Thursday, October 30, 2014

ሁለት የሀረር ተረቶች



 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
“ሀረር ጌይ” በተሰኘው መጽሐፌ ውስጥ “ሀረር የባግዳድ እህት ናት” የሚል የረጅም ጊዜ ልማድ እንዳለ አጫውአችኋለሁ፡፡ ይህም አመለካከት የመጣው ሁለቱ ከተሞች የሚመሳሰሉ በመሆናቸው ነው፡፡ ከተሞቹን ከሚያመሳስሏቸው የህይወት ዘርፎች መካከል አንዱ እምቅ የስነ-ቃል ሀብታቸው ነው፡፡ ከነዚህ የስነ-ቃል ሀብቶች ቀዳሚ ሆኖ የሚጠቀሰው ተረት ነው፡፡ የባግዳድ ተረቶችን በ“አንድ ሺህ አንድ ሌሊት” በኩል አንብበናቸዋል፡፡ የሀረር ተረቶች ግን በመጽሐፍ ያልተሰበሰቡ በመሆናቸው ከብዙኃኑ አንባቢ ዘንድ ሊደርሱ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ እነርሱንም በመጽሐፍ የሚሰበስብ የብዕር ጀግና ያስፈልገናል፡፡

በዚህ ጽሑፍ ሁለት የሀረር ተረቶችን አጋራችኋለሁ፡፡ ሁለቱንም ተረቶች በልጅነቴ የማውቃቸው ቢሆንም በሀረር ከተማ ቆይታዬ በአዲስ መልክ ሰምቼአቸዋለሁ፡፡  

የሓኪም ጋራ መሰንጠቅ

በጥንት ዘመን ሀረር በድርቅ ተመታች፡፡ በድርቁ ሳቢያም ምንጮቿና ወንዞቿ ደረቁ፡፡ አንድ “ኤላ” (የውሃ ጉድጓድ) ግን በተአምራዊ መንገድ ከመጥፋት ተረፈ፡፡ ይሁንና መገኛው ያልታወቀ ትልቅ ዘንዶ ከጉድጓዱ አፋፍ ተቀምጦ “ኤላው የኔ ነው” በማለቱ ከኤላው ውሃ መቅዳት አስቸጋሪ ሆነ፡፡ የሀረር ህዝብ ከኤላው ውሃ መቅዳት ከፈለገ በየዓመቱ አንዲት ቆንጆ ወጣት መገበር እንዳለበት ዘንዶው በአዋጅ አስታወቀ፡፡ የመጠጥ ውሃ ማግኘት የቸገረው የሀረር ህዝብም አማራጭ ሲያጣ ለዘንዶው በመገበር ከኤላው ውሃ ለመቅዳት ተገደደ፡፡

ለዘንዶው የምትሰጠው ልጅ በእጣ ነው የምትወሰነው፡፡ እጣው የሚወጣበት ሁኔታ ግን ፍትሐዊ አልነበረም፡፡ የሀብታምና የባለስልጣናት ልጆች በስውር ዘዴ ከእጣው ውጪ እንዲሆኑ ይደረግና የድሃ ልጆች ብቻ እየተመረጡ ለዘንዶው ይሰጣሉ፡፡ ድሆቹ ይህንን በደል ቢያውቁትም ከሀብታሞቹ ጋር መፎካከር ስለማይችሉ ልጆቻቸውን ለዘንዶው እየገበሩ እምባቸውን መርጨት ግዴታ ሆነባቸው፡፡

ታዲያ በአንድ ዓመት ልጅ የመገበሩ እጣ የደረሰው ለአንዲት “ተቂይ” (አላህን የምትፈራ) ሴት ነው፡፡ ያቺ ሴት አንዲት ልጅ ብቻ ነበራት፡፡ ልጅቷንም ያገኘችው በስተእርጅና ሲሆን ባለቤቷ ከልጅቷ መወለድ በኋላ ሞቶባታል፡፡ በመሆኑም ሴትዮዋ አንድዬ ልጇን እንደ እናትና እንደ አባት ሆና ነው ያሳደገቻት፡፡  እንግዲህ እነዚያ እጣ አውጪዎች ሴትዮዋ በስተእርጅና ያገኛትንና በድህነት ያሳደጋችትን ያቺኑ ልጅ ለዘንዶው እንድትገብር ነው የፈረዱት፡፡

   ይሁንና ሴትዮዋ ልጇን ለዘንዶው አላስረክብም አለች፡፡ የሰፈሯ ሰዎች “እምቢ ካልሽ እኮ ዘንዶው አንቺንም ጨምሮ ይበላሻል” እያሉ ቢያስፈራሯትም ሴትዮዋ ወይ ፍንክች በማለት በቃሏ ጸናች፡፡ ሰዎቹም “በቃ! ውርድ ከራሳችን!! ዘንዶው ቢበላሽ ተጠያቂ አይደለንም” በማለት ብቻዋን ተዋት፡፡ ወደ ዘንዶው ሄደውም ስለሴትዮዋ እምቢተኝነት ነገሩት፡፡ ከዚያም በየቤታቸው ሆነው ተከታዩን ነገር መጠባበቅ ጀመሩ፡፡ ሴትዮዋም ልጇን ከምታስረክብበት ዕለት በፊት ባለው ምሽት የዘንዶውን ጭካኔና የእጣ አውጪዎቹን አሻጥር እያነሳች ፈጣሪዋን ስትለምን አደረች፡፡ በማግስቱም ከቤቷ ቁጭ ብላ ዘንዶው የሚያመጣውን መቅሰፍት መጠባበቅ ጀመረች፡፡

 ሴትዮዋ ልጇን የምታስረክበው ከጧቱ በሶስት ሰዓት ገደማ የነበረ ቢሆንም ዘንዶው በሰዓቱ ግብሩን አላገኘም፡፡ በዚህም የተናደደው ዘንዶ ሴትዮዋን ከነልጅቷ ሊውጣት እጅግ በሚያስፈራ ግርማ ወደ ቤቷ መጓዝ ጀመረ፡፡ የሰፈሩ ሰዎችም “ሊበላት ነው፤ ሴትዮዋ አለቀላት!” እያሉ በአድናቆትና በተመስጦ ትርዒቱን ይመለከቱ ገቡ፡፡

ዘንዶው አቧራውን እያቦነነ ከሴትዮዋ ቤት አጠገብ ደረሰ፡፡ ሴትዮዋንም ሊውጣት መንደርደር ጀመረ፡፡ ፍላጎቱን ከመፈጸሙ በፊት ግን ፈጣሪ ውጥኑን አከሸፈበት!! እጅግ ግዙፍ የሆነ ንስር (አሞራ) ከሀረር በስተሰሜን አቅጣጫ በመምጣት ዘንዶውን ከመሬት ላይ “ላጥ” አድርጎ አነሳው፡፡ ንስሩ ዘንዶውን ወደ ሰማይ በማውጣት ላይ ሳለም የዘንዶው ጭራ ሀረርን በደቡብ በኩል የከበበውን የሀኪም ጋራን በሁለት ቦታ ከፈለው፡፡
 
  ያ ከይሲ ዘንዶ ፈጣሪዋን የምትፈራው ሴትዮ ባደረገችው ጸሎት ተወገደ፡፡ በሀረር ከተማ ላይ የተጣለው ልጅን የመገበር ግዴታም ለዘልዓለሙ ተነሳ!! ይሁንና ያኔ በዘንዶው ጭራ የተከፈሉት ሁለቱ የሐኪም ጋራ ኮረብቶች በአንድ ላይ ሳይመለሱ እስከዚህ ዘመን ድረስ ዘለቁ፡፡

አሚር ሆይ! አንተ “ኸይሩ”ን ብቻ አስብ፤ “ለሸሩ” ባለቤት አለውና!!
------
በጥንት ዘመን አንድ ቅን ሰውዬ በሀረር ከተማ ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ የመጀመሪያው ልጁ ርህሩህና የዋህ የነበረ ሲሆን ሁለተኛው ልጁ ግን ተንኮል እየፈጠረ ሰዎችን ማሞኘትና መሳቅ ይወድ ነበረ፡፡ አባትዬው ትንሹን ልጅ ቢመክረው አልሰማ እያለ አስቸገረው፡፡ ስለዚህ በትንሹ ልጅ ተስፋ የቆረጠው አባት ዘወትር ትልቁን ልጅ እየጠራው “ልጄ ሆይ! አንተ ደጉን ብቻ አስብ፡፡ ለተንኮል ባለቤት አለውና” የሚል ምክር ይሰጠው ነበር፡፡ አባት በዚህም ሳያበቃ ለትልቁ ልጅ “ዓሊ ኸይሮ” (ቅን አሳቢው ዓሊ) የሚል ቅጽል አወጣለት፡፡ ትንሽየውን ግን “ዓሊ ሸርሮ” (ተንኮለኛው ዓሊ) በማለት ሰየመው፡፡
 
   ከጊዜ በኋላ አባት የአዱኛውን ዓለም ተሰናበተ፡፡ በዚህም የተነሳ ልጆቹ ተቸገሩ፡፡ ኑሮ በጣም ከበዳቸው፡፡ በመሆኑም ወደ ሀረሩ አሚር ሄደው በችግር መቆራመዳቸውን ነገሩት፡፡ አሚሩ በአጋጣሚ የቤተ መንግሥት ከብቶችን የሚጠብቅ ሰው ይፈልግ ነበርና ወንድማማቾቹ ለእረኝነት እንዲቀጠሩ ጠየቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹ ለስራው የሚሰጣቸውን ምንዳ ሲጠይቁት ከሚበሉት ምግብና ከሚለብሱት ልብስ በተጨማሪ በዓመቱ መጨረሻ ላይ አንዲት ጊደር እንደሚያገኙ አሳወቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹም ከአሚሩ የቀረበላቸውን ጥያቄ በደስታ ተቀበሉትና ስራቸውን ጀመሩ፡፡

ወንድማማቾቹ በመቶዎች የሚቆጠሩትን የአሚሩን ከብቶች “አው-ሓኪም”፣ “አቦከር” እና “ሸድዳ ዋ መድዳ” ወደሚባሉት ተራሮች እያሰማሩ በትጋት ማገዱን ተያያዙት፡፡ ስራቸውን በደህና ሁኔታ እያከናወኑ ዓመቱን አገባደዱት፡፡ የዓመቱ መጨረሻ እየተቃረበ ሲመጣ ግን የ“አሊ ሸርሮ” ልብ በግለኝነት መመታት ጀመረች፡፡ ለምንዳ የምትሰጣቸውን ጊደር ጉዳይ ሲያስብ አዕምሮው በስስት ተወጠረ፡፡ በመሆኑም “ወንድሜን ገድዬው ጊደሪቱን የግሌ ማድረግ አለብኝ” በማለት ወሰነ፡፡ እቅዱንም በአው ሓኪም ተራራ ላይ ለመፈጸም ቆረጠ፡፡

ወንድማማቾቹ ከብቶቹን ወደ “ሓኪም” ተራራ በወሰዱበት በአንደኛው ቀን “አሊ ሸርሮ” ለወንድሙ “አንተ ከዚህ ሆነህ ከብቶቹን ጠብቅ፤ እኔ ተራራው ላይ ወጥቼ ለምለም ሳር እንዳለ ልይና ልመስ” አለው፡፡ “አሊ ኸይሮ”ም በቀረበለት ሃሳብ ተስማምቶ ከብቶቹን ለብቻው መጠበቅ ጀመረ፡፡ “አሊ ሸርሮ” ከተራራው ላይ እንደ ወጣ ትልቅ ድንጋይ አንቀሳቅሶ ወንድሙ ወዳለበት አቅጣጫ ቁልቁል ለቀቀው፡፡ ድንጋዩ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ ወረደ፡፡ ከ“አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ ግን ወደ ወርቅነት ተቀየረ፡፡ “አሊ ኸይሮ” በዚህ ተአምር ተገረመ፡፡ “ወደ ወርቅነት የተቀየረው ድንጋይ እኔና ወንድሜ ሀብታም እንድንሆን ዘንድ ከአላህ የተሰጠን ነው” በማለት በደስታ ፈጣሪውን አመሰገነ፡፡ የተፈጠረውንም ተአምር ለወንድሙ ለመንገር በጉጉት ይጠባበቅ ጀመር፡፡
 
 “አሊ ሸርሮ” በበኩሉ “አሊ ኸይሮ በድንጋይ በመገደሉ “ጊደሪቱ የኔ ብቸኛ ሀብት ትሆናለች” እያለ በደስታ ከተራራው ወረደ፡፡ ወንድሙ ወደነበረበት ቦታ ሲደርስ ግን ያልጠበቀውን ነገር አየ፡፡ “ይህ ወርቅ ከየት ነው የመጣው?” በማለትም ወንድሙን ጠየቀው፡፡ አሊ ኸይሮም “አንድ ትልቅ ድንጋይ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ መጥቶ እኔ ጋ ሲደርስ ይህንን ወርቅ ሆነ” በማለት መለሰለት፡፡ “አሊ ሸርሮም “ድንጋዩ የተንከባለለው ከስሩ የነበረውን ለምለም ሳር ለማየት ብዬ ስላንቀሳቀስኩት ነው፤ እዚህ ደርሶ ወደ ወርቅ ከተቀየረ እኔም የራሴ ወርቅ ሊኖረኝ ይገባል፡፡ ስለዚህ አንተም በተራህ ወደ ተራራው ውጣና ሌላ ድንጋይ አንከባልልኝ” አለው፡፡

“አሊ ኸይሮ”ም ከወንድሙ የሰማውን ሳይጠራጠር ወደ ተራራው ወጥቶ ትልቅ ድንጋይ አነሳና “አሊ ሸርሮ” ወደነበረበት አቅጣጫ አንከባለለው፡፡ ይሁንና ድንጋዩ ወደ ወርቅነት ሳይቀየር “አሊ ሸርሮ”ን ጭፍልቅ አድርጎ ገደለው፡፡ “አሊ ኸይሮ” ከተራራው ወርዶ ወንድሙ ወደነበረበት ስፍራ ሲሄድ ወንድሙ ሞቶ አገኘው፡፡ በዚህም በጣም ደነገጠ፡፡ ወደ ሀረሩ አሚር ሄዶም የተከሰተውን ሁሉ አንድ በአንድ ነገረው፡፡ ሆኖም አሚሩ ሊያምነው አልቻለም፡፡ “ወንድምህን ራስህ ነህ የገደልከው” በማለትም ከሰሰው፡፡ በመሆኑም “ነፍስ ያጠፋ ሰው ይገደል” በሚለው የሀረር ከተማ ጥንታዊ ህግ መሰረት በድንጋይ ተጨፍልቆ እንዲሞት ተፈረደበት፡፡
 
“አሊ ኸይሮ”ም ፍርዱ ሊፈጸምበት ወደ “ሐኪም” ተራራ ግርጌ ተወሰደ፡፡ ከተራራው ላይ ትልቅ ድንጋይ ተንዶ ቁልቁል ተወረወረበት፡፡ ይሁንና ድንጋዩ “አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ እንደገና ወርቅ ሆኖ ቁጭ አለ፡፡ የቅጣቱን አፈጻጻም ለማየት በስፍራው ተሰብስቦ የነበረው የሀረር ህዝብም በተፈጠረው ነገር በጣም ተገረመ፡፡ “ይህ ተአምር ልጁ ወንድሙን እንዳልገደለ በሐቅ ይመሰክራል” በማለትም ደመደመ፡፡ የሀረሩ አሚር በበኩሉ “የዓሊ ኸይሮ”ን ተአምር ሲያይ “በህይወቴ ስፈልገው የነበረውን ሐቀኛ ሰው ዛሬ አገኘሁት” የሚል ቃል ተናገረ፡፡ “አሊ ኸይሮ”ንም የዙፋኑ ወራሽ በማድረግ ሾመው፡፡
-----
ወደ ሀረር ከተማ ከመጣችሁ “Amiroo! Kheyruma yaadi, Sharriin abbuma eeydii” የሚል አባባል ትሰማላችሁ፡፡ “አሚር ሆይ! አንተ ኸይሩን ብቻ አስብ፤ ለሸርሩ ባለቤት አለውና” እንደማለት ነው፡፡ ከአባባሉ ጀርባ ብዙ ታሪኮች ይነገራሉ፡፡ ከነዚያ ታሪኮች መካከል አንዱ ከላይ የቀረበው ተረት ነው፡፡

 በተረቱ እንደተገለጸው ተንኮለኛ ሰው በለስ የቀናው መስሎት ብዙ የሸር ትብታቦችን ሊተበትብ ይችላል፡፡ ይሁንና እንደዚህ ዓይነቱ ሰው አጓጉል ሆኖ ነው የሚቀረው፡፡ የማታ ማታ ራሱ በሸረበው የተንኮል ድር መታሰሩ የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህ በህይወት እያለ ደግ ደጉን ብቻ አስብ!! ለተንኮሉ ባለቤት አለውና!!
በድጋሚ Amiroo kheyruma yaadi, Sharriin abuma eeydi ብለናል፡፡
----
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 20/2007
-----
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 8/2007
ሀረር-ምስራቅ ኢትዮጵያ

Sunday, September 21, 2014

መሐመድ ወርዲ- ዘመን የማይሽረው አርቲስት

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
                                                       
----
 እነሆ ነፍስ የሆነውን አርቲስት ልናነሳው ወደድን!! ተወዳጅ፣ ጥበበኛ፣ ባለ ተሰጥኦ ከያኒ!! እውነተኛ የሙዚቃ ቀማሪ! ሱዳን ያፈራችው የምንጊዜም ጌጥ!! ከካይሮ እስከ ዑጋንዳ፣ ከጅቡቲ እስከ ማሊ ምንጊዜም እንደተወደደ ያለ የጥበብ ዋርካ!! ሙሐመድ ወርዲ!!

