Sunday, September 21, 2014

መሐመድ ወርዲ- ዘመን የማይሽረው አርቲስት

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
                                                       
----
 እነሆ ነፍስ የሆነውን አርቲስት ልናነሳው ወደድን!! ተወዳጅ፣ ጥበበኛ፣ ባለ ተሰጥኦ ከያኒ!! እውነተኛ የሙዚቃ ቀማሪ! ሱዳን ያፈራችው የምንጊዜም ጌጥ!! ከካይሮ እስከ ዑጋንዳ፣ ከጅቡቲ እስከ ማሊ ምንጊዜም እንደተወደደ ያለ የጥበብ ዋርካ!! ሙሐመድ ወርዲ!!

  “ወርዲ” ማለት ለሱዳኖች ንጉሥ እንደማለት ነው፡፡ እኛም ከአንጋፋ አርቲስቶቻችን ነጥለን አናየውም፡፡ በድሮ ጊዜ ወርዲን በፍቅር ሰምተነዋል፡፡ ዛሬም ወርዲን በመደጋገም እየሰማነው ነው፡፡
*****
ወርዲ ከልቡ ዘፋኝ ነው፡፡ ዘፈኖቹ ከኛ ጋር ከመዛመዳቸው የተነሳ እኛን እኛን ይሸታሉ፡፡ በርካታ ዜማዎቹ እኛ የምንጊዜም ምርጦች አድርገን ለምንወዳቸው ታዋቂ ዘፈኖቻችን መነሻ ለመሆንም በቅተዋል፡፡ ለምሳሌ አንጋፋው ድምጻዊ ጥላሁን ገሠሠ ያዜመውን “አንቺ ከቶ ግድየለሽም”ን ውሰዱት፡፡

አንቺ ከቶ ግድ የለሽም
ስለፍቅር አይገባሽም
ሁሉን ነገር እረስተሽው
ችላ ብለሽ ስለተውሽው
ቻልኩት ፍቅር ለብቻዬ፡፡

አዎን! ዛሬም ድረስ የዚህ ዜማ ተወዳጅነት አልቀነሰም፡፡ ለዚህ ዜማ መሰረቱ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ነው፡፡ ሙሐመድ ወርዲ ዘፈኑን ሲያዜመው እንዲህ ነበር ያለው፡፡

“አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ
ጠል ዐዛበክ ዋ ሱሃዲ
ዋ ሽጃያ አነ ዐዛቢ”

ታዲያ ሙሐመድ ወርዲ የተጫወተውን ዜማ ጋሽ ጥላሁን ወደ አማርኛ የመለሰው እንዲሁ በጋጠወጥነት አይምሰላችሁ፡፡ በነገሩ ውስጥ  የወርዲ ሙሉ ቡራኬ አለበት፡፡ በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመን የካርቱም መንገድ ለኛ አርቲስቶች የውሃ መንገድ ነበረ፡፡ ለሱዳኖችም ከዋዲ ሃልፋ ይልቅ ሸገር ነበር የምትቀርባቸው፡፡ እናም በዚህ ምልልስ መሀል የኛዎቹ አንጋፋዎች (ጥላሁን ገሠሠ፣ ምኒልክ ወስናቸው፣ አለማየሁ እሸቴ፣ ዓሊ ሸቦ፣ ዓሊ ቢራ ወዘተ..) እና የሱዳኖቹ አንጋፋ አርቲስቶች (አሕመድ አል-ሙስጠፋ፣ ሰይድ ኸሊፋ፣ ሙሐመድ ወርዲ፣ አብዱልከሪም አል-ካብሊ፣ አብዱል ዓዚዝ አል-ሙባረክ ወዘተ…) የአንድ ቤተሰብ ልጆች ሆነው ነበር፡፡ ሱዳኖቹ ያዜሙትን የኛዎቹ ወደ አማርኛ፣ ኦሮምኛና ሶማሊኛ እየመለሱ ይጫወቱታል፡፡ የኛንም ዘፈኖች ሱዳኖች በቋንቋቸው እየተረጎሙ ይዘፍኑታል፡፡ አንዳንዴ ዕድል ሲገጥማቸው ሁለቱም ዘፋኞች አንዱን ዜማ በአንድ መድረክ ላይ በየቋንቋቸው ይጫወቱታል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ነው እንግዲህ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ወደ አማርኛ የተመለሰው፡፡

