳምጤ አሰማኽኝ (ሌላ ሰው ይህንኑ መጽሐፍ “ዶን ኪሾት” በሚል ርዕስ ተርጉሞት ነበር፤ ይሁን እንጂ ያኛው ትርጉም ብዙም አይጥምም)
6.     “ሳቤላ”፣ ደራሲ ሄንሪ ውድ፣ ተርጓሚ ሀይለ ሥላሤ መሓሪ
7.     “እናት”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
8.     “ዩኒቨርሲቲዎቼ”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
9.     “አጎቴ ቫኒያ”፣ አንቶን ቼኾቭ
10.    “ሼርሎክ ሆምዝ”፣ ደራሲ ሰር አርተር ኮናን ዶይል፣ ተርጓሚ ዳኛቸው ተፈራ
11.     “ውቢት”፣ ደራሲ አልቤርቶ ሞራቪያ፣ ትርጉም ሺፈራው ጂሶ
12.    የካፒቴኑ ሴት ልጅ፡ ደራሲ አሌክሳንደር ፑሽኪን
13.    “ካፖርቱ”፣ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
14.    እንደ ሰው በምድር እንደ አሳ በባህር፡ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
15.    “ወንጀልና ቅጣት”፣ ደራሲ ፊዮዶር ዶስቶየቪስኪ፣ ተርጓሚ ካሳ ገብረህይወት እና ፋንቱ ሳህሌ
16.    “እንዲህ ሆነላችሁ”፣ ደራሲ ሩድያርድ ኪፕሊንግ፣ ተርጓሚ አረፈዐይኔ ሐጎስ
17.    “አሳረኛው”፣ ደራሲ ነጂብ ማህፉዝ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
18.    ሌባውና ውሾቹ፣ ደራሲ ነጂብ ማሕፉዝ፤
19.    “እፎይታ”፣ ደራሲ አሌክሳንደር ዱማስ ፔሬ፣
20.   “ጃኩሊን”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ
21.    “የደም ጎጆ”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ፣ ተርጓሚ ሌ/ኮሎኔል ጌታቸው መኮንን ሐሰን
22.   “አና ካሬኒና”፣ ደራሲ ሊዮ ቶልስቶይ፣
23.    “ሽማግሌውና ባህሩ”፣ ደራሲ አርነስት ሄሚንግዌይ፣
24.    “እሪ በይ አገሬ”፣ ደራሲ አላን ፒተን፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
25.    “የስዕሉ ሚስጢር”፣ ደራሲ ኦስካር ዋይልድ፣ ተርጓሚ ፋሲል ተካልኝ አደሬ
26.   “ጠልፎ በኪሴ”፣ ደራሲ ተውፊቅ አልሃኪም፣ ተርጓሚ መንግሥቱ ለማ
27.   “የእንስሳት እድር”፣ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል፣ ተርጓሚ ለማ ፈይሳ

===ዓለም አቀፍ የተረት መጻሕፍት===

1.       “ተረበኛው ነስሩዲን”፣ ደራሲ ኢድሪስ ሻህ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
2.     “አንድ ሺህ አንድ ሌሊት”፣ ወደ እንግሊዝኛ ተርጓሚ ሪቻርድ በርተን፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተፈሪ ገዳሙ
3.     “ጥንቸሉ ጴጥሮስ፣ ደራሲ ቤትሪክስ ፖተር፣
4.     “የኤዞፕ ተረቶች”፣ ደራሲ ኤዞፕ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
5.     “የግሪም ተረቶች”፣ ደራሲ የግሪም ወንድማማቾች፣ ተርጓሚ ዓለም እሸቱ

====ዘመን አይሽሬ የግጥም ስብስቦች====

1.      “ነቢዩ”፣ ገጣሚ ካህሊል ጂብራን
2.     የአሌክሳንደር ፑሽኪን ግጥሞች፣ ተርጓሚ አያልነህ ሙላቱ
3.     የዑመር ኸያም ሩባያቶች፣ ወደ እንግሊዝኛ ትርጉም በኤድዋርድ ፊዝጂራልድ፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተስፋዬ ገሠሠ
4.     ኢሊያድ እና ኦዲሴይ፣ ገጣሚ ሆሜር፣ ተርጓሚ ታደለ ገድሌ