  “ወርዲ” ማለት ለሱዳኖች ንጉሥ እንደማለት ነው፡፡ እኛም ከአንጋፋ አርቲስቶቻችን ነጥለን አናየውም፡፡ በድሮ ጊዜ ወርዲን በፍቅር ሰምተነዋል፡፡ ዛሬም ወርዲን በመደጋገም እየሰማነው ነው፡፡
*****
ወርዲ ከልቡ ዘፋኝ ነው፡፡ ዘፈኖቹ ከኛ ጋር ከመዛመዳቸው የተነሳ እኛን እኛን ይሸታሉ፡፡ በርካታ ዜማዎቹ እኛ የምንጊዜም ምርጦች አድርገን ለምንወዳቸው ታዋቂ ዘፈኖቻችን መነሻ ለመሆንም በቅተዋል፡፡ ለምሳሌ አንጋፋው ድምጻዊ ጥላሁን ገሠሠ ያዜመውን “አንቺ ከቶ ግድየለሽም”ን ውሰዱት፡፡

አንቺ ከቶ ግድ የለሽም
ስለፍቅር አይገባሽም
ሁሉን ነገር እረስተሽው
ችላ ብለሽ ስለተውሽው
ቻልኩት ፍቅር ለብቻዬ፡፡

አዎን! ዛሬም ድረስ የዚህ ዜማ ተወዳጅነት አልቀነሰም፡፡ ለዚህ ዜማ መሰረቱ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ነው፡፡ ሙሐመድ ወርዲ ዘፈኑን ሲያዜመው እንዲህ ነበር ያለው፡፡

“አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ
ጠል ዐዛበክ ዋ ሱሃዲ
ዋ ሽጃያ አነ ዐዛቢ”

ታዲያ ሙሐመድ ወርዲ የተጫወተውን ዜማ ጋሽ ጥላሁን ወደ አማርኛ የመለሰው እንዲሁ በጋጠወጥነት አይምሰላችሁ፡፡ በነገሩ ውስጥ  የወርዲ ሙሉ ቡራኬ አለበት፡፡ በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመን የካርቱም መንገድ ለኛ አርቲስቶች የውሃ መንገድ ነበረ፡፡ ለሱዳኖችም ከዋዲ ሃልፋ ይልቅ ሸገር ነበር የምትቀርባቸው፡፡ እናም በዚህ ምልልስ መሀል የኛዎቹ አንጋፋዎች (ጥላሁን ገሠሠ፣ ምኒልክ ወስናቸው፣ አለማየሁ እሸቴ፣ ዓሊ ሸቦ፣ ዓሊ ቢራ ወዘተ..) እና የሱዳኖቹ አንጋፋ አርቲስቶች (አሕመድ አል-ሙስጠፋ፣ ሰይድ ኸሊፋ፣ ሙሐመድ ወርዲ፣ አብዱልከሪም አል-ካብሊ፣ አብዱል ዓዚዝ አል-ሙባረክ ወዘተ…) የአንድ ቤተሰብ ልጆች ሆነው ነበር፡፡ ሱዳኖቹ ያዜሙትን የኛዎቹ ወደ አማርኛ፣ ኦሮምኛና ሶማሊኛ እየመለሱ ይጫወቱታል፡፡ የኛንም ዘፈኖች ሱዳኖች በቋንቋቸው እየተረጎሙ ይዘፍኑታል፡፡ አንዳንዴ ዕድል ሲገጥማቸው ሁለቱም ዘፋኞች አንዱን ዜማ በአንድ መድረክ ላይ በየቋንቋቸው ይጫወቱታል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ነው እንግዲህ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ወደ አማርኛ የተመለሰው፡፡

አዎን!! እነ ጋሽ ጥላሁን እንደ አሁኖቹ ዘፋኞች (አንዳንዶቹን ማለቴ ነው) የሱዳንና የፈረንጅ ዜማን ወደ አማርኛ እየገለበጡ “የራሴ ድርሰት ነው”  ብለው ሊያሞኙን አይከጅሉም፡፡ ዋናው አርቲስት ባለበት ጭምር እየዘፈኑ ያሳዩትና “እንዴት ነው! አበላሽቼብህ ይሆን?” በማለት ምክርና እገዛ ይጠይቁታል፡፡ ሱዳናዊው አርቲስትም በሰማው ነገር ላይ የራሱን አስተያየት ይሰጣል፡፡ የኛዎቹም ከሱዳናዊያኑ አርቲስቶች የሚሰጣቸውን አስተያየት ተንተርሰው እጅግ የተሻለ ስራ ይሰሩና ህዝቡን እንካችሁ ይሉታል፡፡ ለዚያም ነበር ስራው የሚዋጣላቸውና ዘመን ተሻጋሪ የሚሆንላቸው፡፡

በዚህ ስሌት ወደኛ ቋንቋዎች ከተቀየሩት ተወዳጅ የሱዳን ዜማዎች መካከል የጥላሁን ገሠሠ “እዩዋት ስትናፍቀኝ” (ሰይድ ኸሊፋና ኢብራሂም አውድ በጋራ ከዘፈኑት ዘፈን የተወሰደ)፣ የአሰፋ አባተ “ሸግዬ ሸጊቱ” (ከአሕመድ አል-ሙስጠፋ “ሐቢቢ በኪቱ” የተወሰደ)፣ የምንሊክ ወስናቸው “ስኳር” (ከአብዱልከሪም አል-ካብሊ “ሱከር” የተወሰደ) የዓሊ ቢራ “ኦፊ ረፋ ቡልታ” (ከሙሐመድ ወርዲ “ያ ኑረል-ዐይን” የተወሰደ) ይጠቀሳሉ፡፡
                                                                          *****
    በርካታ የሀገራችን የሙዚቃ ወዳጆች ከመሐመድ ወርዲ ዜማዎች መካከል ለ“ገመር ቦባ” እና ለ“ቲስዐተ ዐሸር ሰና” (ብዙዎች የሚያውቁት  “ሰበርታ” በሚለው ስም ነው) ልዩ ፍቅር አላቸው፡፡ ሆኖም ሱዳኖች በአንደኛ ደረጃ የሚያሰልፏቸው ሌሎች በርካታ የወርዲ ዜማዎች አሉ፡፡ በተለይም “ሱድፋ”፣ “ቃሲ ቀልበክ”፣ “አልሀወል አወል”፣ “አነ ማ በንሳክ”፣  “አንናስ አል-ጊያፋ”፣ “ሐረምተ አድ-ዱንያ”፣ “ያ ኑረል ዐይን”፣ “ሸተል ዘማ”፣ “አል-ሙርሳል” የመሳሰሉት ከምርጥ የወርዲ ዜማዎች መካከል ይሰለፋሉ፡፡ እኔ በግሌ በጣም ከምወዳቸው የሱዳን ዜማዎች መካከልም አንዱ የሙሐመድ ወርዲ “አዚብኒ ወተፈነን” ነው፡፡

ዐዚብኒ ወዚድ ዐዘባ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚይክ
ዜይመን ሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚክ፡፡
አዚብኒ ወተፈነን ፊ አልዋን ዐዛቢ
ማ ቲምሳሕ ዲሙዒ ማ ቲርሐም ሸባቢ፡፡
ኸሊኒ ፊሹጁኒ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ
ዜይ መንሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ፡፡

ወርዲ በዚህ ዘፈን ለወዳጁ “ልብሽ ጨክኖብኝ ፍቅርሽ አቃጥሎ እየጨረሰኝ ነው፤ መጥተሸ እምባዬን የማታብሺልኝ ልበ-ደረቅ ነሽ” የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው የፈለገው፡፡ ወርዲ ይህንን ዜማ የዛሬ 20 ዓመት ገደማ በአዲስ አበባ ስታዲየም እጅግ ባማረ ሁኔታ የተጫወተው ሲሆን የሀገራችን አድናቂዎችም በጋለ ስሜት ተቀብለውታል ( ቪዲዮውን በሚከተለው ሊንክ ላይ ተመልከቱት፡፡  https://www.youtube.com/watch?v=WkegFEEwjjM&feature=related
                                                                          *****
ታዲያ የወርዲ ፍቅረኛ በ“አዚብኒ-ወተፈነን” ውስጥ እንደተገለጸው በጭካኔዋ አልዘለቀችም፡፡ ወርዲ በጉንጮቹ ላይ የሚያፈሰው እምባ አሳዝኖአት ከፍቅር በረከቱ ልታቀምሰው መጥታለታለች፡፡ ወርዲም ፍቅረኛውን ያገኘበትን ቀን “የቀኖች ሁሉ ረጢብ፣ እጅግ በጣም ገዳም፣ የምኞቴን ያሳካሁበት ቀን መጥቶልኛል” በማለት ገልጾታል፡፡
“ሱድፋ” የሚለውን የሙሐመድ ወርዲን ዘፈን እናውቀው የለ?.. በዚያ ዘፈን ውስጥ ወርዲ ለወዳጁ ያለውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን ከናፈቁት ወዳጅ ጋር መገናኘቱ የሚሰጠውን ደስታ በተዋቡ ቃላት ገልጾታል፡፡ እኔ በበኩሌ እጅግ በጣም የምወደው የወርዲ ዘፈን ይኸው ሱድፋ ነው፡፡ እነሆ የሱድፋን ሙሉ ግጥም ተጋበዙልኝ፡

ሱድፋ… ሱድፋ
ሱድፈ ወ አጅመል ሱድፈነ የውም ላቄታ
አስዓድ የውም የውሚል ሐዬታ
ኑረ ዐይነያ አያም ሓቤታ

ይህ አዝማቹ ነው እንግዲህ፡፡ “ሱድፋ” ማለት አስገራሚ ዕድል ማለት ነው (በእንግሊዝኛ fortunate የሚለው ቃል ይቀርበዋል)፡፡ ተከታዮቹ ግጥሞች የሚከተሉት ናቸው፡፡

አን-ነዘራት በሪዓ ገመም ዘውፍጀል ኸጀል
አልበሰማት ተበዊ ዘይ ኑረል ዐመል
ወጅሂክ ቤን መዛህሪክ ዘይ በድሪ-ክ-ከመል
ወሽሻመክ ኺዴድክ ዘይ ጠዕመል ኹበል
ተስኪር ገልቢ
ወተሽዒል ሑቢ
ኢሽሀክ ረብቢ
አነ በህ ዋ
-----
ማ ቃዲር አጉል ሊክ አን ሑብቢል ከቢር
ወስፉ ዓለይያ ቃሲ መዓዪሽ ፊ-ድ-ደሚር
ቀድረል ከውን ተኩልሉሁ አክበር ቤ ከቲር
ማሊክኒ ሙሐዪይርኒ ሹፍከል ቢል ኣሲር
አስአሊ ቀልቢ
ኢኪኒ ዪቅደር
ኢሽራሕ ሑቢ
አነ ሙሕታር
------
ሱድፈ ዑዩኑ ሻፈክ ሌይሊ ባቂ ይነዊር
ያ አይያም ረቢዒ ዑምሪ መዓኪ አዝሐር
ፊሃ አጥ-ጤይር ይገኒ ሚን አል-ሓኒ ዪዝከር
ቀልቢ ፈራሸ ሐውሊ ወኢንቲ ሸባቢከ አኽደር
ያ መበሒብቢ
ባዕቡድ ሑብቢክ
አለሻን ሑብቢክ
ሩሒ ፈዳክ
*****
ለመሆኑ መሐመድ ወርዲ ማን ነው?

  ሙሉ ስሙ ሙሐመድ ዑስማን ሳሊሕ ወርዲ ነው፡፡ እርሱ ግን “ሙሐመድ ወርዲ” ወይንም በአጭሩ በቤተሰቡ ስም “ወርዲ” ተብሎ ነው የሚታወቀው፡፡ የተወለደው እ.ኤ.አ. በ1932 “ዋዲ ሀልፋ” በተሰኘው ሰሜናዊው የሱዳን ክፍለ ሀገር፣ “ሱወርዳ” በተባለች ትንሽዬ የገጠር መንደር ውስጥ ነው፡፡ እናቱ የኑቢያ ተወላጅ ስትሆን አባቱ ዐረብ ነው፡፡

ወርዲ የሙት ልጅ ነው፡፡ ሁለቱንም ወላጆቹን በልጅነቱ ነው ያጣው፡፡ በመሆኑም በዘመዶቹ ጥበቃ ስር ሆኖ ነው ያደገው፡፡ ትምህርቱን በዋዲ ሀልፋ እና በካርቱም ተከታትሏል፡፡ የተወለደበትን ሀገር እስከ 1956 በመምህርነት ሙያ ካገለገለ በኋላ በወቅቱ ይሞካክራቸው የነበሩት ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ጣቢያ ተቀርጸው በመተላለፋቸው በህዝብ ልብ ውስጥ ገባ፡፡ ያገኘው የሞራል ድጋፍ ማነሳሻ ስለሆነው መምህርነቱን ትቶ የአርቲስትነቱን ጎራ ተቀላቀለ፡፡ ከዚያም ሱዳኖች ከሚያፈቅሯቸው ቁንጮ ዘፋኞቻቸው አንዱ ለመሆን በቃ፡፡
 
    ወርዲ በህይወቱ የተረጋጋ ኑሮ አልኖረም፡፡ በሱዳን የተለዋወጡት መንግሥታት በተቃዋሚነት እየፈረጁት አንገላተውታል፡፡ በመሆኑም ለሀያ ዓመታት ያህል በካይሮና በለንደን ነው የኖረው፡፡ በ2002 ግን ወደ ሀገሩ በክብር ተመልሷል፡፡ ወርዲ በሙዚቃው ዕድገት ላደረገው አስተዋጽኦ ከካርቱም ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸልሟል፡፡ ከልዩ ልዩ የአውሮጳ፣ አፍሪቃና እስያ ሀገራትም ሽልማቶችን ተቀብሏል፡፡
 መሐመድ ወርዲ በመጨረሻዎቹ ዓመታት በደረሰበት የጤና መታወክ ሁለት ኩላሊቶቹ ከጥቅም ውጪ ሆነው ነበር፡፡ ይኸው የኩላሊት ህመም ፋታ ነስቶት በየካቲት ወር 2012 ከዚህች ዓለም አሰናብቶታል፡፡
*****
ከመግቢያዬ እንደገለጽኩት የሀገራችን የሙዚቃ አፍቃሪዎች በጣም የሚወዱት የመሐመድ ወርዲ ዘፈን “ሰበርታ” ነው፡፡ እኔም “ሱድፋ”ን ከሁሉም እንደማስበልጥ ገልጫለሁ፡፡ በሱዳኖች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነው የመሐመድ ወርዲ ዜማ ግን “ገመር ቦባ” ነው፡፡ ሱዳኖች እ.ኤ.አ. በ2000 ባደረጉት ምርጫ “አል-ገመር ቦባ” የተሰኘው ዘፈን የክፍለ ዘመኑ ምርጥ “ነጠላ ዜማ” ተብሎ ተመርጧል፡፡እኔም ገመር ቦባን በድምጽ (ኦድዮ) ልጋብዛችሁና ላብቃ፡፡

ቦባ ዐሌክ ተጊል… ቦባ ዐሌክ ተጊል
አል-ገመር ቦባ ዐሌይክ ተጊል፡፡
አስ-ሰጊሩን አል-ማ-ከቢር
አር-ሪጌበት-ጊዛዛት አሲር
አስኑን በርራጊን የሺል
አል-ዑዩን መሥለል ፈናጂል
ቢንተ-ሱዳን አሲል
ያ ገመር ቦባ ዐሌክ ተጊል፡፡

(ገመር ቦባን በዚህ ሊንክ ላይ ይስሙት https://archive.org/details/MohammedWardi-AlQamarBoeba )
------
አፈንዲ ሙተቂ
መጀመሪያ ታሕሳስ 6/2006 ተጻፈ፡፡
እንደገና ተሻሽሎ መስከረም 9/2007 ተጻፈ፡፡
---
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.
 You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click this link to go to his facebook page.



Monday, September 15, 2014

የኤርትራ ህልም!

ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
----------                                               
ኤርትራ ዛሬ ራሷን የቻለች ሀገር ናት፡፡ ትናንት ግን የኛው አካል ነበረች፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሤ ብልጥ የሆኑ መስሎአቸው ለሁላችንም አስፈላጊ የነበረውን የፌዴሬሽን ፎርሙላ ሰረዙትና ህዝቡን አስቀየሙት፡፡ ደርግ ደግሞ የራሳችንን ህዝብ እንደ ባዕድ እየቆጠረ በመትረየስ አጨደው፡፡ በታንክ ደመሰሰው፡፡ በዚህም የተነሳ ወጣቱ “አደይ ኤሪቲሪያ”ን እየዘመረ ወደ ባርካና ሳህል ነጎደ፡፡ ራሱን አደራጅቶ ጀብሃና ሻዕቢያ ሆኖ መጣ፡፡ ውጤቱም 1983 ላይ ታየ፡፡
  
   የደርግና የኃይለ ሥላሤ መንግሥታት ያደረጓቸው ነገሮች ሲገርሙን በጣም ግራ የሚያጋባው ሶስተኛው መንግሥታችን መጣ፡፡ ይህ የኛ መንግሥት “የተበላሸውን ሁሉ አስተካክለን አብረን መኖር እንችላለን” ብሎ መከራከር ሲገባው ጭራሹኑ “ኤርትራ ካልተገነጠለች ኢትዮጵያ ሰላም አታገኝም” ባይ ሆኖ ተገኘ፡፡ ክፍለ ሀገሩ “ሓርነት ወጣ” ከተባለ በኋላ ደግሞ መንግሥቱ ከሚከተለው ግልጽነት የጎደለው አሰራር የተነሳ በ1990 ሺዎችን ያረገፈ ግዙፍ ጦርነት ተቀሰቀሰ፡፡ ከአንድ ምንጭ የተቀዱ ህዝቦች ተጋደሉ፡፡ እነሆ ዛሬም ድረስ ነገሩ ሳይለይለት በጨለማ ውስጥ ነው ያለነው፡፡
                                                               
   እኛ ግን ተስፋ አንቆርጥም! በአያያዝ ጉድለት የተለየንን ወገናችንን መመለስ እንፈልጋለን፡፡ ህዝቡ ለጊዜው ሪፈረንደም አድርጎ ነጻነቱን ማወጁን እናደግፋለን፡፡ ቢሆንም ህልም አይከለከለምና አንድ ቀን ተቀራርበን በጋራ ስለመስራት እንወያይ ይሆናል ብለን እናልማለን፡፡ የኛ ልጆች ደግሞ በኮንፌዴሬሽን ስለመስራት ያስቡ ይሆናል፡፡ የልጅ ልጆቻችን በፈቃደኝነት ስለመዋሃድ ያስቡ ይሆናል፡፡ በዚያን ጊዜም አሁን የምንመኘው በአንድነት ውብ የመሆን ሚስጢራችን ይመለስልናል ብለን እንመኛለን፡፡ ምን ይታወቃል? ለፈጣሪ የሚሳነው ነገር የለም፡፡

ወገኖቼ ደጉን ነው የተመኘሁት፡፡ በቅን ልቦና በርትተን ከጸለይንና ከኛ የሚጠበቀውን ካደረግን ሁሉንም የሚችለው ፈጣሪ ህልማችንን እውነት ያደርግልናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
-------
   ምን እንደጣለብኝ እንጃ! ያንን ምድር እጅግ ሲበዛ እወደዋለሁ፡፡ እኔ ለተወለድኩበትና አብዛኛውን ዕድሜዬን ለጨረስኩበት የምስራቅ ኢትዮጵያ ክልል ጎረቤት ከሆነችው ሶማሊያ ይልቅ በ1600 ኪ.ሜ. የምትርቀው አስመራ ናት የምትናፍቀኝ፡፡ ስለሶማሊያ የተጻፈ መጽሐፍ ማንበብ ብዙም አይማርከኝም፡፡ ስለ ኤርትራ የተጻፈ መጽሐፍ ካጋጠመኝ ግን ሳላየው አላልፍም (ይህ ግን ሶማሊያን ከመጥላት እንደማይቆጠርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ)፡፡

    ታዲያ በርካቶቻችሁም እንደኔው ትመስሉኛላችሁ፡፡ ለምሳሌ ከ1970ዎቹ ጀምሮ ሲታተም የቆየው የቤኒ አምሩን ወጣት የሚያሳየው ፖስተር ዛሬም ድረስ ከኛ ጋር ተሳስሮ ነው ያለው፡፡ አሁንም ድረስ በበርካታ ስፍራዎች ተለጥፎ አይቼዋለሁ፡፡ በፌስቡክም እርሱን እንደ ፕሮፋይል ፒክቸር የሚጠቀም ኢትዮጵያዊ ሞልቷል፡፡ በሌላ በኩል የኤርትራን ሙዚቃ የሚያዳምጡ ሰዎች በሽ ናቸው፡፡ ደራሲ መሐመድ ሳልማን መቐለ ሄዶ ያየው ነገር ቢያስገርመው “በኤርትራ ሙዚቃ የምትጨፍር ከተማ” የሚል አስደናቂ ወግ ጽፎ እውነቱን አስረድቶናል፡፡ መንግሥታት ቢጣሉ እንኳ ህዝቦች ምንጊዜም እንደሚነፋፈቁ ከዚህ በላይ የሚያስረዳ ዋቢ ያለ አይመስለኝም፡፡
--------
     ማርታ ሀይሉን አስታወሳችኋት? አዎን! ማርታን “ብራ… ነው… ብራ ነው”፤ “አዘዞ”፤ “ሎጋ ..ና እናውጋ” በተሰኙት ዘፈኖቿ እናውቃታለን፡፡ ከማርታ ዘፈኖች ዘወትር ቀልቤን ይገዛ የነበረው ግን የትግርኛ ዜማዋ ነው፡፡ አዝማቹ እንዲህ ይመስለኛል፡፡

 ካብ አስመራ ድንገት ርእዮ
ምጽዋ ገባሁ ልበይ ሕብዮ፡፡

እንተርጉመው እንዴ?… ግድ የለም ማርታ ራሷ እንዲህ እያለች በአማርኛ ተርጉማዋለች፡፡

“ከአስመራ ድንገት አይቼው
ምጽዋ ገባሁ ልቤን ሰጥቼው”፡፡

     አዎን! ትናንት የኛ ናት ስንላት ለነበረችው ኤርትራ ነው እንዲህ የዘመርንላት፡፡ ዛሬም ብንዘምርላት እንከበራለን እንጂ አንወቀስም፡፡ ምክንያቱም በመንግሥት ደረጃ ነው የተለያየነው፡፡ ሁለት ፓስፖርት እንዲኖረን ነው የተደረግነው፡፡ ሁለታችንም ግን አንድ ህዝቦች ነን፡፡ በደምም ሆነ በባህል በጣም የተዋሃድን የአንድ መሬት ብቃዮች ነን፡፡ ሁለታችንም የተዋብን የሴምና የኩሽ ህዝቦች ውቅር ነን፡፡ እንደኛ የሚያምር ህዝብ በትኛውም ዓለም የለም፡፡ የጀበና ቡና፣ ዶሮ ወጥ፣ ድፎ ዳቦ፣ የስጋ ፍትፍት፣ አምባሻ፣ ወዘተ…. ሁለታችን  ዘንድ ብቻ ነው ያለው፡፡
-----
    በርግጥ እላችኋለሁ፡፡  በምንባብና በወሬ እንጂ በአካል የማላውቃት ኤርትራ ትናፍቀኛለች! ያ በታሪክ ምዕራፎች “ምድሪ ባህረ ነጋሽ” እየተባለ ሲጠራ የኖረው ጀግና መሬትና ህዝብ ይናፍቀኛል፡፡ ያ የሰሜኑ በረኛ እያልን ስንመካበት የነበረው ህዝባችን ይናፍቃል፡፡

እውነትም ኤርትራ ! የዳማት ታሪክ ውቅር! የመጠራ አብያተ መንግሥታት ከርስ! የሀውልቲ ፍርስራሾች ቀብር! የአዱሊስና የዙላ ወደቦች መዘክር! የሱዋኪምና የዳህላክ ሱልጣኖች ደብር!