አዎን!! እነ ጋሽ ጥላሁን እንደ አሁኖቹ ዘፋኞች (አንዳንዶቹን ማለቴ ነው) የሱዳንና የፈረንጅ ዜማን ወደ አማርኛ እየገለበጡ “የራሴ ድርሰት ነው”  ብለው ሊያሞኙን አይከጅሉም፡፡ ዋናው አርቲስት ባለበት ጭምር እየዘፈኑ ያሳዩትና “እንዴት ነው! አበላሽቼብህ ይሆን?” በማለት ምክርና እገዛ ይጠይቁታል፡፡ ሱዳናዊው አርቲስትም በሰማው ነገር ላይ የራሱን አስተያየት ይሰጣል፡፡ የኛዎቹም ከሱዳናዊያኑ አርቲስቶች የሚሰጣቸውን አስተያየት ተንተርሰው እጅግ የተሻለ ስራ ይሰሩና ህዝቡን እንካችሁ ይሉታል፡፡ ለዚያም ነበር ስራው የሚዋጣላቸውና ዘመን ተሻጋሪ የሚሆንላቸው፡፡

በዚህ ስሌት ወደኛ ቋንቋዎች ከተቀየሩት ተወዳጅ የሱዳን ዜማዎች መካከል የጥላሁን ገሠሠ “እዩዋት ስትናፍቀኝ” (ሰይድ ኸሊፋና ኢብራሂም አውድ በጋራ ከዘፈኑት ዘፈን የተወሰደ)፣ የአሰፋ አባተ “ሸግዬ ሸጊቱ” (ከአሕመድ አል-ሙስጠፋ “ሐቢቢ በኪቱ” የተወሰደ)፣ የምንሊክ ወስናቸው “ስኳር” (ከአብዱልከሪም አል-ካብሊ “ሱከር” የተወሰደ) የዓሊ ቢራ “ኦፊ ረፋ ቡልታ” (ከሙሐመድ ወርዲ “ያ ኑረል-ዐይን” የተወሰደ) ይጠቀሳሉ፡፡
                                                                          *****
    በርካታ የሀገራችን የሙዚቃ ወዳጆች ከመሐመድ ወርዲ ዜማዎች መካከል ለ“ገመር ቦባ” እና ለ“ቲስዐተ ዐሸር ሰና” (ብዙዎች የሚያውቁት  “ሰበርታ” በሚለው ስም ነው) ልዩ ፍቅር አላቸው፡፡ ሆኖም ሱዳኖች በአንደኛ ደረጃ የሚያሰልፏቸው ሌሎች በርካታ የወርዲ ዜማዎች አሉ፡፡ በተለይም “ሱድፋ”፣ “ቃሲ ቀልበክ”፣ “አልሀወል አወል”፣ “አነ ማ በንሳክ”፣  “አንናስ አል-ጊያፋ”፣ “ሐረምተ አድ-ዱንያ”፣ “ያ ኑረል ዐይን”፣ “ሸተል ዘማ”፣ “አል-ሙርሳል” የመሳሰሉት ከምርጥ የወርዲ ዜማዎች መካከል ይሰለፋሉ፡፡ እኔ በግሌ በጣም ከምወዳቸው የሱዳን ዜማዎች መካከልም አንዱ የሙሐመድ ወርዲ “አዚብኒ ወተፈነን” ነው፡፡

ዐዚብኒ ወዚድ ዐዘባ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚይክ
ዜይመን ሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚክ፡፡
አዚብኒ ወተፈነን ፊ አልዋን ዐዛቢ
ማ ቲምሳሕ ዲሙዒ ማ ቲርሐም ሸባቢ፡፡
ኸሊኒ ፊሹጁኒ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ
ዜይ መንሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ፡፡