==== ወቅታዊ የሽያጭ ሪከርድ ያስመዘገቡ መጻሕፍት (Best Sellers)====
1.      “የጡት አባት”፣ ደራሲ ማሪዮ ፑዞ
2.     “የሚስጢሩ ቁልፍ”፣ ደራሲ ኬን ፎሌት፣ ተርጓሚ ኤፍሬም እንዳለ
3.     “የዳቪንቺ ኮድ”፣ ደራሲ ዳን ብራውን፣
4.     “ሃሪ ፖተር እና የፈላስፋው ጠጠር”፣ ደራሲ ጄ.ኬ. ሬውሊንግስ፣
5.      “ሳዳም ሑሴን እና የባህረ ሰላጤው ቀውስ”፣ ደራሲ ባሪ ሩቢን፣
6.     “ሞገድ”፣ ደራሲ አርቪንግ ዋላስ፣
7.     “የኦዴሳ ፋይል”፣ ደራሲ ፍሬድሪክ ፎርስይዝ፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
8.     “ዘጠና ደቂቃ በኢንቴቤ”፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     አስራ አንዱ ውልዶች፣ ደራሲ ጄፍሪ አርቸር፤

=== ዓለም አቀፍ ተጽእኖን የፈጠሩ የፖለቲካና የፍልስፍና መጻሕፍት===

1.      “ካፒታል”፣ ደራሲ ካርል ማርክስ፣ (በቡድን ነው የተተረጎመው፡፡ የጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም አስተርጓሚ የነበሩት አቶ ግርማ በሻህ እና ደራሲ ስብሐት ገብረ እግዚአብሄር በተርጓሚዎቹ ውስጥ ይገኛሉ)፡፡
2.     “የኮሚኒስት ፓርቲ ማኒፌስቶ”፣ ደራሲ ካርል ማርክስና ፍሬድሪክ ኤንግልስ፣ ተርጓሚ “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት”
3.     “የሌኒን ምርጥ ስራዎች”፣ ደራሲ ቪላድሚር ሌኒን፣ ተርጓሚ “ኩራዝ”

=== ታዋቂ ግለ-ታሪኮችና የታሪክ ማስታወሻዎች===

4.     “ትንሿ መሬት”፣ ደራሲ ሊዮኒድ ብሬዥኔቭ፣ ተርጓሚ “ፕሮግሬስ የመጻሕፍት ማዘጋጃ ድርጅት”
5.     “የኦሽዊትዝ ሚስጥር”
6.     የአና ማስታወሻ፤ ደራሲ “አና ፍራንክ”፣ ተርጓሚ “አዶኒስ”
7.     “ፓፒዮ”፣ ደራሲ ሄንሪ ቻሬሬ
8.     “በረመዳን ዋዜማ”፣ ደራሲ ሙሐመድ ሀይከል፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     “የጽናት አብነት”፣ ሄለን ከለር

=== ሌሎች ኢ-ልብወለድ መጻሕፍት===
1.      “ጠብታ ማር”፣ ደራሲ ዴል ካርኒጌ፣ ተርጓሚ ባሴ ሀብቴና ደምሴ ጽጌ



Sunday, November 30, 2014

በልጅ እያሱ አሟሟት ዙሪያ


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
------
የልጅ እያሱ ሞት ይፋ የወጣው በህዳር ወር 1928 ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ወደ ማይጨው ከመዝመታቸው ሶስት ቀን አስቀድሞ ነው። በአሟሟታቸው ዙሪያ ከሚነገሩት መካከል

·        ልጅ እያሱ የተገደሉት ሀረር ውስጥ ነው::
·        ልጅ እያሱ የተገደሉት አዲስ አበባ ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ውስጥ ሲሆን የተቀበሩትም ከቤተ መንግሥቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከሚገኘው ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ክልል ነው::
·        ልጅ እያሱ የቀብራቸው ስነ-ስርዓት የተከናወነው ደብረ ሊባኖስ ነው::
·        ልጅ እያሱ የተቀበሩት ሰንዳፋ ውስጥ ነው የሚሉት ይገኙባቸዋል።