ኤርትራ የአብረሃ ደቦጭ ሀገር! የሞገሥ አስገዶም ሀገር! የዘርዓይ ደረስ ሀገር! የሎሬንዞ ታዕዛዝ ሀገር! የደጃች ሀረጎት ሀገር! በአይበገሬ ጀግንነታቸው ድፍን አፍሪቃን ያኮሩ አርበኞች የበቀሉበት ምድር!

ኤርትራ የበረከት መንግሥተ አብ ሀገር! የፀሐይቱ ባራኪ ሀገር! የአብረሃም አፈወርቂ ሀገር! የአሕመድ ሼኽ ሀገር! የሄለን መለስ ሀገር! የየማነ ባሪያው ሀገር! የሄለን ጳውሎስ ሀገር! በስርቅርቅ ድምጻቸው የሰውን ልብ እየሰረሰሩ የመግባት ሀይል ያላቸው የጥበብ ከዋክብት የወጡበት መንደር!

ኤርትራ የፊያሜታ ጊላይ ሀገር! የስዕላይ በራኺ ሀገር! የኦቦይ ተኽሌ ሀገር! የተክላይ ዘድንግል ሀገር! የሆቴል ፓራዲዞ ሀገር! የዕቁባይ ሲላ ሀገር! የምንወደው ደራሲያችን በዓሉ ግርማ በ“ኦሮማይ” መጽሐፉ እንደ ፊልም ግልጥልጥ አድርጎ እየተረከልን ዝንተ-ዓለም እንድንወዳት ያደረገን የቀይ ኮከብ ትዝታ ወመዘክር!

ኤርትራ የፊዮሪ ሀገር! የሳባ ሀገር! የማርቲና ሀገር! የብርኽቲ ሀገር! ፊያሜታ ጊላይን የመሳሰሉ “ሽኮሪናዎች”ን ያበቀለች ውብ የውቦች እመቤት!
-----
  ኤርትራን ስንጠራ በቅድሚያ ወደ አዕምሮአችን የምትመጣው አስመራ ናት፡፡ የአስመራ ናፍቆት ይገድላል፡፡ አስመሪና፣ አስመሪቲ፣ አቲ ጽብቕቲ!…

ውይ ስታምር! “ቀሽቲ” እኮ ናት፡፡ ያኔ በልጅ አዕምሮአችን በዘምባባ ጥላዋ ተሸክፋ በፖስትካርድ ስትቀርብልን “የኛ ውቢት” እያልን እንመጻደቅባት ነበር፡፡ እንቆቅልሽ ስንጫወትና መልሱ ጠፍቶን “ሀገር ስጠኝ” ስንባል እርሷን ለመስጠት እንሰስት ነበር፡፡ ጠያቂውም የዋዘ ስላልሆነ “አስመራ” ካላልነው ለጠየቀን ጥያቄ ትክክለኛውን መልስ አይነግረንም ነበር፡፡ ከማናውቃቸው “ዋሽንግተን” እና ሮማ ይልቅ አስመራ ነበር የምትበልጥብን፡፡ በትምህርት ቤት መዝሙራችንም እንዲህ እንል ነበር፡፡

ኦኬ ኦኬ ኦኬ ስራ
ሰላም ሰላም ወደ አስመራ
አዲስ አስተማሪ ከጃፓን የመጣ
ማስተማሩን ትቶ በቦክስ የሚማታ
አናግረኝና አናግርሃለሁ
በአሜሪካ ሽጉጥ አዳፍንሃለሁ፡፡
አማርኛም አልችል ትግርኛም አልሰማ
ሰተት ብዬ ልግባ አስመራ ከተማ፡፡

ግጥሙ “አንታራም” የሚሉት የህጻናት ጨዋታ ዓይነት ነው፡፡ ነገር ግን አስመራ ከልባችን እንዳትጠፋ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ዛሬም በልባችን ነግሳለች አስመሪና!
 ----
አስመሪና! እቲ ሽኮሪና! ሰሜናይት ጽብቕቲ! በዓሉ ግርማ ላንቺ ክብር የጻፈው ትዝ ይልሻል? እስቲ እናስታውሰው!

አስመሪና አስመራዬ
ካብ ሐንቲ ንግሥቲ ይበልፅ መልክእኪ
አማአድዬ ክርእየኪ ከሎኹ ኽአ
አብ ኢደይ ዘሎ ነገር ይወድቕ፡፡

(አስመራ አስመራዬ)
(ከአንድ ንግሥት ይበልጣል መልክሽ)
(በሩቅ ሲያይሽ በውበቷ ስለተማረሽ)
በእጄ ያለ ነገር ሳይታወቀኝ ይወድቃል)
------
  ጸጸራት፤ ፎርቶ፣ ሐዝሐዝ፣ አርበእተ አስመራ፣ እምባጋሊያኖ፣ ኮምቢሽታቶ፣ አዲ ጓእዳድ፣ ቃኘው፣ ማይተመናይ፣ ሰምበላይ፣ ጎዳይፍ፣  ገጀረት፣ ወዘተ… በጽሑፍ የማውቃቸው የአስመራ ሰፈሮች ናቸው፡፡ አንድ ቀን በሆነልኝና ባየኋቸው እያልኩ አልማሁ፡፡  እነዚህ አስገራሚ የአስመሪና ሰፈሮች ብዙ ባለታሪኮችን አብቅለዋል፡፡ ብዙዎች ገድላቸው እየተደጋገመ ሲነገርላቸው እሰማለሁ፤ አነባለሁ፡፡ ለኛ ቅርብ የነበረ አንድ ውድ ልጅ እየተረሳ በመሆኑ ግን አዝኛለሁ፡፡
 
     አማኑኤል እያሱ ይባላል! አስታወሳችሁት አይደል? አዎን! አማኑኤል በኛ ዕድሜ ዘመን ኢትዮጵያ ዋንጫ መብላት እንደምትችል ያስመሰከረው የታላቁ የ1980 የእግር ኳስ ቡድናችን ቋሚ ተሰላፊ ነበረ፡፡ የማሊያ ቁጥሩ 2 ይመስለኛል፡፡ አማኑኤል የያኔው ቡድናችን ባደረጋቸው ሁሉም ጨዋታዎች ተሰልፏል፡፡ ቡድኑ ዋንጫውን ሲበላም ከጓደኞቹ ጋር ቤተመንግሥት ድረስ ተጋብዞ ተሸልሟል፡፡ አማኑኤልን ያስገኘው ከዚያ ዘመን ዝነኛ ቡድኖቻችን መካከል አንዱ የነበረው የኤርትራ ጫማ ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን የኤርትራ አንደኛ ዲቪዚዮን ዋንጫን በተደጋጋሚ ያሸነፈ ነው፡፡
 
    አማኑኤል እያሱ በኢትዮጵያ ትቅደም አንደኛ ደረጃ ዋንጫም ለኤርትራ ክፍለ ሀገር ምርጥ ቡድንም ተሰልፎ ተጫውቷል፡፡ ባልሳሳት የ1981 የኢትዮጵያ ዋንጫን ያሸነፈው እነ አማኑኤል የነበሩበት የኤርትራ ክፍለ ሀገር ቡድን ነው፡፡ የአማኑኤል እያሱን ወሬ ለመጨረሻ ጊዜ ያነበብኩት በ1988 ለወዳጅነት ጨዋታ አዲስ አበባ መምጣቱን በማስመልከት በርካታ የግል ጋዜጦች ቃለ-መጠይቅ ባደረጉለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ መረጃው የለኝም፡፡ እስቲ የአስመራ ልጆች ወሬው ካላችሁ ስለአማኑኤል እያሱ አንድ ነገር በሉን፡፡
-----------------
አሁን ወደ ምዕራብ ኤርትራ ተሻግረናል! ባርካና ጋሽ የሚባሉት ቆላማ አውራጃዎች እዚህ ነው ያሉት፡፡ አቆርዳት፣ ተሰነይ፣ አሊጊደር፣ ኡምሐጀር፣ ባሬንቱ የተሰኙት ከተሞች በቆላው ምድር ውስጥ ተዘርግተዋል፡፡ ኩናማ፣ ናራ እና ቤጃ የሚባሉት ብሄረሰቦች እዚህ ነው የሚኖሩት፡፡ የአካባቢው ዋነኛው ህዝብ ግን ለኛ በጣም ቅርብ የሆነውን ሳቂታውን የቤኒ አምር ወጣት ያስገኘው የትግረ ህዝብ ነው፡፡

  የትግረ ህዝብ በውስጡ በርካታ ጎሳዎች አሉት፡፡ ከሁሉም የሚበረክተው ግን የቤኒ አምር ጎሳ ነው፡፡ ህዝቡ የሚነጋገርበት የትግረ ቋንቋ ከሴማዊ ቤተሰብ ነው የሚመደበው፡፡ ለዚህ ቋንቋ በጣም የሚቀርበው በደጋው ኤርትራና በኛዋ የትግራይ ክልል የሚነገረው ትግርኛ ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ቋንቋዎች ከጥንታዊው የግዕዝ ቋንቋ ነው የተወለዱት፡፡ የትግረ ቋንቋን ከ35 በመቶ የማያንሰው የኤርትራ ህዝብ ይናገረዋል፡፡ “ትግረ” ከኤርትራ ሌላ በሱዳንም (ከሰላ አካባቢ) በስፋት ይነገራል፡፡

ትግረና ትግርኛ በጣም ከመመሳሰላቸው የተነሳ እንግዳ ለሆነ ሰው አንድ ዓይነት ቋንቋዎች ሊመስሉት ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም ለትግርኛ ተናጋሪዎች የትግረ ቋንቋን መልመድ በጣም ቀላል ነው ይባላል፡፡ የትግረ ተናጋሪም ትግርኛን በቶሎ መልመድ ይቀለዋል፡፡ በመሆኑም ከጠቅላላው የኤርትራ ህዝብ 50% የሚሆነው ሁለቱንም ቋንቋዎች መናገር ይችላል (ይህ ቁጥር ትግርኛ ብቻ የሚናገሩትን፣ ወይንም “ትግረ” ብቻ የሚናገሩትን አይጨምርም)፡፡

 ምዕራባዊው ቆላ ኤርትራዊያን በጣም የሚያደንቋቸውን እንደ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ፣ ሙሐመድ ኢድሪስ እና ኢድሪስ ገላውዴዎስን ያፈራ መሬት ነው፡፡ በዚህ ሰሞን ልቤን ያሸፈተው የትግረ ልጅ ግን “አሕመድ ሼክ” ነው፡፡ አሕመድ ሼክን አወቃችሁት አይደል? አዎን! “ባቡሬይ”፣ “ኢላ ሰርጎ” ወዘተ.. እያለ በማይጠገበው የትግረ ምት የሚያዜመው ተወዳጅ ድምጻዊ ነው፡፡ አንድ ኤርትራዊ ወዳጃችን “ኤላ ሰርጎ”ን ሲፈታልን `ከጀርባው ፌሎሶፊ አለው” ነው ያለኝ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡
 
   የትግረ ሴት ለምትወደው አንድ ሰው (ለባሏ) እንጂ ለማንም ጸጉሯን አትገልጠውም፡፡ ስለዚህ ጉብሊቷን ልጅ የወደደው አሕመድ ሼክ በተዋቡ ግጥሞች እያወደሳት ዘፈነላትና ፍቅሩ ልቧ ውስጥ ዘልቆ መግባቱን ለማረጋገጥ ጸጉሯን ማየት ጀመረ፡፡ እርሷም ግጥሞቹን ከሰማችለት በኋላ ጸጉሯን ገልጣ አሳየችው፡፡ ድል አድራጊው ወዲ ሼክም ይዟት በረረ፡፡ “ኤላ ሰርጎ! ኤላ ሰርጎ” እያለ ነጎደ!
------
ሰሜን ኤርትራ!

ተወዳጇ የከረን ከተማ እዚህ ነው ያለችው! የሀረርጌዋ የድሬ ዳዋ ከተማ መንትያ እህት የምትመስለው ውቢቷ የሰሜን ፈርጥ! በቪዲዮ አይቻት ውበቷን አደነቅኩላት! አበቦቹ! ቤቶቹ! መንገዶቹ ሁሉም ውብ ናቸው፡፡ ከትግራይ የተገኘው ዝነኛው ብርሃነ ሃይለ አንድ ላይ በነበርነበት ዘመን ለከረኗ ጉብል እንዲህ ብሎላታል፡፡

ሸው በሊ ብለነይ ብለነይ
ዝለሊ ብለነይ ብለነይ
አሊሊ ብለነይ ብለነይ
አቲ ጓል ከረነይ ብለነይ

አዎን! ቢለን ከከረን ከተማ ጋር ስሙ የሚጠቀስ ብሄረሰብ ነው፡፡ ቋንቋው ከኛው የአገው ቋንቋ ጋር አንድ ዐይነት ነው፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ነው አንባቢ ሊመራመር የሚገባው፡፡ በወሎና በጎጃም የሚኖረው አገው ምን ሊያደርግ እዚያ ሄደ?… መቼ ነው እዚያ የሄደው?… መላምት ከመዘብዘብ በስተቀር ማንም ሰው ይህንን እንቆቅልሽ በሚያመረቃ ሁኔታ ሊፈታው አልቻለም፡፡ ኤርትራና እኛ አንድ ነን የሚያሰኘኝ እንዲህ ዓይነት ተጨባጭ ማስረጃ ስላለን ነው፡፡
  
  ቢለን ውብ ባህል ያለው ህዝብ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ሴቶቹ ካገቡ በኋላ ጸጉራቸውን መሰተር ግድ ነው፡፡ ህዝቡ የቢለን ቋንቋ ተናጋሪ ቢሆንም የትግረ ቋንቋንም ይጠቀማል፡፡ ትግርኛም በስፋት ይነገራል፡፡ በጣም ታዋቂ የሆነው የቢለን ተወላጅ “ዑመር እዛዝ” ነው፡፡ የጀብሃ ጦር ከመፍረክረኩ በፊት የሁለተኛው ዞን አዛዥ እንደነበረ ከዚህ በፊት ጽፌ ነበር፡፡

  ከከረን ሽቅብ ወደ ሰሜን ስናመራ ታሪካዊቷ አፋቤት አለች፡፡ ጄኔራል ታሪኩ አይኔ የሚመራው ናደው እዝ እዚህ ነበር የሰፈረው፡፡ የቀይ ኮከብ ዘመቻ ዋና አምባም ይህ ነበር፡፡ ከአፋቤት ወደ ሰሜን ስንበር ንዳዳማውና አስቸጋሪው የሳህል መሬት አለ፡፡ በሳህል እምብርት ላይ የኤርትራ ገንዘብ መጠሪያ ለመሆን የበቃችው “ናቅፋ” አለች፡፡ በዓሉ ግርማ እንደተረከልን ከሆነ ሳህል ማለት እሳት ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ይኖሩበታል፡፡ ከብቶች ይሰማሩበታል፡፡ ተክልም ይበቅልበታል፡፡ እዚህ አካባቢ በብዛት የሚኖረው ህዝብ “ረሺዳ” ይባላል (አንዳንዶች “ራሻይዳ” ይሉታል፤ ስህተት ነው፤ ትክክለኛው አጠራር “ረሺዳ” ነው)፡፡

  የ“ረሺዳ” ህዝብ ከሌላው የኤርትራ ህዝብ የሚለይበት በርካታ ነገሮች አሉት፡፡ ለምሳሌ ይህ ህዝብ ከሳዑዲ ዐረቢያ ተነስቶ ወደ ኤርትራ የገባው በቅርብ ዘመን (በ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ) ነው፡፡ በዚያ ወቅት የአሁኗ ሳዑዲ ዐረቢያ አልነበረችም፡፡ ሀገሩ ሁሉ በጎሳዎች የተከፋፈለ በረሃማ ምድር ነበር፡፡ ከነዚህ ጎሳዎች አንዱ አል-ረሺድ ይባላል፡፡ ይህ የአል-ረሺድ ህዝብ የአካባቢው የበላይ እንዲሆን በኦቶማን ቱርክ ተወሰነ፡፡ አብዛኛው ህዝብም ለነርሱ አደረ፡፡ “አል-ሱዑድ” የሚባለው ቤተሰብ ግን “አሻፈረኝ” አለ፡፡ “ራሴ በረሃውን ጠቅልዬ መግዛት ስችል ለምን በአል-ረሺድ ጎሳ የበላይነት አድራለሁ” በማለት አንገራገረ፡፡ በሁለቱ መካከል ጠብ ተነሳ፡፡ በመጀመሪያው ላይ የአል-ረሺድ ጎሳ አሸነፈ፡፡ አል-ሱዑዲዎች ወደ ኢራቅ ሸሹ፡፡

   ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን የአል-ሱዑድ ቤተሰብ በእንግሊዞች ደጋፊነት ራሱን አጠናክሮ መጣ፡፡ በአል-ረሺድ ጎሳ ላይም ድልን ተቀዳጀ፡፡ በዚህም የተነሳ የዐረቢያ በረሃ ለአል-ረሺድ ጎሳ አባላት ሲኦል ሆነ፡፡ ረሺዳዎች እየተያዙ በጅምላ ታረዱ፡፡ ንብረታቸው ተዘረፈ፡፡ በፊት ይረዳቸው የነበረው የቱርኮች መንግሥት በራሱ ችግር በመወጠሩ ምንም ሊያደርግላቸው አልቻለም፡፡ በመሆኑም ከእልቂቱ ለመዳን ሲሉ ባህር እያቋረጡ ወደ አፍሪቃ ምድር ተሰደዱ፡፡ በሱዳንና በኤርትራ መኖሪያቸውን ቀለሱ፡፡