ወርዲ በዚህ ዘፈን ለወዳጁ “ልብሽ ጨክኖብኝ ፍቅርሽ አቃጥሎ እየጨረሰኝ ነው፤ መጥተሸ እምባዬን የማታብሺልኝ ልበ-ደረቅ ነሽ” የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው የፈለገው፡፡ ወርዲ ይህንን ዜማ የዛሬ 20 ዓመት ገደማ በአዲስ አበባ ስታዲየም እጅግ ባማረ ሁኔታ የተጫወተው ሲሆን የሀገራችን አድናቂዎችም በጋለ ስሜት ተቀብለውታል ( ቪዲዮውን በሚከተለው ሊንክ ላይ ተመልከቱት፡፡  https://www.youtube.com/watch?v=WkegFEEwjjM&feature=related
                                                                          *****
ታዲያ የወርዲ ፍቅረኛ በ“አዚብኒ-ወተፈነን” ውስጥ እንደተገለጸው በጭካኔዋ አልዘለቀችም፡፡ ወርዲ በጉንጮቹ ላይ የሚያፈሰው እምባ አሳዝኖአት ከፍቅር በረከቱ ልታቀምሰው መጥታለታለች፡፡ ወርዲም ፍቅረኛውን ያገኘበትን ቀን “የቀኖች ሁሉ ረጢብ፣ እጅግ በጣም ገዳም፣ የምኞቴን ያሳካሁበት ቀን መጥቶልኛል” በማለት ገልጾታል፡፡
“ሱድፋ” የሚለውን የሙሐመድ ወርዲን ዘፈን እናውቀው የለ?.. በዚያ ዘፈን ውስጥ ወርዲ ለወዳጁ ያለውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን ከናፈቁት ወዳጅ ጋር መገናኘቱ የሚሰጠውን ደስታ በተዋቡ ቃላት ገልጾታል፡፡ እኔ በበኩሌ እጅግ በጣም የምወደው የወርዲ ዘፈን ይኸው ሱድፋ ነው፡፡ እነሆ የሱድፋን ሙሉ ግጥም ተጋበዙልኝ፡

ሱድፋ… ሱድፋ
ሱድፈ ወ አጅመል ሱድፈነ የውም ላቄታ
አስዓድ የውም የውሚል ሐዬታ
ኑረ ዐይነያ አያም ሓቤታ

ይህ አዝማቹ ነው እንግዲህ፡፡ “ሱድፋ” ማለት አስገራሚ ዕድል ማለት ነው (በእንግሊዝኛ fortunate የሚለው ቃል ይቀርበዋል)፡፡ ተከታዮቹ ግጥሞች የሚከተሉት ናቸው፡፡

አን-ነዘራት በሪዓ ገመም ዘውፍጀል ኸጀል
አልበሰማት ተበዊ ዘይ ኑረል ዐመል
ወጅሂክ ቤን መዛህሪክ ዘይ በድሪ-ክ-ከመል
ወሽሻመክ ኺዴድክ ዘይ ጠዕመል ኹበል
ተስኪር ገልቢ
ወተሽዒል ሑቢ
ኢሽሀክ ረብቢ
አነ በህ ዋ
-----
ማ ቃዲር አጉል ሊክ አን ሑብቢል ከቢር
ወስፉ ዓለይያ ቃሲ መዓዪሽ ፊ-ድ-ደሚር
ቀድረል ከውን ተኩልሉሁ አክበር ቤ ከቲር
ማሊክኒ ሙሐዪይርኒ ሹፍከል ቢል ኣሲር
አስአሊ ቀልቢ
ኢኪኒ ዪቅደር
ኢሽራሕ ሑቢ
አነ ሙሕታር
------
ሱድፈ ዑዩኑ ሻፈክ ሌይሊ ባቂ ይነዊር
ያ አይያም ረቢዒ ዑምሪ መዓኪ አዝሐር
ፊሃ አጥ-ጤይር ይገኒ ሚን አል-ሓኒ ዪዝከር
ቀልቢ ፈራሸ ሐውሊ ወኢንቲ ሸባቢከ አኽደር
ያ መበሒብቢ
ባዕቡድ ሑብቢክ
አለሻን ሑብቢክ
ሩሒ ፈዳክ
*****
ለመሆኑ መሐመድ ወርዲ ማን ነው?