የልጅ እያሱን አሟሟት አውቃለሁ በማለት እማኝነታቸውን ከሰጡ ግለሰቦች መካከል አገልጋያቸው የነበሩ አዛውንት ኢጣሊያኖች አቤቶ እያሱን ከጋራሙለታ እስር ቤት ለማስወጣት ሙከራ አድርገው እንደነበር በመግለጽ እንዲህ ይላሉ።
 
 “የኢጣሊያ ወኪሎች አባጤናን ከግራዋ እስር ቤት ለማስወጣት ከሞከሩ ጀምሮ ልዑልነታቸው በእስር ቤቱ ክልል እየተከዙ ወዲያ ወዲህ ይንጎራደዱ ነበር። አንድ ቀን ምሽት አንዲት አውቶሞቢል ወደ እስር ቤቱ መጣች። እርሳቸውም ይፈሩት የነበረው ሰው መኖር አለመኖሩን ጠየቁ። በቀጣዩ ቀን “የመጡት አባ ሐና ብቻ ናቸው” አልኳቸው። ነገር ግን ጥቂት ዘግይቶ ሁለተኛዋ አውቶሞቢል ሁለት ሰዎችን አሳፍራ መጣች። ከሁለቱ አንዱ ፊታውራሪ ነበር። እስኪጨልም ቆይተው እያደቡ ወደ እስር ቤቱ ተጠጉ። መዝጊያው ሰፋፊ ስንጥቆች ያሉት በመሆኑ ልዑልነታቸው በስንጥቆቹ ውስጥ አዘውትረው ምራቃቸውን ጢቅ ይሉ ስለነበር ሲያነጣጥሩባቸው ሳያዩአቸው አልቀረም። በተኮሱባቸው ጊዜ የመስኮቱን መቃኖች ጨምድደው ጨበጡ። ኃይለኛ ስለነበሩ ቤቱን በሙሉ ያናጉትና የሚናድ መስሎኝ ፈርቼ ነበር። ተንገዳግደው ወለሉ ላይ ሲወድቁ ሰማሁ። ሬሳቸው በባቡር ተጭኖ ወደ አዲስ አበባ ከመወሰዱ በፊት ሁለቱ ነፍስ ገዳዮች እንደ ባላዛር ሬሳቸው ላይ ተጎንብሰው አጓሩ። ሬሳቸው አዲስ አበባ እንደደረሰ ከፍተኛ ባለስልጣን ለባላምባራስ አበበ አረጋይ አስረከቡ። እንግዲህ ሬሳቸው ለዘላለም ያረፈበትን ቦታ የሚያውቁት ባላምባራስ አበበ አረጋይ ብቻ ናቸው። ይሁንና እኒሁ ሰው ደግሞ በ1953 በተሞከረው የመንግሥት ግልበጣ ጊዜ የመከላከያ ሚኒስትር ሆነው ነበርና በአረንጓዴው የገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ታዛ ወለል ላይ ደማቸው ፈስሶ ሞቱ። አባ ሃና ጂማም ተመሳሳይ እጣ ገጠማቸው”።

    እንደ አዛውንቱ ምስክርነት ከሆነ አባ ሐና ጅማም ሆነ አበበ አረጋይ የልጅ እያሱን አስከሬን በተረካከቡበት ቦታ ላይ ስለተገደሉ ምስጢሩ አብሮ ሞቷል ማለት ነው።
ሌላኛዋ ለቤተ መንግሥቱ ቅርበት ያላቸው ሴት ደግሞ ለጎበዜ ጣፈጠ እንዲህ ብለው ነበር የተናገሩት (“አባ ጤና እያሱ” ከተሰኘው የጎበዜ ጣፈጠ ድርሰት የተወሰደ ነው)።

    “ዕለቱን አላስታውስም። ቢሆንም ልጅ እያሱ አርፈዋልና ቤተ መንግሥት እንድትመጡ የሚል መልዕክት ተላለፈ። እኛም ማልደን ወደ ቤተ መንግሥቱ ሄድን። አዲስ አበባ ውስጥ የምንገኝ ወይዛዝርትና መኳንንት ተሰብስበን ስንላቀስ ዋልን። ሬሳ ግን አልነበረም። እቴጌ መነን በጣም አዝነውና ተክዘው እንባቸውን ያፈሱ ነበር።  ጃንሆይ በርኖሳቸውን ገልብጠው ደርበው ወንድሜ ወንድሜ በማለት ያለቅሱ ነበር።”