እንግዲህ ረሺዳዎች ከዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሸሽ ወደ ኤርትራ የመጡ ተፈናቃዮች ናቸው ማለት ነው፡፡ በኤርትራ ውስጥ ንጹህ የዐረብ ዝሪያ የሚባሉት እነርሱ ናቸው፡፡ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸውም ዐረብኛ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ለአካለ መጠን የደረሰች ማንኛዋም ሴት ፊቷንም ሆነ ጸጉሯን መሸፈን ግዴታዋ ነው፡፡ በዓሉ ግርማ በኦሮማይ ውስጥ ሲተርክልን “ማንኛውም የረሺዳ ባል የሚስቱን ፊት ገልጦ የሚያይበትን ሰው አይፈልግም” በማለት የተናገረውም የባህላቸው አንድ አካል ነው፡፡
-------
አሁን ወደ ምስራቅ ኤርትራ ተሻግረናል፡፡ ብርኽቲ የሆነችው ምጽዋ እዚህ ነው ያለችው፡፡ ብርሃነ ሃይለ “ሸው በሊ ብለነይ” የተሰኘውን ዘፈን ሲቀጥል ምጽዋን እንዲህ ይላታል፡፡

“አብ ዋሊድ ማሳዋ
ኩለ ሊየን ሒልዋ”
 
   ትርጉሙን በትክክል ባላውቀውም “የምጽዋ ልጆች ሁሉም ጣፋጭ ናቸው” የሚል መልዕክት እንዳዘለ ይገባኛል፡፡ የምጽዋ ልጆች ቆንጆ ናቸው ተብሎ እየተደጋገመ ተነግሮላቸዋል፡፡ ከወደብ ከተማ የተገኙ በመሆናቸው ዓለም አቀፍ ስልጣኔና ልዩ ልዩ ባህሎች በነርሱ ላይ ሲነፍስ ይታያል፡፡

  ምጽዋ በጣም ውብ ናት፡፡ በተለይም ኪነ-ህንጻዋ ብዙ ተብሎለታል፡፡ ከዑስማናዊያን ቱርኮች ዘመን ጀምሮ ብዙ ገዥዎች ሲፈራረቁባት የነበረች መሆኗ በከተማዋ የሚታየውን ኪነ-ህንጻ እንዳሳመረው ምሁራን ያስረዳሉ፡፡
  
ኤርትራዊያን ምጽዋን ይወዷታል፡፡ እኛም እንወዳታለን፡፡ ነገር ግን ወደዚያ ለመድረስ የሚሻ ሰው እንደ እሳት የሚፋጀውን ሙቀቷን መቻል አለበት-ከተማዋ በዓለም ላይ ከፍተኛ ሙቀት ካላቸው ስፍራቸው አንዷ ናትና፡፡ የዚህች ከተማ ህዝብ ኑሮውን ከአየር ጸባዩ ጋር እንዲጣጣም አድርጎ ቀይሶታል፡፡ በመሆኑም አብዛኛው የንግድ እንቅስቃሴ የሚከናወነው ከምሽት እስከ እኩለ ሌሊት ባለው ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ከተማዋ ለዘወትር እንደጋለች አትቀርም፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ሙቀቱ ጋብ ይልና ጤናማው አየር ይነፍስባታል፡፡ ይህም ከጥር-የካቲት ባለው ጊዜ እና በሀምሌ ወር ነው፡፡ በነዚህ ወራት ከተማዋን የሚጎበኘው ቱሪስት በጣም ይጨምራል፡፡ በቀድሞው ዘመን ቀዳማዊ ኃይለሥላሤም ከተማዋን ለመጎብኘት የሚመጡት በነዚህ ወራት ነው (እርሳቸው ያሰሩት ቤተ-መንግሥት እስከ አሁን ድረስ አለ)፡፡

     ምጽዋ በወደብነት አገልግሎት መስጠት የጀመረችበት ዘመን በትክክል አይታወቅም፡፡ የታሪክ ምሁራን እንደሚሉት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በአካባቢው ከተማ ቀመስ ሰፈራ ነበር፡፡ ይሁንና እስከ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እንደ ወደብ ሲያገለግሉ የነበሩት ከምጽዋ አጠገብ የነበሩት ጥንታዊያኑ “ዙላ” እና “አዱሊስ” ነበሩ፡፡ የምጽዋ ተፈላጊነት ጉልህ ሆኖ የተከሰተው የባህር መደቡ በ1508 በዑሥማናዊያን ቱርኮች (Ottoman Turks) በተያዘበት ወቅት ነው፡፡ ከቱርኮቹ በማስከተልም ግብጾችና የኢጣሊያ ወራሪዎች ተፈራርቀውባታል፡፡

   ኢትዮጵያና ኤርትራ በፌዴሬሽን ከተዋሃዱ በኋላ ምጽዋ ከፍተኛ እመርታ ማሳየት ጀምራ ነበር፡፡ ከ1970ዎቹ መግቢያ ጀምሮ ግን የጦርነት ቀጣና ሆነች፡፡ የሻዕቢያ ሀይሎችና የኢትዮጵያ ሰራዊት ከፍተኛ እልቂት የተፈጸመባቸውን ጦርነቶች አካሂደውባታል፡፡ በተለይም በ1982 (እ.ኤ.አ. 1990) በተካሄደው ጦርነት ከሁለቱም ወገን በአስር ሺህ የሚቆጠር ሰራዊት መርገፉን ሁኔታውን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖችና የዐይን ምስክሮች ገልጸዋል (የሀምሳ አለቃ ታደሰ ቴሌ ሳልባኖን “አይ ምጽዋ” አስታውሱት)፡፡ የቀድሞው የኢትዮጵያ መሪ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያምም “ለከፍተኛ ሽንፈትና ኪሳራ የዳረገን ውድቀት ያጋጠመን በምጽዋ ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

የድሮው ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) የአሁኑ “ህዝባዊ ግንባር ንዴሞክራሲን ንፍትሒን” (ህግዴፍ) ምጽዋን የተቆጣጠረበትን ዘመቻ “ኦፕሬሽን ፈንቅል” በማለት ይጠራዋል፡፡ ምጽዋ የተያዘችበት ዕለትም (የካቲት 20) በየዓመቱ ይከበራል፡፡ በርካታ ህዝብ ወደ ምጽዋ ከሚጎርፉባቸው ዕለታት መካከልም አንዱ ይህ “የኦፕሬሽን ፈንቅል” መታሰቢያ የሚከበርበት ቀን ነው፡፡

ምጽዋ የብዙ ህዝቦች መኖሪያ ናት፡፡ ዋነኞቹ ነዋሪዎች ግን የአሳውርታ፣ ሳሆ፤ እና አፋር ብሄረሰቦች ተወላጆች ናቸው፡፡ በከተማዋ በዋናነት የሚነገረው ቋንቋ ዐረብኛ ነው፡፡ የሻዕቢያ መስራች ተብሎ የሚታወቀው ዑሥማን ሳልህ ሳቤ የተወለደው በምጽዋ አጠገብ ካለችው ሂርጊጎ የተባለች አነስተኛ መንደር ነው፡፡ ኢብራሂም አፋ፣ ረመዳን መሐመድ ኑር እና ዓሊ ሰዒድ አብደላን የመሳሰሉት የህግሓኤ (ሻዕቢያ) እውቅ ኮማንደሮችም የምጽዋ ልጆች ናቸው፡፡ 

  ከምጽዋ ወደብ ዝቅ ብሎ ጥንታዊቷ የአዱሊስ ወደብ ትገኛለች፡፡ ይህች የወደብ ከተማ ከክርስቶስ ልደት በፊት ጀምሮ የተጓዦች መግቢያና መውጪያ ነበረች፡፡ የጥንቱ ሮማዊያንና ግሪኮችም በደንብ ያውቋታል፡፡ አጼ ካሌብ ወደ ደቡብ ዐረቢያ ሲዘምት ወታደሮቹን በመርከብ ያስጫነው ከዚህች የወደብ ከተማ ነው፡፡ በሀገራቸው ከፍተኛ በደል ያጋጠማቸው የነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ተከታዮች ከጥቃቱ ለመሸሽ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ በአዱሊስ በኩል ነበር ያለፉት፡፡ ሌላም ብዙ ታሪክ ተስተናግዶአል-በአዱሊስ፡፡
---------
ከምጽዋ ወደ መሀል ኤርትራ ለመጓዝ መንገዱን ስንጀምር በቅድሚያ የምናገኘው የሳሆ ህዝብን ነው፡፡ ይህ ህዝብ በስተደቡብ በኩል ከሚጎራበተው የአፋር ህዝብ ጋር ተመሳሳይ የሆነ የኢኮኖሚ መሰረት አለው፡፡ ሁለቱም በከብት እርባታ ነው የሚተዳደሩት፡፡ ሁለቱም ኩሻዊ ቋንቋ ነው የሚናገሩት፡፡ በአለባበስ ግን ሳሆን ከአፋር በቀላሉ መለየት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ የሳሆ ተወላጅ የሆነ ሰው አፋሮች የሚታጠቁትን “ጊሌ” የሚባለውን ረጅም ቢላዋ አይታጠቅም፡፡ የሳሆ ሰው የሚያሸርጠው ሽርጥም ከአፋር ሽርጥ ረዘም ይላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሳሆ ብዙ ጊዜ ከእጁ ጦር አያጣም፡፡ ታዲያ የሳሆ ቋንቋ በትግራይ ክልል ምስራቃዊ ዞን የሚኖረው የኢሮብ ህዝብ ከሚናገረው ቋንቋ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ኢሮብና ሳሆ የሚለያዩት በሚከተሉት እምነትና በኢኮኖሚ መሰረታቸው ነው፡፡ ሳሆ ሙሉ በሙሉ የእስልምና እምነት ተከታይ ነው፡፡ ኢሮብ ግን በአብዛኛው ክርስቲያን ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ የሚበዙትም ካቶሊኮች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል የኢሮብ ህዝብ አራሽ ገበሬ ይበዛዋል፡፡ ከላይ እንደተገለጸው የሳሆ ህዝብ በከብት እርባታ ነው የሚተዳደረው፡፡

ሳሆን ስናልፍ ደግሞ ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ በስፋት የሚኖርባቸውን የአከለ ጉዛይ፣ ሰራዬ እና ሐማሴን አውራጃዎችን እናገኛቸዋለን፡፡ በኤርትራ ውስጥ ካሉት ብሄረሰቦች መካከል ብዙ ቁጥር ያለው (50 % የሚሆነው) ይህ ትግርኛ ተናጋሪ ህዝብ ነው፡፡ ይህ ህዝብ በባህሉም ሆነ በቋንቋው ከኛው የትግራይ ህዝብ ጋር ይመሳሰላል፡፡ ህዝቡ በአብዛኛው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ መሆኑም ከትግራይ ህዝብ ጋር ያመሳስለዋል፡፡ ይሁንና ቋንቋው ባለፉት በርካታ ዘመናት ከጣሊያንኛ፣ ከዐረብኛ እና ከትግረ ቋንቋዎች ጋር በመወራረሱ በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚነገረው ትግርኛ የተለየ ዘዬ ሊሆን በቅቷል፡፡

አጅግ በርካታ የሆኑ የኤርትራ ከተሞች ያሉት በዚህ ክልል ነው፡፡ ጊንዳዕ፣ ሐሙሲት፣ ሰገነይቲ፣ ደቀምሐረ፣ መንደፈራ (አዲ ዑግሪ)፣ አዲኳላ፣ ሰንዓፈ፣ ደባሩዋ ወዘተ… እዚህ ነው የሚገኙት፡፡ በመሀከላቸው ደግሞ አስመራ ጉብ ብላ ትታያለች፡፡ ከከተሞቹ መካከል የሚበዙት በጣሊያን ዘመን የተቆረቆሩ ናቸው፡፡ በሰራዬና በአከለ ጉዛይ አውራጃ ውስጥ ግን የጥንቱ የአክሱም ዘመነ መንግሥት ታዋቂ ከተሞች የነበሩትን እንደ “ሀውልቲ” እና “መጠራ” የመሳሰሉ መንደሮችን ማግኘት ይቻላል፡፡ በነዚህ ከተሞች ፍርስራሽ ስር ገና ያልተነካ ድልብ የአርኪዮሎጂ ሀብት አለ፡፡ ወደፊት ቆፈረን የምናወጣቸውን ማቴሪያሎች የህዝቦቻችንን አንድነት የሚመሰክሩ ቋሚ ቅርሶች አድርገን ልጆቻችንን እናስተምራለን ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ 
-------
ኤርትራን በኢትኖግራፊ ጉዞ እንዲህ ቃኝተናታል፡፡ ነገር ግን በዚሁ አናበቃም፡፡ ወደፊትም በተሻለ ዝግጅት ተመልሰን እንዘይራታለን፡፡ ለአሁኑ በዚሁ ይብቃን!!
ሰላም!!
-----
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 30/2006
-----
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his facebook page. Just click this link


Thursday, August 14, 2014

እስልምና፣ “ጂሃድ” እና ሰሞነኛው የኢራቅ ሚሊሻ


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
--------
ኢራቅ በሳዳም ሁሴን አገዛዝ ስር በነበረችበት ዘመን ከሞላ ጎደል ሰላምና መረጋጋት ነበራት፡፡ ሀገራዊ አንድነቷም የተጠበቀ ነው፡፡ አሜሪካ አንድም ማስረጃ ባልነበረው ወሬ ተነሳስታ በ2003 (እ.ኤ.አ) ሀገሪቷን ከወረረቻት በኋላ ግን አንድነቷም ሆነ ሰላሟ ተናግቷል፡፡ በኤፍራጥስና ጤግሮስ ወንዞች ላይ የከተመችው ውቢቷ ባግዳድም በየዕለቱ የቦንብና የፈንጂ ፍንዳታ ማስተናገድ ምሷ ሆኗል፡፡ 
    ከዚህ ባሻገር ሀገሪቷ ክቡር የሆነውን የእስልምና አስተምህሮ እንዳሻቸው እየተረጎሙ ስውር አጀንዳዎቻቸውን ለማስፈጸም የሚተጉ ጽንፈኛ ግለሰቦችና ቡድኖች መፈልፈያ ሆናለች፡፡ አቡ ሙስዓብ አል-ዘርቃዊን የመሳሰሉ ጽንፈኞች ኢራቅን የእቶን እሳት መቀጣጠያ ሲያደርጓት እንደከረሙ ተመልክተናል፡፡ በዘንድሮው ዓመት ደግሞ ድሮ ከምንሰማቸው እጅግ የከፋ ጽንፈኛ ቡድን በዚያው ምድር ላይ እጆቹን ሲዘረጋ ለመታዘብ በቅተናል፡፡
  ራሱን “የኢራቅና የሻም ኢስላማዊ መንግሥት” እያለ የሚጠራው (ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “ኢስላማዊ መንግሥት” በሚለው አጭር ስያሜ ብቻ የሚጠራው) ቡድን ከየት ተገኘ?.. እንዴት ተመሰረተ?… መስራቾቹስ እነማን ናቸው?… ከጀርባ የሚገፉትስ እነ ማን ናቸው?…. የመጨረሻ ዓላማው ምንድነው?…. እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ የነጠረ መረጃ ሊኖረን ይገባል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን ብዙዎቹን ጥያቄዎች ለመመለስ አይቻልም፡፡ ስለዚህ ጥያቄዎቹን ጊዜ ይመልሳቸው ማለቱ ይሻላል፡፡ ቡድኑ ለሚተግብራቸው የጽንፈኝነት አድራጎት እስልምናን እንደ ማስረጃ እየጠቀሰ ማነብነቡ ግን በጣም ያሳምመናል፡፡
   በዘመናችን የሚታዩትና በእስልምና ስም የሚነግዱ ጽንፈኞች በሙሉ “ጂሃድ እያደረግን ነው” እያሉ ነው የሚፎክሩት፡፡ ለብዙ ክፍለ ዘመናት በሙስሊሞች መሀል በሰላም ሲኖሩ የነበሩ ማህበረሰቦች ሀይማኖታቸውን እንዲቀይሩ ማስገደድም ጀምረዋል፡፡ “ጂሃዳቸው” ግብ መትቶ ሀገር ከተቆጣጠሩ በኋላ የሚመሰርቱት “ኋላቀር” መንግሥት ምን ዓይነት እንደሆነም ምልክቱን እያየን ነው፡፡ በርግጥ በእስልምና እይታ እንዲህ ዐይነቱ ጽንፈኝነት “ጂሃድ” ማድረግ ነው ተብሎ ሊጠራ ይችላልን?… እስልምናስ “ኋላቀርነትን” የሚናፍቅ እምነት ነውን?… በነዚህ ነጥቦች ዙሪያ አንዳንድ ነገሮችን ለመናገር አስቤ ነው ይህንን መጣጥፍ የጻፍኩት፡፡