  ሙሉ ስሙ ሙሐመድ ዑስማን ሳሊሕ ወርዲ ነው፡፡ እርሱ ግን “ሙሐመድ ወርዲ” ወይንም በአጭሩ በቤተሰቡ ስም “ወርዲ” ተብሎ ነው የሚታወቀው፡፡ የተወለደው እ.ኤ.አ. በ1932 “ዋዲ ሀልፋ” በተሰኘው ሰሜናዊው የሱዳን ክፍለ ሀገር፣ “ሱወርዳ” በተባለች ትንሽዬ የገጠር መንደር ውስጥ ነው፡፡ እናቱ የኑቢያ ተወላጅ ስትሆን አባቱ ዐረብ ነው፡፡

ወርዲ የሙት ልጅ ነው፡፡ ሁለቱንም ወላጆቹን በልጅነቱ ነው ያጣው፡፡ በመሆኑም በዘመዶቹ ጥበቃ ስር ሆኖ ነው ያደገው፡፡ ትምህርቱን በዋዲ ሀልፋ እና በካርቱም ተከታትሏል፡፡ የተወለደበትን ሀገር እስከ 1956 በመምህርነት ሙያ ካገለገለ በኋላ በወቅቱ ይሞካክራቸው የነበሩት ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ጣቢያ ተቀርጸው በመተላለፋቸው በህዝብ ልብ ውስጥ ገባ፡፡ ያገኘው የሞራል ድጋፍ ማነሳሻ ስለሆነው መምህርነቱን ትቶ የአርቲስትነቱን ጎራ ተቀላቀለ፡፡ ከዚያም ሱዳኖች ከሚያፈቅሯቸው ቁንጮ ዘፋኞቻቸው አንዱ ለመሆን በቃ፡፡
 
    ወርዲ በህይወቱ የተረጋጋ ኑሮ አልኖረም፡፡ በሱዳን የተለዋወጡት መንግሥታት በተቃዋሚነት እየፈረጁት አንገላተውታል፡፡ በመሆኑም ለሀያ ዓመታት ያህል በካይሮና በለንደን ነው የኖረው፡፡ በ2002 ግን ወደ ሀገሩ በክብር ተመልሷል፡፡ ወርዲ በሙዚቃው ዕድገት ላደረገው አስተዋጽኦ ከካርቱም ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸልሟል፡፡ ከልዩ ልዩ የአውሮጳ፣ አፍሪቃና እስያ ሀገራትም ሽልማቶችን ተቀብሏል፡፡
 መሐመድ ወርዲ በመጨረሻዎቹ ዓመታት በደረሰበት የጤና መታወክ ሁለት ኩላሊቶቹ ከጥቅም ውጪ ሆነው ነበር፡፡ ይኸው የኩላሊት ህመም ፋታ ነስቶት በየካቲት ወር 2012 ከዚህች ዓለም አሰናብቶታል፡፡
*****
ከመግቢያዬ እንደገለጽኩት የሀገራችን የሙዚቃ አፍቃሪዎች በጣም የሚወዱት የመሐመድ ወርዲ ዘፈን “ሰበርታ” ነው፡፡ እኔም “ሱድፋ”ን ከሁሉም እንደማስበልጥ ገልጫለሁ፡፡ በሱዳኖች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነው የመሐመድ ወርዲ ዜማ ግን “ገመር ቦባ” ነው፡፡ ሱዳኖች እ.ኤ.አ. በ2000 ባደረጉት ምርጫ “አል-ገመር ቦባ” የተሰኘው ዘፈን የክፍለ ዘመኑ ምርጥ “ነጠላ ዜማ” ተብሎ ተመርጧል፡፡እኔም ገመር ቦባን በድምጽ (ኦድዮ) ልጋብዛችሁና ላብቃ፡፡

ቦባ ዐሌክ ተጊል… ቦባ ዐሌክ ተጊል
አል-ገመር ቦባ ዐሌይክ ተጊል፡፡
አስ-ሰጊሩን አል-ማ-ከቢር
አር-ሪጌበት-ጊዛዛት አሲር
አስኑን በርራጊን የሺል
አል-ዑዩን መሥለል ፈናጂል
ቢንተ-ሱዳን አሲል
ያ ገመር ቦባ ዐሌክ ተጊል፡፡

(ገመር ቦባን በዚህ ሊንክ ላይ ይስሙት https://archive.org/details/MohammedWardi-AlQamarBoeba )
------
አፈንዲ ሙተቂ
መጀመሪያ ታሕሳስ 6/2006 ተጻፈ፡፡
እንደገና ተሻሽሎ መስከረም 9/2007 ተጻፈ፡፡
---
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.
 You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click this link to go to his facebook page.



No comments:

Post a Comment