ልጅ እያሱን በታሸገ ባቡር አሳፍሬ ወደ አዲስ አበባ ልኬአቸኋለሁ በማለት እማኝነታቸውን የሚሰጡት ብላቴን ጌታ ዶ/ር ሎሬንዞ ታዕዛዝ በበኩላቸው የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን ቄስ የነበሩ ገ/መድህን የተባሉ ግለሰብ እንዲህ በማለት ነግረውኛል ይላሉ።

“በቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን ትይዩ የዱክ ቤት ይባል በነበረው ህንጻ ሰገነት ላይ አንድ እጆቹን በሰንሰለት የታበተ ሰው ከቀትር በኋላ ዘወትር ሲመላለስ እናየው ነበር። ነገር ግን ጃንሆይ ወደ ጦርነቱ ከመዝመታቸው በፊት ሌሊቱን ጸሎተ ፍትሐት እንድናደርግ ታዘዝን። ሆኖም የሟቹን ሰው የክርስትና ስም የሚነግረን አልነበረም። ከዚያ በኋላ ያ ሰውዬ ይመላለስበት ከነበረው ሰገነት ላይ አልታየም። እኛም የሞቱት ልጅ እያሱ እንደሆኑ ተረዳን።

(ምንጭ፡- ጎህ መጽሄት፣ ቅጽ 1 ቁጥር 5፣ ጥቅምት 1993፣ ገጽ 6/22)
-----------------
ለዚሁ መጽሄት ቃለ-ምልልስ የሰጡት የልጅ እያሱ የልጅ ልጅ ፕሮፌሰር ግርማ ዮሐንስ እያሱ ቄስ ገ/መድሕን የተባሉት ሰው ከሰጡት ምስክርነት ጋር የሚጣጣም ቃል አሰምተዋል። ፕሮፌሰር ግርማ እንዳሉት ልጅ እያሱ በስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ባለው የዱክ ቤት (አሁን Law Faculty ዋና ህንጻ የሆነው) መታሰራቸው እውነት ነው። “አጼ ኃይለ ስላሴ ወደ ማይጨው ሀሙስ ከመዝመታቸው በፊት ማክሰኞ ሌሊት ልጅ እያሱ ተገድለው አሁን የዩኒቨርሲቲው የእግር ኳስ ሜዳ ከሆነውና ያኔ የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን አጸድ ከነበረው ስፍራ ተቀብረዋል” ይላሉ ፕሮፌሰር ግርማ።
---------------
አፈንዲ ሙተቂ
ሰኔ 22/2005
ሀረር- ምስራቅ ኢትዮጵያ

Friday, November 28, 2014

የትግል ስም (Nom De Guerre)




ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

===ለመግቢያ ያህል====

    “የትግል ስም” ቃሉ እንደሚያመለክተው በትግል ዓለም ውስጥ ላለ ሰው ነው የሚያገለግለው፡፡ ታጋዩ በትግል ዓለም ውስጥ እያለ የሚጠቀምበት መጠሪያው ነው፡፡ ታጋዮች የትግል ስምን የሚጠቀሙት በልዩ ልዩ ምክንያቶች ነው፡፡ ዋነኛው ምክንያት ግን ታጋዩ በእውነተኛ ስም ሲጠቀም ሊደርስበት ከሚችል አደጋ ለመከላከል የሚል ነው፡፡
     
የትግል ስም እንደ ብዕር ስም በሚስጢራዊነት አይያዝም፤ ሰውዬው ድሮ የሚታወቅበትን ስም ተክቶ በስራ ላይ የሚውል ነው፡፡ ታጋዩ ወደ ትግል ዓለም ከገባ በኋላ የሚያገኛቸው የትግል ጓዶች በትግል ስሙ ነው የሚጠሩት፡፡ በመታወቂያም ሆነ በሌሎች ሰነዶች ጥቅም ላይ የሚውለውም የትግል ስም ነው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ ትግሉን በድል ካጠናቀቀ በኋላም በአብዛኛው በትግል ስሙ መገልገሉን ሲቀጥልበት ይታያል፡፡

   የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅም ላይ ያለው ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ ሆኖም የሩሲያ ኮሚኒስቶች በትግል ስም በብዛት በመጠቀም ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ እንደ ቭላድሚር ሌኒን፣ ጆሴፍ ስታሊን፣ ሊኦን ትሮትስኪ፣ ሉሊ ማርቶቭ ያሉ ስሞች በሙሉ የትግል ስሞች ናቸው፡፡ በሌሎች ሀገሮች የነበሩ ኮሚኒስቶችም በትግል ስም በብዛት ይጠቀሙ ነበር፡፡ ሆ ቺ ሚን፣ ኪም ኢል ሱንግ፣ ቼ ጉቬራ የመሳሰሉ መጠሪያዎች የትግል ስሞች ናቸው (የቼ ጉቬራ ትክክለኛ ስም “ኧርነስቶ ጉቬራ” ነው፤ የኪም ኢል ሱንግ ትክክለኛ ስም “ኪም ሱንግ ቹ” ነው)፡፡

====የትግል ስም በኢትዮጵያ===

   የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በስራ ላይ ያዋለው ኢትዮጵያዊ ማን እንደሆነ በትክክል አይታወቅም፡፡ ሆኖም ከተማሪዎች ንቅናቄ የፈለቁት ወጣቶች የፋኖነት ህይወት በጀመሩበት ዘመን በብዛት ስራ ላይ እንደዋሉት ይታወቃል፡፡ ታዲያ እነዚያ ፋኖዎች የትግል ስምን የሚጠቀሙበት ምክንያትና ስሙን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዘይቤ አንድ ወጥ አልነበረም፡፡ በህቡዕ እና በትጥቅ ትግል መንግሥትን ለመለወጥ የሚታገሉ ድርጅቶች ከተመሰረቱ በኋላ በጣም ጎልብቶ የመጣው የትግል ስም አጠቃቀም ልማድም እንደ ፓርቲው ይለያያል፡፡ ከዚህ በማስከተልም በቀደምት ድርጅቶች ውስጥ ይሰራበት የነበረውን ልማድ በአጭሩ እናወሳለን፡፡

1.      ጀብሃ እና ሻዕቢያ

ጀብሃ እና ሻዕቢያ የትግል ስምን የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ አልተመዘገበም (ወይም አላነበብኩም)፡፡ ሆኖም ሁለቱም ፓርቲዎች የሚስጢር ስም የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ በስፋት ይታወቃል፡፡ በተለይም ታጋዮቹ ለየት ያለ ተልዕኮ በሚፈጽሙበት ወቅት በሚስጢር ስም እንዲጠቀሙ ይደረጋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጀብሃና ሻዕቢያ ዘንድ ታጋዩን በቅጽል ስም መጥራት በጣም የተለመደ ነው፡፡ ለምሳሌ የጀብሃው “መሐመድ ቺክኒ”፣ የሻዕቢያዎቹ “ወልደ ዲንክል”፣ “ተክላይ አደን”፣ “ሀይሌ ጀብሀ” ይጠቀሳሉ፡፡ “የማነ ጃማይካ” የሚባለው የህወሐት ታጋይም ከድሮ የሻዕቢያ አባል በነበረበት ዘመን ሲጠራበት በነበረው ቅጽል ነው የሚታወቀው፡፡   

2.     ህወሐት

ህወሐት በትግል ስም የመጠቀም ሰፊ ልማድ አለው፡፡ በትጥቅ ትግሉ ዘመን ፓርቲው እያንዳንዱ ታጋይ በትግል ስም እንዲጠቀም ያደርግ ነበር፡፡ እነዚያ ታጋዮች ከትጥቅ ትግሉ ፍጻሜ በኋላም በትግል ስማቸው መጠራታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በዚህ ረገድ ከፓርቲው የተገለሉትም ሆነ በፓርቲው ውስጥ ያሉት ተመሳሳይ መንገድ እየተከተሉ ነው፡፡