==“ጂሃድ” እና ጽንፈኞች=

  ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በህይወት ዘመናቸው ከብዙ ባላንጣዎቻቸው ጋር ተጋድለዋል፤ ተዋግተዋል፡፡ ይሁንና እሳቸውም ሆኑ ተከታዮቻቸው ከባላንጣዎቻቸው ጋር የተጋደሉት ሰዎች እስልምናን በጉልበት እንዲቀበሉ ለመጫን በሚል አይደለም፤ እነዚያ ባላንጣዎቻቸው ሊያጠፏቸው ስለተነሱባቸው ነው ራሳቸውን ለመከላከል የተዋጉት፡፡ ጠላቶቻቸው ከመካ ከተማ ጀምሮ ሊያጠፏቸው ሲዶልቱ፣ ሴራ ሲሸርቡና ቅጥረኞችን ሲልኩባቸው ነበር፡፡ ይባስ ብሎም “ሀይማኖታችንን አርክሶ አዲስ እምነት የጀመረው ሙሐመድ ተላልፎ ካልተሰጠን በስተቀር ከማንም ጋር ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ግንኙት እንዲያደርግ አይፈቀድለትም” ተብሎ ለሁለት ዓመታት ያህል ነብዩ በተገኙበት የበኒ ሐሺም ቤተሰብ ላይ ማዕቀብ ተጥሏል፡፡ የነቢዩ ቤተሰብም “ሙሐመድን አሳልፈን አንሰጥም” በማለት እቀባው እስኪነሳለት ድረስ ከመካ ከተማ ተሰዶ ለመኖር ተገዷል፡፡ በርሳቸው ተከታዮች ላይ የደረሰው ሰቆቃና ችግር ደግሞ በቀላሉ አይነገርም፡፡ በተለይ ደካሞችና ተከላካይ ያልነበራቸው እንደ አማር ቢን ያሲር እና ወላጆቹ፣ ኢትዮጵያዊው “ቢላል”፣ ወዘተ… የመሳሰሉት የሰቆቃና የስቃይ መሞከሪያ ሆነው ነበር ለማለት ይቻላል፡፡ ይህ ስቃይ ሲባባስ ነው ነብዩ ግማሾቹን ተከታዮቻቸውን በስውር ወደ ኢትዮጵያ የሰደዱት፡፡ በመጨረሻም ነቢዩና ተከታዮቻቸው በሙሉ ከመካ ወደ መዲና ለመሰደድ የበቁት ከቁሬይሽ መኳንንቶች ከሚመጣባቸው ጥቃትና በደል ለመሸሽ ሲሉ ነው፡፡
  የነቢዩ ጠላቶች ግን እዚያም አላረፉላቸውም፡፡ “ሙሐመድ ሀይል ገንብቶ እኛን ከማጥፋቱ በፊት እዚያ ሄደን ልናጥፋው ይገባናል” በማለት የክተት አዋጅ አውጀው እስከ መዲና ድረስ ሄዱላቸው፡፡ በዚህን ጊዜ ነው አላህ በቅዱስ ቁርኣን “ለነዚያ በእምነታቸው ምክንያት አላግባብ ለተፈተኑት ሙስሊሞች መዋጋት ተፈቀደላቸው” በማለት ጠላቶቻቸውን በጦርነት እንዲዋጉዋቸው መንገዱን ያሳያቸው፡፡ “ጂሃድ” (ተጋድሎ) የተሰኘው ጽንሰ-ሐሳብም ያኔ ነው የተፈጠረው፡፡
  “ጂሃድ” ቃሉ ራሱ እንደሚያመለክተው “ትግል” ወይንም “ተጋድሎ” ማለት ነው፡፡ ሐቀኛ ሰው ሐቁን ላለማስደፈር የሚያደርገው ትግል ነው በዚህ ስም የሚጠራው፡፡ አንድን ውጥን ከግብ ለማድረስ የሚደረግ ርብርብም “ጂሃድ” ሊባል ይችላል፡፡ ሀጢአተኛ ሰው ነፍሱን ከሐጢአት ለማጽዳት የሚያደርገው ትግልም ጂሀድ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንዶች አላግባብ “ቅዱስ ጦርነት” እያሉ ይፈቱታል፡፡ ፍቺውን ሲያሰፉትም “እስልምናን ለማስፋፋትና በሸሪዓ የሚተዳደር መንግሥት ለመመስረት የሚደረግ ጦርነት ነው” ይላሉ፡፡ ስህተት ነው፡፡ በጣም ስህተት! ጦርነት በባህሪው አውዳሚ ነው፡፡ የትኛውም ጦርነት “ቅዱስ” ሊባል አይችልም፡፡ የትኛውም ሀይማኖት ጦርነትን “ቅዱስ ነው” ብሎ አይባርክም፡፡ ነቢዩ ሙሐመድም ጦርነትን፣ ሁከትና ብጥብጥን አውግዘዋቸዋል፡፡
  ይሁንና አንተ የማታውቀው ጠላትህ አንተን አጥፍቶ ሀገርህን ሊወርስብህ ሲመጣብ ቆመህ አትጠብቀውም፤ የራስህን ሀይማኖት ትተህ የርሱን እምነት እንድትከተል ሲወጋህም በዝምታ አትመለከተውም፡፡ ያኔ በምትችለው መንገድ ሁሉ ትዋጋዋለህ፤ ቢቻል በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እንዲመለስ ታደርገዋለህ፤ እምቢዮው ካለ ግን በሚገባው የጦርነት ቋንቋ ታናግረዋለህ፡፡ “ጂሃድ” የሚባለውም እንዲህ ዐይነቱ ፍትሐዊ ትግል ነው፡፡
    ለሀገርህ፣ ለህዝብህና ለሀይማኖትህ የምታደርገው ተጋድሎ በሰላማዊ መንገድ ካልተቋጨ ብቻ ነው የጦርነትን አማራጭ የምትከተለው፡፡ ታዲያ ጦርነቱን የምታከናውነው እንዲሁ በዘፈቀደ አይደለም፡፡ ለ“ጂሃድ” ስትሰለፍ በማንኛውም መልኩ ገደቡን አታልፍም፤ አንተን በቀጥታ ከሚወጉት ውጪ ሌሎችን አታጠቃም፤ በጦርነቱ ውስጥ የሌለውን ሰላማዊ ህዝብ አትነካም፡፡ በተለይም በጦርነት እሳት ቀዳሚ ተጠቂ በሆኑት ህጻናት፤ ሴቶችና አረጋዊያን ላይ በጭራሽ እጅህን አታነሳም፤ በማሳ ላይ ያለ አዝመራ፣ በበረት ውስጥ ያሉ ከብቶች፣ ህዝብ የሚጠቀምበት የጉድጓድ ውሃ፣ መስጊድ፣ ቤተክርስቲያን፣ ምኩራብ (የአይሁድ ቤተ-ጸሎት) ወዘተ… አታጠቃም፡፡ እነዚህን እያጠፋህ “ጂሃድ እያካሄድኩ ነው” ብትል በእስልምና ሚዛን አንድም ተቀባይነት አታገኝም፡፡
*****
ለ“ጂሀድ” የወጣ ጦር ከውጊያ ሜዳው ከደረሰ በኋላ እንኳ ውዝግቡ በሰላም እንዲያልቅ የሚቻለውን ጥረት ያደርጋል፡፡ የሰላሙ ጥረት መፍትሔ ካላገኘ ብቻ ነው ወደ ውጊያ የሚገባው፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በህይወት ዘመናቸው 27 ዘመቻዎችን አድርገዋል፡፡ ከነዚህ ዘመቻዎች መካከል ውጊያ የተደረገው በስምንቱ ብቻ ነው፡፡ አስራ ዘጠኙ ዘመቻዎች ያለ አንዳች ጦርነት ነው የተጠናቀቁት፡፡
  ከዚህ ሌላም ሁኔታዎች አስገደድውት በጦርነት ውስጥ የገባ “ሙጃሂድ” (ታጋይ) ጦርነቱ እንዳይራዘም እና አውዳሚ ባልሆነ መልኩ እንዲጠናቀቅ የተለያዩ ዘዴዎችን መጠቀም ይኖርበታል፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በመዲና ዙሪያ ምሽግ በመቆፈር በአምስት እጥፍ የሚበልጣቸው የአህዛብ ሰራዊት በፍርሐት ተርበድብዶ እንዲመለስ አድርገውታል፡፡ እንዲሁም ደግሞ በስምንተኛው ዓመተ-ሂጅራ የመካ ከተማን በአነስተኛ ውጊያ (13 ሰው ብቻ የሞተበት) ለመቆጣጠር የቻሉት ሰራዊታቸውን በአራት አቅጣጫዎች በማሰማራት ከተማዋን ለመክበብ በመቻላቸው ነው፡፡ በዚህም በመካ ከተማ ላይ አንድም ውድመት እንዳይሰከት ለማድረግ ችለዋል፡፡
     በጂሃድ ውስጥ ሌላው ውግዝ ተግባር ደግሞ ጦርነትን በጠቅላላ ድምሰሳ (total destrcuction) ስልት ለማሸነፍ መሞከር ነው፡፡ የጠላትን ሀይል በሚቻለው ዘዴ ሁሉ ለማንበርከክ እስከ መጨረሻው ድረስ መታገል ይቻላል፡፡ ይህ ዘዴ ግን ከተዋጊው ውጪ በጦርነቱ ውስጥ ባልተሳተፈው ሲቪል ህዝብ ላይ አደጋ የሚያደርስ መሆን የለበትም፡፡ አንድን ከተማ መቆጣጠር ሲያቅትህ በጅምላ ጥቃት ከተማዋን ማውደም በጭራሽ ከ“ጂሃድ” አይቆጠርም፡፡
  ለምሳሌ ነቢዩ ሙሐመድና ተከታዮቻቸው “ሐዋዚን” ከሚባለው የዐረብ ጎሳ ተዋጊዎች ጋር ውጊያ ገጥመው አሸንፈውታል፡፡ በጦርነቱ የተሸነፉት የሀዋዚን ተዋጊዎች “ጧኢፍ” በምትባለው ከተማ መሸጉ፡፡ ነቢዩ ጣኢፍን ለበርካታ ቀናት ከበቡ፤ የሀዋዚን ተዋጊዎችም እጃቸውን እንዲሰጡ ጠየቁ፡፡ ባላንጣዎቻቸው ግን አምቢኝ አሉ (ጣኢፍ በዘመኑ ሉአላዊነት ያላት የከተማ መንግሥት ነበረች)፡፡ ይባስ ብሎም በከተማዋ ግንቦች ጫፍ ላይ ሆነው በነቢዩና በተከታዮቻቸው ላይ ልዩ ልዩ የባለጌ ስድቦችን ያወርዱ ጀመር፡፡ ይሁንና ነቢዩ በምላሹ ተናድደው የጧኢፍ ከተማዋን አላወደሟትም፡፡ የሀዋዚን ተዋጊዎችን እንቅስቃሴ በዐይነ ቁራኛ የሚጠብቅ ጦር በከተማ አቅራቢያ መድበው ለራሳቸው በክብር ወደ መዲና ተመለሱ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ እዚያ የመደቡትን ጦር አስነሱ፡፡ ከዓመት በኋላ በጦርነት ያልተቻሉት የሀዋዚን ተዋጊዎች በራሳቸው ፈቃድ እጅ ሰጡ፡፡ ሁሉም በፍላጎታቸው እስልምናን ተቀበሉ፡፡
   ይህ የነቢዩ አድራጎት ያስገርማል፡፡ “ጧኢፍ” ነቢዩ በመልዕክተኛነት ከተላኩ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ስደትን የሞከሩባት ከተማ ናት፡፡ ነቢዩና ጥቂት ተከታዮቻቸው ወደ ከተማዋ ደርሰው ነዋሪቿ እስልምናን እንዲቀበሉ ጠየቋቸው፤ በከተማዋ ለመኖር እንዲፈቀድላቸውም ለመኑ፡፡ የጧኢፍ ነዋሪዎች ግን ነቢዩን የድንጋይ ውርጅብኝ አከናነቧቸው፤ ጧኢፍ ውስጥ የነበሩ ህጻናትና ታዳጊዎች ተሰባስበው ያንን አሰቃቂ ትርኢት በጩኸትና በዘፈን አዳመቁት፡፡ የትኛውም ከተማ ነቢዩን በእንደዚያ ዓይነቱ ወራዳ ምግባር አላስተናገደም (በመካ ከተማ ካዩት ስቃይና ሰቆቃ በስተቀር)፡፡ ከአስር ዓመታት በኋላ ያቺ ከተማ በነቢዩና በተከታዮቻቸው ተከበበች፡፡ በከተማዋ የመሸጉት የሀዋዚን ተዋጊዎች አስነዋሪ ስድቦችን እየተሳደቡ ተፈታተኗቸው፡፡ ይሁንና ነቢዩ የጥንቱን የድንጋይ ወገራ ትዝታቸውን ከሀዋዚን ጦረኞች ስድብ ጋር በመደመር ከተማዋን አላጠፏትም፡፡ በራሷ ጊዜ ከእጃቸው እንደምትገባ በመተማመን ወደ መናገሻ ከተማቸው ተመለሱ፡፡ በዚያ ዘመን የነበረ ሌላ መሪ እንዲህ ሲያደርግ አልታየም፡፡ አንድ ከተማ እጅ አልሰጥም ካለች ከተማዋን ማውደም ነው እንጂ ጦሩን ይዞ ወደ ኋላ መመለስ በዚያ ዘመን አይታወቅም፡፡ ሰውዬው ግን ነቢይ ነውና  ለ“ጠቅላላ ድምሰሳ” (total destrcuction) አልቸኮለም፡፡  የኢራቅ ጽንፈኛ ሚሊሻስ?…. አሜሪካስ?…. እስራኤልስ?.. አል-ሸባብስ?… ሂትለርስ?… ሁሉም በጠቅላላ ድምሰሳ (total destrcuction) ስልት ያምናሉ፡፡
*****
“ጀሃድ” በትንኮሳ የሚፈጸምም አይደለም፡፡ ሌሎች ሳይደርሱብህ የሰው ሀገርና ድንበር ወርረህ “ለእስልምና ነው የምዋጋው” ማለት የለም፡፡ በቅዱስ ቁርኣን በተጻፈውም ሆነ ነቢዩ በአንደበታቸው ባስተማሩት መልዕክት ውስጥ “እንዲሁ ከመሬት ተነስህ ሌሎችን ተዋጋ” የሚል ነገር አናነብም፡፡ እያንዳንዱ እርምጃህ የመነሻ ምክንያት ሊኖረው ግድ ይላል፡፡ ነቢዩ ያካሄዷቸው ዘመቻዎች በሙሉ በቂ ምክንያቶች ነበሯቸው፡፡ ጠላቶቻቸው ከተነኮሷቸው በኋላ ነው ነቢዩ ለጂሃድ የወጡት (ሰ.ዐ.ወ)፡፡ በኋለኞቹ ሁለት ዓመታት ውስጥ የተደረጉት ዘመቻዎች ደግሞ ነቢዩ ዐረቢያ ማዕከላዊ መንግሥት መሪነታቸው የሀገሩን ጸጥታና ዳር ድንበር ለማስከበር ያካሄዷቸው ናቸው እንጂ ውጊያ በመሻት የተደረጉ አልነበሩም፡፡
      ከነቢዩ ህልፈት በኋላ የነቢዩ ተከታዮች ከፋርስና ከሮማዊያን ጋር ያኳሄዷቸው ጦርነቶች ብዙ መነሻዎች ነበሯቸው፡፡ ከጀርባቸው የነበረው ዋነኛ ምክንያት ግን አንድና አንድ ብቻ ነው፡፡ ይህም ሮማዊያንና ፋርሶች ከዐረቢያ የተነሳውን አዲስ ሀይል በቅኝ ግዛቶቻቸው ላይ የተጋረጠ አደጋ አድርገው መውሰዳቸው ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ሁለቱም ሀይሎች የነቢዩን መንግሥት በስውርና በግልጽ ውጊያ ሊያጠፉት ሞክረዋል፡፡ ይሁንና አዲሱ ሀይል የሚበገርላቸው አልሆነም፡፡ ሮማዊያንንና ፋርሶችን በከፍተኛ ወኔ እየተዋጋቸው ከያዟቸው የእስያ፣ የመካከለኛው ምስራቅና የሰሜን አፍሪቃ (ስፔንን ጨምሮ) ቅኝ ግዛቶች በሙሉ አባሮአቸል፡፡ ከነዚህ ቄሳራዊ ቅኝ ገዥዎች የነጠቃቸውን ግዛቶች በአዲስ የኸሊፋ መንግሥት ስር አጠቃሎአቸዋል፡፡ የሮም መንግሥት በደንበኛው መሬቱ (hinterland) ላይ ከተገደበ በኋላ ከሙስሊሞች ጋር በጉርብትና የመኖር ፖለሲን ስለተከተለ ከርሱ ጋር የሚደረገው ጦርነት ቆሟል፡፡ የፋርሶች መንግሥት ግን በጄ አላለም፡፡ በሙስሊሞች ላይ ትንኮሳ መፈጸሙንና ከተሞችን ማውደሙን ስለቀጠለ ውድቀቱን በራሱ እጅ አፋጥኗል፡፡
*****
የጅሃድ እስላማዊ ግንዛቤ ይህ ነው፡፡ በትክክል ጂሃድ ማድረግ ማለት እንዲህ ነው፡፡ አላህ ታጋዮችን ሊረዳቸው ቃል የገባው ይህንን መርህ ተከትለው የታገሉ እንደሆነ ነው፡፡ ነቢዩንና ተከታዮቻቸውን “አንድ ከልቡ የሚታገል ሙጃሂድ ለአስር ጠላቱ ይበቃል” በማለት ያወደሳቸው በዚህ መመሪያ መሰረት ይታገሉ ስለነበር ነው፡፡ ጥቂቶች ሆነው በብዙ እጥፍ የሚበልጧቸውን የሮምና የፋርስ የጦር ሀይሎችን ለማሸነፍ የበቁት ሐቁን ይዘው በወኔና በቆራጥነት ስለተዋጓቸው ነው፡፡
  የዘመናችን ጽንፈኛ ሀይላት ከዚህ መርህ ጋር በጭራሽ የሚተዋወቁ አይደሉም፡፡ ለጂሃድ የጨፈገገ ትርጓሜ እየሰጡት በአሉታዊ መልኩ እንዲታይ አድርገውታል፡፡ ቅዱስ ቁርአንንና የነቢዩን ሐዲሶች እንዳሻቸው እየተረጎሙ የድብቅ ፍላጎታቸው ማስፈጸሚያ ያደርጉአቸዋል፡፡ በሴፕቴምበር 11/2001 እንደታየው አውሮፕላኖችን እየጠለፉ በሺህ የሚቆጠሩ ንጹሐንን ይፈጃሉ፡፡ በህዝብ ማጓጓዣ ባቡሮችና አውቶቡሶች ላይ ቦንብ ያጠምዳሉ፡፡ የመኖሪያ ህንጻዎችን በፈንጂ ያጋያሉ፡፡ እንደ ሶማሊያው አል-ሸባብ የአንድ አባት ልጆችን ያጋድላሉ፡፡ እንደ ቦኮ-ሀራም በምንም ውስጥ የሌሉ ሴቶችን እየጠለፉ መደራደሪያ ያደርጉአቸዋል፡፡ አልፎ ተርፎም የነርሱን ድርጊት የማይደግፈውን “ሙስሊም አይደለህም” እያሉ ይረሽኑታል፡፡ ይህ ነው እንግዲህ ጽንፈኝነት ማለት!
  ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ዓይነት ጽንፈኛ ቡድኖች ወደፊት እንደሚነሱ ተንብየዋል፡፡ የጽንፈኝነቱ የመጀመሪያው ምልክትም በኸሊፋ ዑመር (ረ.ዐ) ዘመን ታይቷል፡፡ ከዚያም የዑስማን መንግሥት በነዚህ ጽንፈኞች ታውኳል፤ ኸሊፋ ዑስማንም በነርሱ እጅ ተገድለዋል፡፡ በኸሊፋ ዓሊ ዘመን ደግሞ ጽንፈኞቹ ለይቶላቸው ከኸሊፋቸው ጋር በግልጽ ተዋግተዋል፤ ከኸሊፋው ጋር የቆሙትንም “ከእስልምና የወጡ ካፊሮች” በማለት ፈርጀዋቸዋል፡፡ በመጨረሻም የዓሊ ህይወት በነርሱ እጅ ጠፍቷል፡፡
   በዚህ ዘመን የተነሱት ጽንፈኞችም የነዚያዎቹ ተከታዮች ናቸው፡፡ ነገር ግን ክርር ያለው አካሄዳቸው ለየትኛውም ሰው ስለማይመች ተቀባይነት አያገኙም፡፡ በተጨማሪም ከክር የቀጠነው ጽንፈኝነታቸው አንድነታቸውን ጠብቀው እንዲሄዱ አያስችላቸውም፡፡ በታሪክ እንደታየው እንዲህ ዓይነት ቡድኖች በጥቂት ዓመታት ውስጥ በብዙ ቡድኖች ተፈረካክሰው እርስ በረስ መባላት ይጀምራሉ፡፡ በዓሊ ዘመን የተነሱት የ“ኸዋሪጃ” ጽንፈኞች ተፈረካክሰው እንደጠፉት ሁሉ በሌሎች ዘመናት የተነሱ ጽንፈኞችም ራሳቸውን በራሳቸው ያጠፋሉ፡፡ የአሁኖቹም መንገዳቸው ይኸው ነው፡፡

===ጽንፈኞችና ሽብር===

ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ለጂሃድ የወጣ ሰው የሚዋጋው መሳሪያ ታጥቆ ለውጊያ ከተሰለፈ ሀይል ጋር ነው፡፡ በውጊያው ውስጥ ባልተሰለፉ ሲቪል ዜጎች ላይ ጥቃት ማድረስ በፍጹም አይፈቀድለትም፡፡ የዘመናችን ጽንፈኞች ግን ከዚህ መርህ ጋር የሚተዋወቁ አልሆኑም፡፡ ዓላማቸውን ለማሳካት የሚጠቀሙበት ዋነኛ ዘዴ ሽብር ፈጠራ ነው፡፡ ጽንፈኞቹ በሚያደርሱት ጥቃት የሚሸበሩትም ሆኑ የሚሞቱት በአብዛኛው ሲቪሎች ናቸው፡፡ ንጹሐንን እየቀጠፉ ነው “ለእስልምና ነው የምንታገለው” የሚሉት፡፡
እስልምና ግን እንዲህ የዘቀጠ ርዕዮት አይደለም፡፡ ኢስላም የሰው ልጅ ከየትኛውም ፍጥረት በላይ የተከበረ መሆኑን ነው የሚያስተምረው፡፡ ቅዱስ ቁርኣን “አንዲት ነፍስን ያለ ሐቅ ያጠፋ ሰው በምድር ላይ የሚኖሩ ሰዎችን በሙሉ እንደገደለ ይቆጠራል” ይላል፡፡ ጽንፈኞች በምን ማስረጃ ነው ይህንን ቁርኣናዊ ህግ የሚሞግቱት?… “ለአሜሪካ መንግሥት ታክስ የሚከፍል ሁሉ የእስልምና ጠላት ነው” የሚል ሎጂክ በጭራሽ ኢስላማዊ መሰረት የለውም፡፡ ኢስላም በግልጽ በተደነገገ ህግ ነው የሚተገበረው፡፡ እንደ ኒኮሎ ማኪያቬሊ “ወደ እውነት ለመድረስ በብዙ ውሸቶች ውስጥ መዘፈቅ” ወይንም “ዜጎችን እየጨረሱ ወደ ውጤት መድረስ” የሚል መመሪያ በእስልምና ውስጥ የለም፡፡ ሽብር ምን ጊዜም ቢሆን ሽብር ነው፡፡