ህወሐቶች የትግል ስም የሚመርጡት ስማቸውን ሙሉ በሙሉ በመቀየር አይደለም፡፡ የታጋዩ የልደት ስም ብቻ ነው የሚለወጠው እንጂ የአባቱ ስም አይቀየርም፡፡ ከታዋቂ የህወሐት ሰዎች መካከል የሚከተሉትን ከትግል ስማቸው ጋር መጥቀስ ይቻላል፡፡

1.      እምባዬ መስፍን= ስዩም መስፍን
2.     ዘርዑ ገሠሠ= አግዓዚ ገሠሠ
3.     መሐሪ ተኽለ= ሙሴ ተኽለ
4.     አምሀ ጸሐየ= አባይ ፀሐየ
5.     ዮሐንስ ገ/መድህን= ዋልታ ገ/መድህን
6.     ስዕለ አብርሃ= ስዬ አብርሃ
7.     ወልደስላሤ ነጋ= ስብሐት ነጋ
8.     ለገሰ ዜናዊ= መለስ ዜናዊ
9.     ራስወርቅ ቀጸላ= አታኽልቲ ቀፀላ
10.    ገሰሰው አየለ= ስሁል አየለ
11.     መሐመድ ዩኑስ= ሳሞራ ዩኑስ
12.    ዮሐንስ እቁባይ= አርከበ እቁባይ
13.    ሐዱሽ አርኣያ= ሀየሎም አርኣያ

    ህወሐቶችም እንደ ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን በቅጽል ስም የመጥራት ልማድም አላቸው፡፡ ለምሳሌ ከህወሐት ታጋዮች የሚበዙት ሙሉጌታ ገ/ህይወትን “ጫልቱ”፣ ሰለሞን ተስፋዬን “ጢሞ”፣ ጄኔራል አበበ ተክለ ሀይማኖትን “ጀቤ”፣ ጄኔራል አብርሃ ወልደማሪያምን “ኳርተር”፣ ካሳ ገብረመድህንን “ሸሪፎ”፣ አብረሃ ታደሰን “መጅሙእ”፣ ጸጋይ በርሄን “ሀለቃ”፣ ጄኔራል ታደሰ በርሄን “ጋውና” እያሉ ነው የሚጠሩት፡፡ ግንቦት 20/1983 ከአዲስ አበባ ሬድዮ ጣቢያ “የዘመናት የህዝብ ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሰራዊት…” በማለት ያወጀውን ታጋይ በእውነተኛ ስሙ የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው፡፡ የታጋዩ ቅጽል ስም “ላውንቸር” ስለመሆኑ ግን ብዙዎቻችን እናውቃለን፡፡
 
    ከዚህ በተጨማሪ ህወሐትና ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን “ወዲ እገሌ” (የእገሌ ልጅ) እያሉ በሰሜኑ የሀገራችን ስም በሚሰራበት ባህላዊ ዘይቤ መጥራትን ያዘወትራሉ፡፡ በኦፊሴላዊ ደብዳቤዎች ጭምር “ወዲ እገሌ” የሚለውን ልማድ ሲጠቀሙ ይስተዋላል (በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ይፋ የሆኑትን የአቶ ኢሳያስና የአቶ መለስን ደብዳቤዎች አስታውሷቸው)፡፡

3.     መኢሶን

የመኢሶን ሰዎች በትግል ላይ በነበሩበት ወቅት በልደት ስማቸው ነው የሚጠቀሙት፡፡ ሆኖም ከዋነኛ ስማቸው በተጨማሪ በሚስጢር ስምም ይገለገሉ እንደነበር ከልዩ ልዩ ሰነዶች የተገኘው መረጃ ያረጋግጣል፡፡ በዚህ መሰረት የመኢሶን መስራቾች ከሚታወቁበት የሚስጢር ስሞች የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡
a.     ሀይሌ ፊዳ= መላኩ
b.     ነገደ ጎበዜ= ነጋልኝ
c.     አብዱላሂ ዩሱፍ= አደም
d.     አንዳርጋቸው አሰግድ= ወልዴ
e.     ፍቅሬ መርዕድ= ሳሙኤል
f.      ከበደ መንገሻ= ነጋ
g.     ሲሳይ ታከለ= አሸናፊ
h.     ንግስት አዳነ= አይዳ
i.      ተረፈ ወልደጻዲቅ= ሚካኤል