==ጽንፈኞችና ብዝሐነት==

የጽንፈኛውን የኢራቅ ሚሊሻ መነሳትን ተከትሎ የዓለም ሚዲያዎችን የተቆጣጠረው ሌላኛው ርዕስ “ሙስሊም ያልሆኑ ወገኖች በግዴታ እስልምናን እንዲቀበሉ ተደርገዋል” የሚል ነው፡፡ ጽንፈኞች ለዚህኛው አድራጎታቸውም “እስልምና እንደዚያ እንድናደርግ አዟል” ይሉናል፡፡ ለመሆኑ ቅዱስ ቁርኣን “ሌሎችን በግዴታ እንዲሰልሙ አድርጉ” ይላል? በፍጹም! ቅዱስ ቁርኣን እንዲህ ነው የሚለው፡፡

لَاۤ اِکۡرَاہَ فِی الدِّیۡنِ ۟ۙ قَدۡ تَّبَیَّنَ الرُّشۡدُ مِنَ الۡغَیِّ

“በሀይማኖት ማስገደድ የለም፤ ቀጥተኛው ጎዳና ቀጥተኛ ካልሆነው በርግጥ ተብራርቷል”
(አል-በቀራህ-266)

ነብዩ እና ተከታዮቻቸው በዘመናቸው የነበሩ የበርካታ እምነት ተከታዮች እምነታቸውን እንዲቀይሩ ያላስገደዱት በዚሁ ቁርአናዊ መመሪያ ስለሚመሩ ነው፡፡ ክርስቲያኖች፣ አይሁዶች፣ ዞራስትሪያኖች (መጁስ)፣ ሳቢኢን (የጥንታዊ የሜሶጶጣሚያ እምነት ተከታዮች)፣ ቂብጢዎች (የጥንታዊ የግብጽ እምነት ተከታዮች)፣ የዚዲዎችና ሌሎችም ከሙስሊሞች ጋር በሰላም ይኖሩ ነበር፡፡ አሁን እንደምንሰማው ቤተክርስቲያንና ምኵራብ ማፍረስም ሆነ ቄስና ካህን መግደል በዚያ ዘመን በጭራሽ አልነበረም፡፡ ጽንፈኞች የሚነዙት ወሬ ከየትኛውም እስላማዊ መመሪያ ጋር አይጣጣምም፡፡
   በዚያ ዘመን ነቢዩና ተከታዮቻቸው በግልጽ የተዋጉት ከአይሁዶች ጋር ነው፡፡ ይህም በሀይማኖታቸው ምክንያት አይደለም፡፡ አይሁዶቹ የመዲና ከተማን ደንብ አክብረው ለመኖር የገቡትን ቃል-ኪዳን አፍርሰው ከነቢዩ ጠላቶች ጋር በመወገን ስለተዋጓቸው ነው፡፡ በዚህም  የተነሳ አይሁዶቹ ለጥፋታቸው ተመጣጣኝ ቅጣት ከፍለው በከተማዋ እንዲኖሩ፤ አሊያም ከተማዋን ለቀው እንዲሄዱ ምርጫ ተሰጣቸው፡፡ ጥቂቶች ቅጣቱን ለመክፈል ተስማማሙ፡፡ አብዛኞቹ ግን ከተማዋን ለቀው ወደ ተቡክ (አሁን ሳዑዲና ዮርዳኖስ ድንበር) ተሰደዱ፡፡
  ነብዩ በሀይማኖት የተነሳ ከክርስቲያኖች ጋር የተጋጩበት የታሪክ አጋጣሚ የለም፡፡ በዑመር (ረ.ዐ) ዘመን ደግሞ አስገራሚ ድርጊት ተፈጽሟል፡፡ በወቅቱ ሙስሊሞቹ ከሮማዊያን ጋር በፍልስጥኤም ምድር እየተዋጉ ነበር፡፡ ሙስሊሞቹ አሸንፈው ከተማዋን በያዙበት ቀን ዑመር ሳይጠበቁ ወደ ከተማዋ መጡ፡፡ እኚህ መሪ የትልቅ ግዛት ገዥ ሆነው በመናኛ አለባበስ፣ ያለ አንዳች አጃቢ ወደ ከተማዋ በመግባታቸው ብዙዎች ተደነቁ፡፡ ከሁሉም በላይ በድርጊቱ የተደነቁት ግን የእየሩሳሌም ፓትሪያርክ ነበሩ፡፡ ፓትሪያርኩ “ የሙስሊሞቹ መሪ ይህ መናኛ ልብስ የለበሰ እና አጃቢ የሌለው ሰውዬ ከሆነ በርግጥም ይህ ሰው ቅዱስ ነው” በማለት ደመደሙ፡፡ በመሆኑም ዑመር ከቤተ ክርስቲያናቸው ገብተው በሙስሊሞቹ ስርዓት “ሰላት” እንዲሰግዱ ጋበዟቸው፡፡ ዑመርም ግብዣውን ተቀበሉ፡፡ ነገር ግን ከቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ሳይገቡ በቅጥረ-ግቢው ውስጥ “ሁለት ረከዓ” ሰላት ሰገዱ፡፡ (ዑመር ይህንን ያደረጉት ሙስሊሞች ወደፊት “ዑመር የሰገደበት ቤተክርስቲያን ለኛ የተገባ ነው” የሚል ውዝግብ ሊፈጥሩ ይችላሉ በሚል ምክንያት ነው እንጂ ወደ ውስጥ መግባቱን ጠልተውት አይደለም” )፡፡
*****
ሙስሊሞች፣ ክርስቲያኖች፣ አይሁዶችና ሌሎችም የሃይማኖት ቡድኖች ከዚያ ዘመን ጀምሮ ለብዙ ዘመናት በጉርብትና አብረው ኖረዋል፡፡ የኦቶማን ቱርኮች ኢምፓየር እስከፈረሰበት ድረስ በሙስሊሞች የበላይነት በተመራው ኢስላማዊ ኸሊፌት ውስጥ ክርስቲያኖችም ሆኑ አይሁዶች ሀይማኖታቸውን በግዳጅ እንዲቀይሩ የተደረገበት ዘመን የለም፡፡
  አዳዲሶቹ ጽንፈኞች ግን ከነብዩ ዘመን አስቀድሞ በመካከለኛው ምስራቅ የሚኖሩ የልዩ ልዩ እምነት ተከታዮች ሀይማኖታቸውን እንዲቀይሩ ያስገድዱአቸዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት ትምህርት ከእስልምና ጋር ሆድና ጀርባ ነው፡፡ እስልምና እንደዚህ ዓይነት ርዕዮት ያለው ቢሆን ኖሮ በዛሬዋ ኢራቅ ምድር ከአስር የሚበልጡ ጥንታዊ የሀይማኖት ቡድኖች ባልተገኙም ነበር (ከነዚህ ቡድኖች መካከል አንዳንዶቹ ከጥንቱ የሀሙራቢ ዘመን የተረፉ ናቸው)፡፡

==ጽንፈኞች እና ዘመናዊነት==

እነዚህ ጽንፈኞች እስልምና ኋላቀር እምነት ተደርጎ እንዲታይ የሚፈልጉ አሻጥረኞችም ይመስላሉ፡፡ በየትኛውም ሀገር ሲነሱ በቅድሚያ የሚፈጽሟቸው ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛው በጥንት ዘመናት የተሰሩ ታሪካዊ መዘክሮችንና ቅርሶችን ማውደም ነው፡፡ ሁለተኛው ዘመን ያፈራቸውን የቴክኖሎጂ ትሩፋቶች እርም ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም የሚጠቅሱት ምክንያት “በእስልምና ያልተፈቀዱ ናቸው” የሚል ነው፡፡ ይሁንና የእስልምና አስተምህሮ ከነዚህ ጽንፈኞች አባባል ጋር በጭራሽ አይገጣጠምም፡፡ እስቲ በምሳሌዎች ላስረዳ፡፡
  “ጣሊባን” የተባለው ጽንፈኛ ቡድን እ.ኤ.አ በግንቦት ወር 2001 በአፍጋኒስታን ምስራቃዊ ክፍል የነበሩ ሁለት የቡድሃ ሀውልቶችን በታንክ ደምስሷል፡፡ ለእርምጃው የሰጠው ምክንያት “ሀውልት በእስልምና የተከለከለ ነው” የሚል ነው፡፡ በርግጥ በሰው ልጅ አምሳል ሀውልት ማቆም በእስልምና አይፈቀድም፡፡ ይሁንና እስልምና “አዲስ ሀውልት ለራሳችሁ አትገንቡ” ነው የሚለው እንጂ “በጥንት ዘመን የተገነቡ  ሀውልቶችን አፍርሱ” የሚል ትእዛዝ አላስተላለፈም፡፡ እንደዚያ ቢሆን ኖሮ በግብጽ፣ በሶሪያ፣ ኢራቅ (ሜሶጶጣሚያ)  እና ኢራን (ፋርስ) የሚታዩትን በሺህ የሚቆጠሩ ሀውልቶችን በዛሬው ዘመን በቁማቸው ባለገኘናቸው ነበር፡፡
  አዎን! እስልምና ወደነዚህ ሀገራት የገባው ነቢዩ “እጅግ ምርጥ ትውልድ” ባሉት በመጀመሪያው የሰሐባ ትውልድ ዘመን ነው፡፡ ሰሐባዎቹ በግብጽ ያሉትን ፒራሚዶች፣ ቤተ-መቅደሶች፣ ስፊኒክሶችና ልዩ ልዩ ሐውልቶች (ታላቁን የራምሰስ ሀውልትን ጨምሮ) “ንክች” አላደረጓቸውም፡፡ በኢራቅና በኢራን የነበሩትንም እንደዚያው፡፡ እነዚያን ጥንታዊ ሀውልቶችንና ቤተመቅደሶችን ማፍረስ በእስልምና የታዘዘ ቢሆን ኖሮ የነቢዩ ሰሐባዎች አንዳቸውንም ሳያስቀሩ ድምጥማጣቸውን ባጠፏቸው ነበር፡፡ ይሁንና ሰሓቦች እንደ አሁኖቹ ጽንፈኞች አዕምሮ ቢስ አልነበሩም፡፡ እነዚያ ጥንታዊ ግንባታዎች በልዩ ልዩ የዘመን ፈተናዎች ውስጥ አልፈው ወደነርሱ ዘመን እንደተሸጋገሩ ይረዳሉ፡፡ ስለዚህ አንድም ዓይነት የማጥፋት ሙከራ ሳይፈጽሙባቸው ጥንት እንደነበሩት ተዋቸው፡፡
  የዘመናችን ጽንፈኞች ሌላው መታወቂያ ዜጎች ዘመን ባፈራቸው የቴክኖሎጂ ውጤቶችና ቀልጣፋ አሰራሮች እንዳይጠቀሙ መከልከል ነው፡፡ ጽንፈኞቹ በዚህ አስተሳሰባቸው በጥንታዊ ጋርዮሽ ዘመን ከነበረ ሰው ጋር እንኳ የሚወዳደሩ አይደሉም፡፡ በጣም ልብ የሚነካው እስልምና በነዚህ ቴክኖሎጂዎችና ውጤታማ አሰራሮች መጠቀምን የሚከለክል አድርገው መለፈፋቸው ነው፡፡  “እግር ኳስ ለምን አየህ” በሚል ምክንያት ዜጎችን በጅራፍ መግረፍን የመሳሰሉ ቅጣቶችንም ይፈጽማሉ፡፡
  እስልምና አዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶችና በተቀላጠፈ አሰራር መጠቀምን ይከለክላል?… በጭራሽ!! ነቢዩ እንዲህ ዓይነት ትምህርት በጭራሽ አላስተማሩም፡፡ አላህ በቅዱስ ቁርኣን እርም ካደረጋቸው ድርጊቶችና መጠቀሚያዎች ውጪ ነቢዩ እርም ያደረጉት የተለየ ነገር የለም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ነቢዩና ተከታዮቻቸው ድሮ የማያውቁት አዲስ ፈጠራ ወይንም አዲስ አሰራር እንዳለ ሲነገራቸው በስራ ላይ በማዋል አንደኛ እንደነበሩ የህይወት ታሪካቸው ያስረዳል፡፡ ለምሳሌ ያህል እነዚህን መጥቀስ እንችላለን፡፡
·        ነቢዩ በዘመናቸው ለነበሩት ነገሥታት ደብዳቤ መጻፍ አስፈለጋቸው፡፡ አንዱ ባልደረባቸው “ደብዳቤው ከርስዎ የተላከ መሆኑን የሚያረጋግጥ ማህተም ያስፈልግዎታል፤ ማህተም ቢያስቀርጹ መልካም ይመስለኛል” አላቸው፡፡ ነቢዩ የማህተም አስፈላጊነት ሲነገራቸው እምቢ አላሉም፡፡ ሃሳቡን ወዲያውኑ ተቀብለው አዲስ ማህተም አስቀረጹ፡፡
·        የቁሬይሽ ተዋጊዎች በመዲና ላይ ሶስተኛ ዙር ወረራ ሊፈጽሙ ተነሱ፡፡ ከቁሬይሾች ጋር በርካታ ማህበረሰቦች ማበራቸውም ተሰማ፡፡ ይህም ወሬ ለነቢዩ ደረሳቸው፡፡ ነቢዩ በጉዳዩ ላይ ከባልደረቦቻቸው ጋር ሲወያዩ ሳልማን አል-ፋርሲ የሚባለው ባልደረባቸው “በከተማችን ዙሪያ ምሽግ ብንቆፍር ጠላቶታችንን በቀላሉ መመለስ እንችላለን” አላቸው፡፡ ሳልማን የፋርስ (ኢራን) ተወላጅ ነው፡፡ በሀገሩ ሲደረግ ያየውን ነው ለነቢዩ የነበረው፡፡ እስከዚያ ጊዜ ድረስ “ምሽግ” በዐረቦች ዘንድ የማይታወቅም ነበር፡፡
በመሆኑም ነቢዩ ምሽግ በመቆፈሩ ብልሃት ተገረሙ፡፡ በተግባር ላይ ሊያውሉትም ተነሱ፡፡ የመዲና ከተማን ከዳር እስከ ዳር በምሽግ ቁፋሮ አጠሯት፡፡ የመካ ቁረይሾች እየፎከሩ ወደ መዲና ሲመጡ ምሽጉ ገደባቸው፡፡ በፈረስና በእግር እየዘለሉ ምሽጉን ለማለፍ ቢሞክሩም ምንም አልተሳካላቸውም፡፡ ይህ ሁኔታ ሌሊቱን ከጣለው ከባድ ዝናብ ጋር ተዳምሮ በጣም አስፈራቸው፡፡ በመሆኑም እቃቸውን እንኳ በወጉ ሳይሰበስቡ ወደመጡበት ፈረጠጡ፡፡
·        በርካታ መልዕክተኞች ወደ ነቢዩ ዘንድ ይመጡ ነበር፡፡ ታዲያ አንዱ የነቢዩ ባልደረባ “ንጉሦችና የጦር መሪዎች መልዕክተኞችን በሚቀበሉበት ጊዜ የአዘቦት ልብሳቸውን አይለብሱም፤ ለየት ያለ ልብስ ለብሰው በርሱ ላይ ካባ ይደርባሉ” አላቸው፡፡ ነቢዩም ምክሩን ተቀብለው በተግባር ላይ አውለውታል፡፡
·        በኸሊፋ ዑመር ጊዜ ታሪኮችን መመዝገብ ተጀምሮ ነበር፡፡ ታሪክ የሚመዘገብበት የቀን መቁጠሪያ ደግሞ በዐረቦች ዘንድ አይታወቅም፡፡ በመሆኑም ዑመር የነቢዩ ስደት (ሂጅራ) እንደ መነሻ ሆኖ እንዲያገለግል ውሳኔ አስተላለፉ፡፡ ይህም ተግባራዊ ሆኖ እስከ አሁኑ ዘመን ድረስ እየተሰራበት ይገኛል፡፡
·        አምስተኛው ኸሊፋ ሙአዊያ ኢብን አቡ-ሱፍያን ደግሞ በተማከለ አሰራር ደብዳቤዎችን ከግለሰቦች ተቀብሎ የሚያከፋፍል ተቋም በመመስረት በዓለም ታሪክ አዲስ አሰራር አስተዋውቀል፡፡ ዛሬ “ፖስታ ቤት” የሚባለውን ተቋም የፈጠሩት ኸሊፋ ሙአዊያ (ረ.ዐ) ናቸው፡፡
·        ዛሬ ዓለም በሙሉ የሚጠቀምበት “የሂንዱ-ዐረብ” የቁጥር ዘዴ የመጨረሻ ቅርጹን ያገኘው በሙስሊሞች አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ለሂሳብ አቆጣጠር የሚያመቸው “የዜሮ ጽንሰ ሃሳብ” የተፈለሰፈው በ8ኛው ክፍለ ዘመን በባግዳድ ከተማ ነው፡፡
·        የሳይንስና የምርምር ዘርፍ ከፍተኛ እመርታ እንዲሳይ ያደረጉትን አል-ጀብራ፣ አልጎሪዝም እና ሎጋሪዝም የተሰኙ የሂሳብ ስልቶችን የፈጠረው ሙሐመድ ኢብን ሙሳ አል-ኸዋሪዝሚ የተባለ ሙስሊም ሳይንቲስት ነው፡፡
·        ሌላም ብዙ ብዙ መዘርዘር ይቻላል፡፡

እነዚያ የጥንት ሙስሊሞች በአዳዲስ ፈጠራዎች ከመጠቀም አልፈው ለራሳቸውም ልዩ ልዩ ፈጠራዎችን አስተዋውቀዋል፡፡ በአዳዲስ ፈጠራዎች መጠቀም “ውግዝ” ቢሆን ኖሮ ነቢዩና ባልደረቦቻቸው “እርም፤ ነው አትጠጉት” በማለት ክልከላ ያስቀምጡበት ነበር፡፡ ይሁንና የዘመናችን ጽንፈኞች እንዲህ ዓይነቶቹን ታሪኮች ያነበቧቸው አይመስሉም (በጣም የሚያስቀው ነገር ለራሳቸው በዘመናዊ ጠመንዣዎችና በኢንተርኔት ይጠቀማሉ፣ ሌሎችን ግን ከመጠቀም ያግዳሉ)፡፡
 ይህ በፈጠራዎች የመጠቀም ጉዳይ ከተነሳ ዘንድ ግን አንድ ነገር መታወቅ አለበት፡፡ ይኸውም በጥቅም ላይ የሚውለው አዲስ ፈጠራና አሰራር የአላህ ክልከላ ያደረገበትን ድንበር ማለፍ የሌለበት መሆኑ ነው፡፡ ለምሳሌ ማንኛውም የእስልምና ሙፍቲ “አስካሪ መጠጥ ለጤና ይጠቅማችኋል፣ ድንበር ሳታልፉ ጠጡ” በማለት ውሳኔ መስጠት አይችልም፡፡ ቁማርን ህጋዊ ማድረግም በፍጹም አይቻልም፡፡ በሰብዓዊ መብት ስም ግብረ-ሰዶምን ህጋዊ ማድረግም ተቀባይነት የለውም፡፡ ጽንፈኞቹ ግን በነዚህ ላይ ልል አቋም ያላቸው ነው የሚመስሉት፡፡ ለምሳሌ እርግጠኛ ማስረጃ ባይኖረንም ከጽንፈኞቹ መካከል ብዙዎቹ በአደንዛዥ እጽ ንግድ ውስጥ የተዘፈቁ መሆናቸውን እንሰማለን፡፡

===እንደ ማጠቃለያ===

  እነዚህ ጽንፈኞች በየትኛውም ሙስሊም አልተወከሉም፡፡ እስልምናን እንወክላለን ቢሉም ማንም አይቀበላቸውም፡፡ ይሁንና አንዳንድ ሰዎች እስልምናን በነዚህ ጽንፈኞች አድራጎት ሊመዝኑት ይሞክራሉ፡፡ ይህንን ጽንፈኝነት እንደ ሰበብ በመቁጠር እስልምናን ጥላሸት ለመቀባት ይሞክራሉ፡፡ ታዲያ ጽንፈኞቹ እንዲስፋፉ እና እንዲጠናከሩ እያደረጉ ካሉት ምክንያቶች አንዱ የእስልምና ጠላቶች በሀይማኖቱ ላይ የሚያካሄዱት ይህንን የመሰለ የስም ማጥፋት ዘመቻ ነው፡፡ ሙስሊሞችም ሆኑ ሙስሊም ያልሆኑ ምሁራን እንዲህ ዓይነት ምግባሮችን አይተው እንዳላዩ ሆነው ማለፍ የለባቸውም፡፡ በተቻለው መጠን ጽንፈኞቹ የሚፈጽሙት አድራጎት ነቢዩ ያስተማሩትን እስልምና እንደማይወክል ማስረዳት ይገባቸዋል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ “ጽንፈኝነት” በሀይማኖት ያልተገደበ ስለመሆኑም መታወቅ አለበት፡፡ ጽንፈኛ ቡድኖች ከየትኛውም ሀይማኖት ሊመነጩ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ በጥንት ዘመን “Masada” የተሰኘ የአይሁዳዊያን ጽንፈኛ ቡድን ነበር፡፡ ዛሬም በእስራኤል ውስጥ በመቶ የሚቆጠሩ እጅግ ጽንፈኛ ቡድኖች አሉ፡፡ በ7ኛው ክፍለ ዘመን ደግሞ “ኸዋሪጃ” የሚባሉት ጽንፈኞች ከሙስሊሙ ዓለም ተነስተዋል፡፡ በዘመናችንም አል-ሸባብ፣ አል-ቃኢዳ፣ ቦኮ ሀራም የመሳሰሉት ተፈጥረዋል፡፡ ከክርስትናው ዓለምም በ“መስቀል ጦርነት” የሚያምኑ ጽንፈኛ ቡድኖች በተለያዩ ዘመናት ተነስተዋል፡፡ በዘመናችን በሰሜን ኡጋንዳ ጫካዎች ውስጥ መሽጎ ልዩ ልዩ ሰቆቃዎችን የሚፈጽመው Lords Resistance Army የተባለው ሚሊሺያ “ኡጋንዳን በወንጌልና በአስርቱ ትዕዛዛት እመራታለሁ” እያለ የሚለፍፍ ጽንፈኛ ቡድን ነው፡፡ ከሶስት ዓመታት በፊት ከሰማኒያ የሚበልጡ ንጹሃንን የጨፈጨፈው የኖርዌይ ጽንፈኛ ግለሰብም በሃይማኖቱ ክርስቲያን ነው፡፡ በጃፓን ሜትሮ (የምድር ውስጥ ባቡር) ላይ በመርዝ ጋዝ ንጹሃንን የፈጀው የኡም-ሺኖሮኪዮ ሀይማኖታዊ ቡድን “የፈጣሪን ትዕዛዝ” እተገብራለሁ የሚል ጽንፈኛ ነው፡፡ በሀይማኖት የማያምኑ (ማቴሪያሊስቶች፣ ኮሚንስቶች ወዘተ…) ጽንፈኛ ቡድኖችም በልዩ ልዩ ዘመናት ተነስተዋል፡፡ ስለዚህ ጽንፈኞች የትኛውንም ሀይማኖት መጠቀሚያ በማድረግ ሊነሱ እንደሚችሉ መታወቅ ይገባል፡፡ በዚህ ረገድ ሚዲያዎች ወደ አንድ ሀይማኖት ብቻ ጣታቸውን መጠንቆላቸውን በማቆም ሐቁን እየተነትኑ ማስረዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡
   በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ ጽንፈኞቹ የሚፈጽሙትን አድራጎት በመመልከት ብቻ አሜሪካና አጋሮቿ የሚፈጽሟቸውን ህገ-ወጥ ድርጊቶች የሚያወድሱ ሰዎችም መታረም አለባቸው፡፡ አሜሪካ ለብሄራዊ ጥቅሟ ስትል የምትፈጽማቸው ድርጊቶች ሁሉ በህገ-ወጥነት መታየት አለባቸው እንጂ ጽንፈኞቹ ከሚፈጽሟቸው አድራጎቶች ጋር መተካካት የለባቸውም፡፡ አሜሪካ ኢራቅን መውረሯ መቼም ቢሆን ህገ-ወጥ ነው (የርሷ እርምጃ ነው የአሁኑን ትርምስምስ ያስከተለው)፡፡ እስራኤል ፍልስጥኤምን አላግባብ ይዛ ህዝቡን መጨፍጨፏ መቼም ቢሆን ህገ-ወጥ ነው፡፡ የጽንፈኞችን ነውረኛ ድርጊቶች ተመልክቶ እነዚህን ህገ-ወጥ ስራዎች ማወደስ በምንም መልኩ ተቀባይነት የለውም፡፡ ሁሉም በየራሱ መንገድ መመዘን አለበት፡፡
*****
---
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 7/2006
ገለምሶ-ሀረርጌ
------

ይህ ጽሑፍ የኔ (የጸሐፊው) ወጥ ስራ ነው እንጂ ጥቂት ሰዎች እንደገመቱት “ትርጉም” አይደለም፡፡ ከዚህ በፊት በየትኛውም ቋንቋ አልቀረበም፡፡ ጽሑፉ ብዙዎች ዘንድ እንዲደርስ Share ብታደርጉት ምስጋናዬ እጅግ የላቀ ነው፡፡ በመጽሔትና በጋዜጣ ማሳተምም ይቻላል፡፡ 

Monday, August 11, 2014

ትኩረት-ከውጪ ቋንቋዎች ለተወረሱ ቃላት


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
--------
የሀገራችን ቋንቋዎች ከውጪ ቋንቋዎች በርካታ ቃላትን ወርሰዋል፡፡ ይህም ከብሉይ ዘመን ጀምሮ ይታይ የነበረ ክስተት ነው፡፡ የመወራረሱ አድማስ ስፋቱን የጨመረው ግን በአስራ ዘጠነኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በቀጣዮቹ አንድ መቶ ሀያ ዓመታት ውስጥ የታዩት ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ክስተቶች የሀገራችን ቋንቋዎችን ለውጪ ቋንቋዎች ተጽእኖ የበለጠ ክፍት እንዲሆኑ አድርገዋቸዋል፡፡  

  ታዲያ ከሶስት ሺህ ከሚልቁት የውጪ ቋንቋዎች መካከል ለሀገራችን ቋንቋዎች ብዙ ቃላትን ለማውረስ የበቁት አራቱ ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱም ዐረብኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ ጣሊያንኛና እንግሊዝኛ ናቸው፡፡ የቱርክ እና የጀርመን ቋንቋዎችም ጥቂት ቃላትን ለሀገራችን ቋንቋዎች አበርክተዋል፡፡
*****
   ዐረብኛ በሀገራችን ቋንቋዎች ላይ ተጽእኖ ለመፍጠር የቻለው በዋናነት የእስልምና ሀይማኖት የአምልኮና የትምህርት ቋንቋ ስለሆነ ነው፡፡ በመሆኑም ከእስልምና እምነት ጋር በተያያዘ ለአምልኮና ለትምህርት አገልግሎት ላይ የሚውሉ ቃላት በአብዛኛው ከዐረብኛ የተገኙ ናቸው፡፡ ለምሳሌ መስጊድ/መስጂድ፣ ኢማም፣ ቃዲ፣ አዛን፣ መጅሊስ፣ መድረሳ ወዘተ… የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ በሂደት ደግሞ የዐረብኛ ቃላት በአምልኮ ውስጥ ካላቸው አስፈላጊነት አልፈው በተራው ሰው ንግግር ውስጥም ገብተዋል፡፡ ይህ ክስተት በስፋት የሚስተዋለው ግን አብላጫው ነዋሪ ህዝብ ሙስሊም በሆነባቸው እንደ ወሎ፣ ሀረርጌ፣ ባሌ፣ ጅማ፣ ሶማሊ (ኦጋዴን)፣ ቤኒሻንጉልና አፋር አካባቢዎች ነው፡፡ በነዚህ አካባቢዎች ከሚነገሩት ቋንቋዎች “መርሐባ”፣ “አሕለን”፣ “ፉጡር”፣ “ሀድራ”፣ “ሙሐባ”፣ “መናም”፣ “ጂስም”፣ “አዛ”፣ “ኩርሲ”፣ “ማዕና”፣ “ዒልም”፣ “አስል” እና ሌሎች በርከት ያሉ የዐረብኛ ቃላትን በቀላሉ ለይቶ ማውጣት ይቻላል፡፡

ታዲያ የዐረብኛ ቃላትን የመውረሱ ተግባር በኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች ብቻ የተገደበ አይደለም፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በእኩል ደረጃ የሚጠቀምባቸው በርከት ያሉ የዐረብኛ ቃላትንም ወርሰናል፡፡ ይህም ክስተት የተፈጠረው ከንግድ መስፋፋት ጋር ነው፡፡ በተለይ እስከ አስራ ዘጠነኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ድረስ የሀገራችንን ንግድ በበላይነት ተቆጣጥረው የነበሩት ሲራራ ነጋዴዎች ዐረብኛን በንግድ ቋንቋነት በስፋት ይጠቀሙበት የነበረ ከመሆኑ የተነሳ በሀገራችን ቋንቋዎች ውስጥ መሰረት ያልነበራቸው በርካታ ቃላት እንዲወረሱ ምክንያት ሆነዋል፡፡ ለምሳሌ ዛሬ የአማርኛ ቃላት አድርገን የምንጠቀምባቸው እንደ  ሀዋላ፣ ጉምሩክ፣ ሰንዱቅ፣ ሱቅ፣ መጋዘን፣ ሽርክና፣ ወኪል፣ ሰነድ፣ ደላላ፣ መሃለቅ ወዘተ የመሳሰሉት የአማርኛ ቃላት ምንጫቸው ዐረብኛ ነው፡፡ እንደ ሐዲድ፣ ባቡር እና መኪና የመሳሰሉ ቃላትም ከዐረብኛ ነው የተወረሱት፡፡ ይሁንና ዐረብኛና አማርኛ ሴማዊ ቋንቋዎች በመሆናቸው የሚጋሯቸውን ቃላት እንደ ውርስ ቃላት ማየት ስህተት ነው፡፡ ለምሳሌ ሰላም፣ ደም፣ ቤት፣ ፎቅ፣ ክፍል፣ ዐይን፣ ፈረስ፣ ዘመን፣ ሐሩር፣ ሚዛን የመሳሰሉ ቃላት በሁለቱም ቋንቋዎች ውስጥ አሉ፡፡ ሁለቱም ቋንቋዎች ሴማዊ በመሆናቸው ነው እነዚህን ቃላት የተጋሩት፡፡ የነዚህ ቃላት መነሻ የሁሉም ሴማዊ ቋንቋዎች አባት እንደሆነ የሚታመንበት ግንደ-ሴማዊ ቋንቋ (Proto-Semetic Language) ነው፡፡
*****
     አዲስ አበባን ከጅቡቲ ጋር የሚያገናኘው የኢትዮ-ጅቡቲ የምድር ባቡር መስመር ሲሰራ ደግሞ ፈረንሳይኛ ወደ ሀገራችን ቋንቋዎች እየሰረገ መግባት ጀምሮ ነበር፡፡ የተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤትም በ1910ዎቹ ውስጥ ሲከፈት የፈረንሳይኛ ተጽእኖ በጣም ተጠናክሯል፡፡ የዘመኑ የትምህርት ካሪኩለምም ከፈረንሳይ የተቀዳ በመሆኑ የትምህርት ቤቱ ተማሪዎችና ምሩቃኑ ፈረንሳይኛን ይናገሩ ነበር፡፡ በነዚያ ምሩቃን በተሞላው ሲቪል ሰርቪስም ሆነ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ውስጥ ፈረንሳይኛ እንደ ሁለተኛ ቋንቋ ሆኖ አገልግሏል፡፡ ለመንግሥታዊ አገልግሎት የሚያስፈልጉ ሰነዶችና የስራ መመሪያዎችም ከፈረንሳይኛ ሲተረጎሙ ነው የኖሩት (የመጀመሪያው ህገ-መንግሥትም ከፈረንሳይ የተቀዳ ነው)፡፡  በዚህም ሂደት በርካታ የፈረንሳይኛ ቃላት በአማርኛ ተወርሰዋል፡፡ ከፈረንሳይኛ ከወረስናቸው ቃላት መካከል “ኦፊሴል”፣ “ሞኖፖል”፣ “ሌጋሲዮን”፣ “ኮሚስዮን”፣ “ፔኒስዮን”፣ “ዲክላራሲዮን”፣ “ኦፕራሲዮን”፣ “ካሚዮን”፣ “ፍሪሲዮን”፣ “ሬኮማንዴ”፣ “ለገሀር (ላጋር)፣ “ቡፌ”፣ “ሌሲ ፓሴ”፣ “ዴኤታ”፣ “ ካፌ”፣ “ራንዴቩ”፣ የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡

   የኢጣሊያ ወረራ ከተወልን ማስታወሻዎች መካከል ትልቁ በሀገራችን ቋንቋዎች ውስጥ የሚታየው የጣሊያንኛ ተጽእኖ ነው፡፡ በአማርኛ፣ ኦሮምኛና ትግርኛ ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ የጣሊያንኛ ቃላትን መቁጠር ይቻላል፡፡ በተለይም በቀድሞ ዘመናት ከተሽከርካሪ እና ትራንስፖርት እንቅስቃሴ፣ እንዲሁም ከኢንዱስትሪ ጋር በተያያዘ ከሚሰራባቸው ቃላት መካከል ብዙዎቹ የጣሊያንኛ መሰረት ያላቸው ናቸው፡፡ ዛሬም ድረስ የነዚያ ቃላት ቅሪቶች በሀገርኛ ቋንቋዎች ውስጥ ይስተዋላሉ፡፡ ከጣሊያንኛ ከወረስናቸው ቃላት መካከል “ፓስታ”፣ “ማካሮኒ”፣ “ላዛኛ”፣ “ስፓጌቲ”፣ “ስልስ” (ሳልሳ)፣ “አሮስቶ”፣ “ፋብሪካ”፣ “ጋዜጣ”፣ “ሊቼንሳ”፣ “ፉርኖ”፣ “ቪያጆ” (በመኪና የሚደረግ ጉዞ)፣ “ላቫጆ”፣ “ካሮሴሪያ”፣ “ካምቢዮ”፣ “ሞቶሪኖ”፣ “ፍሬን”፣ “ፊልትሮ”፣ “ሳልቫታዮ”፣ “ፖርቶ መጋላ”፣ “ፒንሳ”፣ “ቺንጊያ” ፣ “ፈረፋንጎ”፣ “ኩሽኔታ” “ኪያቤ”፣ “ካቻቢቴ” “ባሌስትራ”፣ “ቸርኬ” “ፒስታ” “ኮማርዳሬ” “ጎሚኒ” “ሮንዴላ” “ዲፍረንሻሌ” “ስፒናታ” “ሳልዳሬ” “ቡኮ”፣ “ፖምፓ” (ቧንቧ)፣ “አውታንቲ”፣ “ማኖ”፣ “ኢሊ ጎሬ”፣ “ቴስታ”፣ “ፑንቶ”፣ “ቦጦሎኒ”፣ “ካምቦ” ወዘተ…. የመሳሰሉት ተጠቃሽ ናቸው፡፡
*****
ጣሊያኖች ከተባረሩ በኋላ እንግሊዝኛ በሀገርኛ ቋንቋዎች ውስጥ ሰርጾ መግባት ጀመረ፡፡ በተለይ እንግሊዞች በኢትዮጵያ ውስጥ በነበሩባቸው አስር ዓመታት የእንግሊዝኛ ቃላት በሀገራችን ቋንቋዎች በብዛት ተወረሱ፡፡ በዚያን ጊዜ ከተወረሱት ቃላት ውስጥ እስከ አሁን ድረስ በአገልግሎት ላይ ያሉትን እንደ “ፖሊስ”፣ “ባንክ”፣ “ሚኒስቴር”፣ “ካፒታል”፣ “ኤሌክትሪክ”፣ “ኮሌጅ”፣ “አካዴሚ”፣ “ኤክስፐርት”፣ “ዲሬክተር” የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እንዲሁም እንደ ፕሮፌሰር፣ ዶክተር፣ ኢንጂነር፣ ጄኔራል፣ አድሚራል፣ ኮሞዶር፣ ኮሎኔል እና ካፒቴን የመሳሰሉ የማዕረግ ስሞችም የተወረሱት ከእንግሊዝኛ ነው፡፡

    በእንግሊዝኛ ወደ ኢትዮጵያ መምጣት የተነሳ ፈረንሳይኛና ጣሊያንኛ በሀገራችን ቋንቋዎች ላይ የነበራቸው ተጽእኖ በፊት ከነበረበት ደረጃ ሊያድግ አልቻለም፡፡ ነገር ግን በሀገራችን ቋንቋዎች የተወረሱት የጣሊያንኛና የፈረንሳይኛ ቃላት በዘመኑ አገልግሎት መስጠታቸውን አላቆሙም፡፡ ለምሳሌ በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመን “ኮሚሲዮን” እንጂ “ኮሚሽን” የሚባል የአማርኛ ቃል አይታወቅም፡፡ ከፈረንሳይኛና ከጣሊያንኛ የተወረሰ የሀገርና የከተማ አጠራርም ቢሆን በአማርኛ ቋንቋ አንዳች ለውጥ ሳይደረግበት ያገለግል ነበር፡፡ እንደ ምሳሌም “ቤልጅግ”፣ “ስዊስ”፣ “ሎንዶን”፣ “መስኮብ”፣ “ብሩክሴል” የመሳሰሉትን የሀገርና የከተማ ስሞች መጥቀስ ይቻላል፡፡

    ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት ውድቀት በኋላ ግን ከፈረንሳይኛና ከጣሊያንኛ የተገኙ የሀገርና የከተማ ስያሜዎች ከእንግሊዞች በተወረሱ ስሞች ተተክተዋል፡፡ በዚህም መሰረት “ቤልጅግ” ወደ “ቤልጅየም”፤ “ስዊስ” ወደ “ስዊትዘርላንድ.፣ “ብሩክሴል” ወደ “ብራሰልስ”፣ “መስኮብ”ም ወደ “ሞስኮ” ተለውጠዋል፡፡ በመሆኑም ከልዩ ልዩ  ቋንቋዎች በተገኙ የቦታ ስያሜዎችና ቃላት ተውቦ ይታይ የነበረው አማርኛ የመኮማተር ባህሪን ለማዳበር ተገዷል፡፡