ታዲያ እነዚህ ስሞች ሚስጢራዊ ደብዳቤ በሚጻፍበት ወቅት ወይም ሚስጢራዊ ስብሰባ በሚካሄድበት ጊዜ ብቻ ነው የሚያገለግሉት፡፡ መኢሶኖች በመታወቂያም ሆነ በፓስፖርት የሚገለገሉት በዋነኛ ስማቸው ነው እንጂ በሚስጢር ስም አይደለም፡፡

4.     ኢህአፓ

ኢህአፓዎችም በትግል ላይ ሳሉ ዋነኛ ስማቸውን በመተው በፓርቲው በሚሰጣቸው ስም ይገለገሉ ነበር፡፡ ፓርቲውን ወክለው በሚገኙበት መድረክ ሁሉ በዚያው ስም ነበር የሚጠቀሙት፡፡ ለታጋዮቹ የትግል ስም የሚሰጥበት ዘይቤ ግን አንድ ወጥ አይደለም፡፡ አንዳንድ ታጋዮች የልደት ስማቸውን ብቻ ይለውጡና ሌላ ቅጥያ ሳያስከትሉበት በዚያው ይጠራሉ (ለምሳሌ “ጋይም” እና “አያልነሽ”ን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ አንዳንዶች ግን የአባታቸውን ስም ጭምር ይለውጣሉ፡፡ ከዚህ ሌላም ብዙዎቹ የኢህአፓ ታጋዮች ከትግሉ ዓለም ከተገለሉ በኋላ ወደ ቀድሞ ስማቸው ሲመለሱ ይታያል፡፡ ከኢህአፓ አባላት የትግል ስሞች የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡

a.     ክፍሉ ታደሰ= ታዬ አስራት
b.     መላኩ ተገኝ= ያፌት
c.     ገብረ እግዚአብሄር ወልደሚካኤል= ጋይም
d.     የዓለም ገዥ ከበደ= አያልነሽ
e.     መርሻ ዮሴፍ= በላይነህ ንጋቱ
  
በነገራችን ላይ ድሮ የኢህአፓ ታጋዮች የነበሩት የአሁኖቹ የኢህዴን/ብአዴን ዋነኛ ባለስልጣናት በትግል ስማቸው ነው የሚጠሩት፡፡ እንደምሳሌም መብራቱ ገ/ህይወት (በረከት ስምኦን)እና ፍቅሩ ዮሴፍን (ህላዌ ዮሴፍ) መጥቀስ ይቻላል፡፡ ጌታቸው ጀቤሳ በበኩሉ ለረጅም ጊዜ በትግል ስሙ ሲጠቀም ከቆየ በኋላ ከኢህዴን ሲወጣ “ያሬድ ጥበቡ” የተሰኘውን እውነተኛ ስሙን መጠቀምን መርጧል፡፡

5.     ኦነግ
 
 ከላይ የጠቀስኳቸው ድርጅቶች የትግል ስምን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዋነኛ ምክንያት የታጋዮቻቸውንና ደህንነት ለማስጠበቅ በሚል ነው፡፡ በተለይም ታጋዩ በተወለደበት አካባቢ ለውጊያም ሆነ ለሌላ ተልዕኮ የሚሰማራ ከሆነ በዋነኛ ስሙ ቢጠቀም ህይወቱ አደጋ ላይ ይወድቃል ተብሎ ስለሚታመን ነው በትግል ስም እንዲጠቀም ሲደረግ የነበረው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ በትግል ስም ቢጠቀም በወላጆቹና በሌሎች ዘመዶቹ ላይ አደጋ እንዳይደርስባቸው ለመከላከል ይረዳል የሚል ምክንያት ከድርጅቶቹ ይቀርብ ነበር፡፡

    የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ባህል ግን ከዚህ ይለያል፡፡ በዚህ ድርጅት ውስጥ ያለ ታጋይ የትግል ስም እንዲጠቀም የሚደረገው በዋነኛነት ለታጋዩ ደህንነት ተብሎ አይደለም፡፡ ከታጋዩ ደህንነት በላይ ለድርጅቱ አንድነት ጠቃሚ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ የኦነግ ሰዎች ታጋዮቻቸው በትግል ስማቸው ቢጠቀሙ ሀይማኖትና ክፍለ ሀገርን አስታክኮ የሚመጣ መከፋፈልን ለመከላከል ይረዳል በማለት ያምናሉ፡፡ አንድ ታጋይ በስሙ ብቻ ተለይቶ ጥቃት እንዳይደርስበት ለመታደግም ጠቃሚ ነው በማለት ያስረዳሉ፡፡ 
     በዚህም መሰረት የኦሮሞ ስም የሌለው ታጋይ (አሕመድ፣ አብደላ፣ አበበ፣ ከበደ ወዘተ… በመሳሰሉት የሚጠራ) ወደ ድርጅቱ ሲመጣ ቀዳሚ ስሙን ይተውና በኦሮሞ ስም እንዲጠራ ይደረጋል፡፡ የታጋዩ የአባት ስም ኦሮምኛ ካልሆነ እርሱንም ይቀይራል፡፡ ታዲያ ታጋዩ የአባቱን ስም የሚመርጠው በዘፈቀደ አይደለም፡፡ የዘረግ ሀረጉን ወደላይ ሲቆጥር መጀመሪያ የሚመጣበትን የኦሮሞ ስም (የኦሮሞ ስም ያለው ቅመ-አያት የሚጠራበትን) ነው እንደ አባቱ ስም የሚገለገልበት፡፡ የአባቱ ስም ኦሮምኛ ከሆነ (ለምሳሌ እንደ ዮሐንስ ለታ) የራሱን ስም ብቻ ነው የሚቀይረው፡፡ ታጋዩ ይዞት የመጣው ሰው ሙሉ በሙሉ ኦሮምኛ ከሆነ ግን በስሙ ላይ የሚደረግ ለውጥ የለም (እንደ ምሳሌም ባሮ ቱምሳ፣ ኢብሳ ጉተማ፣ አባቢያ አባጆብር የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ ሆኖም ጥቂት የኦነግ ሰዎች ይህንን ልማድ አልተከተሉም፡፡ ከዚህ አሰራር ጋር በማይጣጣም መንገድ ነው የትግል ስማቸውን የመረጡት፡፡ እንደ ምሳሌም በተከታታይ የኦነግ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡትን በሪሶ ዋቤ፣ ገላሳ ዲልቦ እና ዳውድ ኢብሳን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ድርጅቱን ከውጪ ሀገር የተቀላቀሉትም እንደ አዲስ የትግል ስም ሲሰጣቸው አይታይም (ለምሳሌ ጣሃ አብዲ፣ በያን አሶባ ወዘተ.. ይጠቀሳሉ)፡፡ ከታዋቂ የኦነግ ሰዎች መካከል የጥቂቶቹ የትግል ስም እንደሚከተለው ነው፡፡

a.     አብዱልከሪም ኢብራሂም= ጃራ አባገዳ (ከኦነግ በልዩነት ወጥቶ “የኦሮሞ ነጻነት እስላማዊ ግንባር” የተሰኘውን ድርጅት ቢመሰርትም ከኦነግ መስራቾችም አንዱ ነበር)
b.     መገርሳ በሪ= በሪሶ ዋቤ
c.     ዮሐንስ በንቲ= ገላሳ ዲልቦ
d.     ፍሬው ኢብሳ= ዳውድ ኢብሳ
e.     ቃሲም ሑሴን= ነዲ ገመዳ
f.      ዮሐንስ ለታ= ሌንጮ ለታ
g.     አብረሃም ለታ= አባጫላ ለታ
h.     ዮሐንስ ኖጎ= ዲማ ኖጎ
i.      አብዱልፈታህ ሙሳ= ቡልቱም ቢዮ
j.      ጀማል ሮበሌ= ጉተማ ሀዋስ
-------------
መጋቢት 28/2006
አፈንዲ ሙተቂ