   ይህ ቀደምት ውርስ ስሞችን በእንግሊዝኛ አጠራሮች የመተካቱ ሂደት ሳያቋርጥ በመቀጠሉ ከሁለቱ ቋንቋዎች (ከፈረንሳይኛና ጣሊያንኛ) የተወረሱ የሀገር ስሞችን ከማራገፍ አልፎ በጥንታዊው አማርኛ ውስጥ መሰረት የነበራቸውን የሀገር ስሞችንም በእንግሊዝኛ ስያሜዎች መለወጥ ተጀምሯል፡፡ ለምሳሌ የዓለም ትልቋ ሀገር ከጥንት ጀምሮ በአማርኛ ስትጠራ “ሩሲያ” ነው የምትባለው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን “ራሽያ” የሚለው አጠራር እያየለ መጥቷል፡፡ “ስጳኝ” የሚለው ትክክለኛ የአማርኛ አጠራር “ስፔን” በሚለው የእንግሊዝኛ ቅጂ ተቀይሯል፡፡ “አርመን” የሚለው አጠራርም በ“አርሜኒያ” ተተክቷል፡፡ “ቤልጅግም” ወደ “ቤልጅየም” ተቀይሯል፡፡ “ቆጵሮስ” የሚለውን ጥንታዊ የአማርኛና የግዕዝ አጠራር “ሳይፕረስ” በሚለው አዲስ ደራሽ የቅጂ ስም የሚለውጡ ሰዎችም እየበረከቱ ነው፡፡ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን በኦፊሴል ያገለግሉ የነበሩት እንደ “ነምሳ” (አውስትሪያ) እና “ናርበጅ” (ኖርዌይ) የመሳሰሉ የሀገራት መጠሪያዎች በዚህ ዘመን በአማርኛ ቋንቋ አገልግሎት መስጠታቸውን አቁመዋል፡፡

   ለሌሎች አገልግሎቶች የሚውሉ የፈረንሳይኛና የጣሊያንኛ ውርስ ቃላትም ቢሆኑ የመጥፋት እጣ ደርሶአቸዋል፡፡ ለምሳሌ በዛሬው ዘመን ከፈረንሳይኛ በተወረሰው “ኮሚሲዮን” የሚገለገል ሰው የለም፡፡ በአማርኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች በስፋት ሲያገለግል የነበረው “ኦፕራሲዮን”ም በዚህ ዘመን “ቀዶ ጥገና” እና “ኦፕሬሽን” በሚሉት ስሞች ተተክቷል፡፡ “ፔኒሲዮን” የሚለው ቃልም ሙሉ በሙሉ አገልግሎቱን አቁሟል፡፡
*****
 “እነዚህ ቃላት ድሮውንም የውጪ ቃላት በመሆናቸው ከአማርኛ መጥፋታቸው የሚያስነሳው አቧራ የለም” ይባል ይሆናል፡፡ ነገሩን በታሪክና በአንትሮፖሎጂ መነጽር ካየነው ግን ትልቅ ጉዳት አለው፡፡ ምክንያቱም የነዚህ ቃላት በቋንቋዎቻችን ውስጥ መኖር የ20ኛው ክፍለ ዘመን ታሪካችን የተጓዘበትን መንገድና የእኛነታችንን ህብርነት የሚያሳይ በመሆኑ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው የፈረንሳይኛ ቃላት በአማርኛ ውስጥ በመኖራቸው ተገርሞ “ይህ እንዴት ተከሰተ?…” የሚል ጥያቄ ቢያቀርብ የጅቡቲው ምድር ባቡርና የተፈሪ መኮንን ትምህርት ታሪክ ይተረክለታል፡፡ በጣሊያንኛ ቃላት ላይ ጥያቄ ለሚያቀርብ ሰውም የአምስቱ ዓመቱ የኢጣሊያ ወረራና የአርበኞቻችን የተጋድሎ ታሪክ ይነገረዋል፡፡

በሌላ በኩል በአንድ ቋንቋ ውስጥ ያሉ ውርስ ቃላትና ሀረጋት የታሪካዊ ምርምር መሰረቶች የሚሆኑበት አጋጣሚም ሞልቷል፤ ቃላቱና ሐረጋቱ እንደ ታሪክ ማስረጃ የሚያገለግሉበት ሁኔታም አለ፡፡ ብዙ የታሪክ እንቆቅልሾች በቃላትና በሀረጋት መነሻነት ሊፈቱ ችለዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ዛሬ በግዴለሽነት ከኦሮምኛና ከአማርኛ ቋንቋ ውስጥ እየተወገዱ ያሉት የፈረንሳይኛና የጣሊያንኛ ውርስ ቃላቶቻችን ጠሊቅ የሆኑ ኪነታዊ ስራዎች የሚወጠኑበት መሰረቶች ሆነው ሲያገለግሉ ታይተዋል፡፡ እንደምሳሌም የቴዲ አፍሮን “ሼ-መንደፈር” እና “ላምባ ዲና”ን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ቴዲ እየረሳናቸው ያሉትን አንድ የፈረንሳይኛና አንድ የጣሊያንኛ ቃላትን ወስዶ የሁለት ውብ ዜማዎች መሰረት አድርጎአቸዋል፡፡ በመሆኑም ውርስ ቃላቱን በነበሩበት ሁኔታ ማስቀጠሉ ተገቢ ነው፡፡  

   በዚህ ረገድ የሀገራችን ሚዲያዎችና ፕሬሶች ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ እያካሄዱት ያለውን አጥፊ ሚና መግታት አለባቸው፡፡ ፈረንሳይም ሆነ እንግሊዝ፣ ጣሊያንም ሆነ ጀርመን ሁሉም ባዕድ ነው፡፡ ፊት የመጣውንና በህዝቡ ውስጥ የቆየውን ቃል አስወግዶ በሌላ የባዕድ ቃል መተካት በምንም መልኩ የስኬት መለኪያ አይሆንም፡፡ በተለይ ግን በረጅም ዘመናት የታሪክ ጉዞአችን ያዳበርናቸውንና እኛ ብቻ የምንጠቀምባቸውን ጥንታዊ የሀገርና የከተማ አጠራሮች (ሩሲያ፣ ቆጵሮስ፣ አርመን፣ ደማስቆ፣ ስዊስ፣ ኡክራኒያ፣ ቱርክ፣ ኢጣሊያ፣ ሮማ፣ አቴና፣ ሶሪያ፣ ፍልስጥኤም፣ ሊባኖስ፣ ግብጽ ወዘተ.. የመሳሰሉትን) ከእንግሊዝኛ በተኮረጁ ስሞች (ራሽያ፣ ሳይፕረስ፣ ደማስከስ፣ ፓለስታይን፣ ኢጂፕት ወዘተ..) መተካት ይቅርታ የማይሰጠው ጥፋት ነው፡፡ ቴክኖሎጂንና የተቀላጠፈ አሰራርን መኮረጅ እንጂ ነባር ቃላትን ማጥፋት የእድገት መሰረት ሊሆን አይችልም፡፡ ዐረቦችም ሆኑ ፈረንጆች፣ ቱርኮችም ሆኑ ህንዶች እንዲህ ዓይነት ጥፋት ሲያጠፉ አይታዩም፡፡ እኛም ይህንኑ ፈለግ መከተል አለብን፡፡ ስለዚህ የሚመለከተው ሁሉ ለጉዳዩ አጽንኦት ሊሰጠው ይገባል፡፡
--------
አፈንዲ ሙተቂ
ግንቦት 13/2006
ሸገር-አዲስ አበባ


“አንድ በላተኛ” ጠመንጃዎች በኢትዮጵያ


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
---------
በዲሞትፈር፣ አርገው ገፍተር
በወጨፎ፣ አርገው ቀፎ
በሰናድር፣ አርገው ክንችር
በምንሽር፣ ያዘው አብሽር
ባጭር አልቤን፣ ደረት ልቤን፡፡

(ወዳጄ ካሳሁን አለማየሁ ከጻፈው ሀገርኛ ግጥም የተወሰደ)
*****
ጠመንዣ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሀገራችን የገባው በ16ኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ ነበር፡፡ በዚያ ዘመን ከሰለሞናዊ አጼ ንጉሠ ነገሥቶች ጋር ሲፋለሙ የነበሩት የአዳል ሱልጣኔት ገዥዎች ናቸው ጠመንዣን ወደ ሀገራችን ያስገቡት፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ የሰለሞናዊ ነገሥታት ወታደሮችም ጠመንዣን ለመታጠቅ ችለዋል፡፡ ወታደሮች ሙሉ በሙሉ በጠመንዣ መዋጋት የጀመሩት ግን በአድዋው ጦርነት ማግስት ነው፡፡ እስከ አድዋው ጦርነት ድረስ ጦርና ጎራዴን ከጠመንጃ ጋር በማፈራረቅ ይጠቀሙ ነበር፡፡

    እንደዚህም ሆኖ ግን የያንዳንዱ ዘመን የቴክኖሎጂ ውጤት የሆነ ጠመንዣ ወደ ኢትዮጵያ ይገባ እንደነበረ ይታመናል፡፡ የውጪ መንግሥታት ለኢትዮጵያ ነገሥታት ከሚያቀርቧቸው ገጸ-በረከቶች መካከል አንዱ ጠመንዣ ስለመሆኑም በስፋት ተጽፏል፡፡ ከነዚያ የጠመንዣ ዓይነቶች መካከል አንዳንዶቹ እስከዚህ ዘመን ድረስ ይደነቃሉ፡፡ ለምሳሌ በጅማ ከተማ በሚገኘው የአባጅፋር ሙዚየም ውስጥ አነስተኛ ከዘራ የሚመስል አንድ ጠመንዣ አለ፡፡ ያ መሳሪያ ጠመንዣ መሆኑን የምትረዱት አስጎብኚው አተኳኮሱን ሲያሳችሁ ብቻ ነው፡፡ በሌላ ቦታ ብታዩት ትንሽዬ ከዘራ ነው ብላችሁ የምታልፉት ይመስለኛል (ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለማሪያም እንደዚያ ዓይነት የከዘራ ጠመንዣ እንደነበራቸው አንድ የቀድሞ ጦር አባል ጥቅምት 1985 በታተመው በእፎይታ መጽሔት ላይ አስነብበውን ነበረ)፡፡

   ጠመንዣ በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት የተሰራጨው በሀያኛው ክፍለ ዘመን ነው፡፡ ከነዚያ ጠመንዣዎች ውስጥ አንዳንዶቹ ዛሬም ድረስ ያገለግላሉ፡፡ አንዳንዶቹ ግን የአገልግሎት ዘመናቸው አብቅቶ ስሞቻቸው ብቻ ቀርተውናል፡፡ በዚህ ጽሑፍ ውስጥ በጥቅሉ “አንድ በላተኛ” የሚባሉትን ጠመንጃዎች በጥቂቱ እንቃኛለን፡፡
*****
“አንድ በላተኛ” ኦቶማቲክ ያልሆኑ ጠመንዣዎች በወል የሚጠሩበት የአማርኛ ስም ነው፡፡ እነዚህ ጠመንዣዎች በኦሮምኛ “ተከ ኛቴ” (takka nyaattee) ይባላሉ፡፡ ጠመንዣዎቹ እንዲህ እየተባሉ የሚጠሩት አንድ ጥይት ብቻ ስለሚጎርሱ ሳይሆን የጎረሱትን ጥይት አንድ በአንድ የሚተኩሱ በመሆናቸው ነው፡፡ ይህም ማለት ጠመንዣው ተቀባብሎ አንዴ ከተተኮሰበት በኋላ እንደገና ማቀባበልን ይጠይቃል፡፡ በመሆኑም “አንድ በላተኛ” ከተሰኘው ስያሜ በተጨማሪ “ቆመህ ጠብቀኝ” የሚል የፉገራና የስላቅ ስያሜም ወጥቶላቸዋል፡፡

    “አንድ በላተኛ” የሆኑ ጠመንዣዎች በአብዣኛው አምስት ያህል ጥይቶችን ነው የሚጎርሱት፡፡ እነዚህም ጥይቶች ትልልቆች ናቸው፡፡ ጥይቱ ከተተኮሰ በኋላ በርቀት ላይ የሚገኝን ነገር መትቶ የመጣል ሀይሉም ከፍተኛ ነው ይባላል፡፡ በመሆኑም “አንድ በላተኛ” ጠመንዣዎች በተለይ ለአደን ስራ በጣም ተመራጭ ናቸው፡፡

  በድሮው ዘመን ለውጊያ ይፈለጉ የነበሩት እነዚህ “አንድ በላተኛ”ዎች በሰለጠነው ዓለም እምብዛም አያገለግሉም፡፡ በኛ ሀገር ግን አስከ አሁን ድረስ በጥበቃ ስራ ላይ የተሰማሩ ዘበኞችና የአካባቢ ሚሊሻዎች በብዛት የሚያነግቱት “አንድ በላተኛ” ጠመንጃዎችን ነው፡፡  

   በሀገራችን ውስጥ የብዙ ሀገራት ስሪት የሆኑ “አንድ በላተኛ” ጠመንዣዎች አሉ፡፡ እነዚህን ጠመንዣዎች የምንጠራባቸው የተለምዶ ስያሜዎች በፋብሪካ የተሰጧቸው የሞዴል ስሞች ናቸው ብሎ ለመናገር ይከብዳል፡፡ የሆነው ሆኖ በኛ ሀገር ሲያገለግሉ ከነበሩት የጠመንዣ ዓይነቶች መካከል ጥቂቶቹን እንተዋወቃቸው፡፡  

1.      ምንሽር፡

“ምንሽር” ጣሊያን ሰራሽ ጠመንዣ ነው፡፡ በሀገራችን ውስጥ በስፋት ያገለግል ነበር፡፡ በተለይም የኢትዮጵያ አርበኞች የጣሊያን ወራሪዎችን የተፋለሙበት ዓይነተኛው የጠመንዣ ዓይነት ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ ጠረፎችና በትግራይ ገጠሮች በአገልግሎት ላይ ያለ መሆኑ ይነገራል፡፡ በሌሎች ክልሎች ግን እምብዛም አይታይም፡፡  

2.     አልቤን:

የአልባኒያ ስሪት የሆነ የጠመንጃ ዐይነት ነው፡፡ በዚህ ዘመን ብዙም የማይታየው ይህ ጠመንጃ በኢጣሊያ ወረራ ዘመን ከፍተኛ አገልግሎት ሰጥቷል፡፡

3.     ውጅግራ፡

ይህኛው ጠመንዣ ድምጹ ብራቅ ነው ይባልለታል፡፡ እንደ ከርከሮ እና ጅግራ ያሉት እንስሳት ወደ ሰብል ማሳ እንዳይጠጉ ለመከላከል ከተፈለገ አንድ የውጅግራ ጥይት ይበቃቸዋል፡፡

4.     ረሽ፡

ብዙ ጊዜ ለአደን ስራ የሚያገለግል ነው፡፡ ለዚህም ያግዝ ዘንድ በጠመንዣው ላይ የማነጣጠሪያ “ቴሌስኮፕ ተገጥሞለታል፡፡ ብዙ ሰዎች “መተሬ” (sniper) እያሉ የሚጠሩት ጠመንዣ እርሱ ሳይሆን ይመስለኛል፡፡

 ይህ ጠመንዣ ጥይት በሚጎርስበት ጊዜ ከሰደፉ በኩል ሰበር ብሎ ይቆለመማል፡፡ በተጨማሪም ሁለት አፈሙዝ ነው ያለው፡፡ ጥይቱ ከተተኮሰ በኋላ በአየር ላይ ስለሚበተን እንደ ጅግራ፣ ቆቅና ዳክዬ መሳሰሉ አዕዋፋት በመንጋ በሚበሩበት ወቅት ለማደን ተመራጭ ነው፡፡ ረሽ በሰሜን ኢትዮጵያ ገጠሮች “ግንጥል” የሚል ስያሜ እንዳለው “እንዳላማው አበራ” የሚባል የፌስቡክ ጓደኛዬ አጫውቶኛል፡፡

5.     ዲሞትፈር

በኢትዮጵያ ውስጥ በብዛት የተሰራጨ የጠመንጃ ዓይነቶች አንዱ ነው፡፡ የዘንጉ ርዝማኔ ይለያያል፡፡ ከዚህ ጠመንዣ ጋር በተያያዘ በሀገራችን ውስጥ ታሪካዊ እና አወዛጋቢ የሆነ አንድ አባባል ተፈጥሯል፤ “ዲሞን በዲሞትፈር” የሚል፡፡ አባባሉ የተፈጠረው በዘመነ ቀይ ሽብር ነው፡፡ “ዲሞ” እየተባሉ የተጠሩት የኢህአፓ አባላትና ደጋፊዎች ናቸው፡፡ (“ዲሞ” የኢህአፓ ልሳን ከነበረችው “ዲሞክራሲያ” ጋዜጣ ስያሜ ላይ የተቀነጨበ ነው)፡፡

   ይህ አባባል ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰማው ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም ጥር 26 ቀን 1969 በተቀናቃኝ የደርግ አባላት ላይ  የወሰዱትን እርምጃ ለመደገፍ በሚል በቀጣዩ ቀን በተዘጋጀው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ነው፡፡ ብዙ ጸሐፍት እንደሚሉት “ዲሞን በዲሞትፈር” የሚለውን አባባል ፈጥረው ወደ አደባባይ ያወጡት የመኢሶን አመራሮች ናቸው፡፡ መኢሶን ግን ነገሩን ያስተባብላል፡፡ ያም ሆነ ይህ አባባሉ “ዲሞትፈር” ጠመንዣ በቀይ ሽብር አፈጻጸም ውስጥ የነበረውን ሚና የሚያስረዳ ይመስለኛል፡፡

ዲሞትፈር በሀገራችን ውስጥ አሁንም በስፋት ያገለግላል፡፡ ይሁንና በጎንደርና ጎጃም ክፍለ ሀገራት ይበልጥ የሚታወቀው “ጓንዴ” በሚለው ስም ነው፡፡
  
6.     ቺኮዝ


በደርግ ዘመን የመጨረሻ ዓመታት በቀበሌ ደረጃ የተደራጁ የአብዮት ጥበቃ ጓዶች ሲታጠቁ የነበሩት ጠመንዣ ነው፡፡ ከስያሜው ለመረዳት እንደሚቻለው ጠመንጃው የተሰራው በቼኮዝሎቫኪያ ነው፡፡ ቼኮዝ ግራጫ ቀለም ያለው ጠመንዣ ነው፡፡

ቺኮዝ በጣም አደገኛ መሳሪያ ነው፡፡ ጥይቱ ወደ ሰውነት ሲገባ ቀዳዳው ትንሽ ነው፡፡ ሲወጣ ግን አካልን በሰፊው ቦድሶ ነው የሚወጣው፡፡ አንድ ሰው በቺኮዝ መመታቱን ለማወቅ ጥይቱ የገባበትንና የወጣበትን ቦታ ብቻ መመልከት ይበቃል፡፡

7.     ቤንቶቭ

“አንድ በላተኛ” ጠመንዣዎች ሁሉ ለመሸከም የማይከብደው ይህኛው ነው፡፡ የጠመንዣው እንጨትም ጥቁር ቡናማ መልክ አለው፡፡ በደርግ ዘመን የቀበሌ ጥበቃ ጓዶች ከቺኮዝ ቀጥሎ በብዛት ይታጠቁ የነበሩት ቤንቶቭን ነው፡፡
*****

እላይ ከዘረዘርናቸው መሳሪያዎች ሌላ ወጨፎ፣ ቤልጅግ፣ መውዜር፣ ሰናድር፣ ናስማሰር፣ ጉንጮ፣ ስኩዌር ወዘተ… የሚባሉ “አንድ በላተኛ” ጠመንዣዎች በሀገራችን ውስጥ በስፋት ያገለግሉ እንደነበረ መዛግብትና የቃል ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ ከላይ እንደገለጽኩት በውጪው ዓለም በከፍተኛ ፍጥነት እየተለወጠ በመሄድ ላይ የሚገኘው የመሳሪያና የወታደራዊ ምህንድስና ቴክኖሎጂ እነዚህን አንድ በላተኛ ጠመንጃዎች ከአገልግሎት ውጪ አድርጎአቸዋል፡፡ በሀገራችንም ውስጥ ብዙዎቹ ለጥበቃ ስራ ቢያገለግሉም በቅርብ ዓመታት አገልግሎታቸውን ማቋረጣቸው እንደማይቀር ይታመናል፡፡ ቢሆንም አባቶቻችን ታሪክ ሲሰሩ የነበሩት በነርሱ ነውና የያንዳንዱን መሳሪያ ስርጭትና የአገልግሎት አድማስ መዝግቦ ለመጪው ትውልድ ማቆየት ይገባል፡፡ ሰላም!!