Thursday, September 12, 2013

==የአሕመዶ ቦቴ ጨዋታዎች==


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
እንደ መግቢያ….
አንዳንዴ ትገርሙኛላችሁ! በሁሉም እንቶ ፈንቶ እየሳቃችሁ እነ “እገሌ” እንዲጀነኑብን አደረጋችኋቸው! ምን አለ ረጋ ብትሉ?…ቴቪ ላይ የታየ ሁሉ ኮሜዲያን ነው ያላችሁ ማን ነው?
  እርግጥ ክበበው ገዳ ነፍስ ነው፡፡ ያ የሞተው ተስፋዬ ካሳም ነፍስ ነው፡፡ እንግዳዘርና አበበ በለውም ነፍስ ነበሩ፡፡ እንዲሁም ሟቾቹ የብሄራዊ ቴአትር ተዋኒያን ዓለሙ ገብረአብና ሲራክ ታደሰ ሲተውኑ በሳቅ ያንፈርፍራሉ፡፡ ከኦሮምኛ አክተሮች አድማሱ ብርሃኑ (ብዙ ጊዜ ሽማግሌ ሆኖ የሚሰራው) ወደር የለውም፡፡ ሌላው ግን “ኮርጆ” ነው፡፡ አስቃለሁ ብሎ ጨጓራ ያበግናል፡፡

ኮሚክ ከፈለጋችሁስ እነ “ቦቴ” አሉላችሁ!…. ጥርስ የማያስከድኑ የህይወት ቅመሞች…. ለጨዋታ የተፈጠሩ የጨዋታ አባቶች፡፡ እስቲ ከቦቴ ጨዋታዎች ትንሽ ልጨልፍላችሁ፡፡
---
  እኔ፣ “ቦቴ”፣ ሙሐመድ ነጃሽ እና ኢስሐቅ ዓሊ ባልንጀራሞች ነን፡፡ በእድሜ ብንበላለጥም የእህል ውሃ ነገር ጓደኛሞች አድርጎናል (ደግሞም አባቶቻችን ጓደኛሞች በመሆናቸው ፍቅራቸውን ወደኛ አስተላልፈዋል)፡፡ ታዲያ አራታችንም በአንዱ የረመዳን ምሽት ቦሌ በሚገኘው የመሐመድ ነጃሽ ቤት ተሰባስበናል፡፡ ከትንሽ ጊዜ በኋላም አንድ “ጥቁር እንግዳ” የኛን ጀመዓ ተቀላቀለ፡፡ ከመሐመድ ነጃሽ በስተቀር ሌሎቻችን አናውቀውም፡፡
   ሰውዬው እኛ የማንፈልገውን የፖለቲካ ወሬ መቅደድ ጀመረ፡፡ ለጥቂት ጊዜ በትዕግስት አደመጥነው፡፡ እያደርን ግን “ሰውየው ተልኮብን ይሆን?” እያልን ተጠራጠርን፡፡ ሆኖም በድፍረት የሚናገረው ጠፋ፡፡ ከቆይታ በኋላ ግን “ቦቴ” አንድ ብልሃት ታየው፡፡ እናም እንዲህ አለ፡፡
   “መሐመድ ነጃሽ፤ እንግዳህን አደብ አስይዘው፡፡ እኔ ቤት ውስጥ እንዲህ አይነት ወሬ እንዲያወራ አልፈቅድለትም፡፡ እምቢ ካለ ግን ያንተ ቤት ሄዳችሁ የፈለጋችሁትን ቅደዱ፡፡”
  በዚህም ቤቱ የቦቴ ሆነ፡፡ እኛም ልክ እንደ ቦቴ ቤት ማስመሰሉን ተያያዝነው፡፡ በተለይ ቦቴ “ይህንን ቤት ስሰራ እኮ በራሴ አንጡራ ሀብት ነው፡፡ የማንም ስሙኒ አልተቀላቀበትም፡፡ ለልጆቼ የማወርሰው ቅርስ ይህ ነው…ወዘተ..” በሚሉ ቃላቶች “አክት” እያደረገ ያስፈግገን ገባ፡፡ ሙሐመድ ነጃሽ ግን ድራማውን እያበላሸ አስቸገረን፡፡ ስልክ ሲደወል “እባክህ ያንን ስልክ አንሳው!” በማለት ትእዛዝ ይሰጣል፡፡ የቤት ሰራተኛውንም “እገሌ! ሻይ አፍይልን” ይላታል፡፡ በአይን ብንጠቅሰው አልገባው አለ፡፡ ይባስ ብሎ ደግሞ ግድግዳ ላይ የሚሄድ በረሮ በመጽሐፍ መትቶ ሊገድል ተነሳ፡፡ በዚህን ጊዜ ቦቴ አላስችልህ አለው፡፡ እናም በስጨት ብሎ እንዲህ አለ፡፡
   “አንተ መሐመድ! የኔን በረሮ ማን ግደልብኝ አለህ? ያንተ ቤት ሂድና የራስህን በረሮ ግደል እንጂ የኔን አትንካብኝ”፡፡
    በሳቅ የታፈንነው ሶስታችንም ቤቱን አበራየነው፡፡
 -----
አንዱ “ሀጂ ቅደደው” ቦቴ ባለበት ቦታ ቀደዳ ጀመረ፡፡ እንደፈለገው ቀደዳውን ለቀቀው፡፡ ቦቴ ዝም ብሎ ሰማው፡፡ በኋላ ሐጂው “ዱባይ ሄጂ፣ ባህሩን ዋኝቼ፣ በወደቡ ተጫውቼ ምናምን” ሲል ቦቴ “አኸ! አል-ፈላህ ሬስቶራንት ፊት ለፊት ያየሁት ለካስ አንተን ነው?” አለው፡፡ ይህንን የሰማው በቤቱ የነበረው ጀመዓ በሳቅ ሀገሩን አደበላለቀው፡፡
-----
የቦቴ ወንድም በአዲስ አበባ አንድ ቤት ሰርቷል፡፡ ነገር ግን “ቤቱ ህገወጥ ግንባታ ነው” ተብሎ በክፍለ ከተማው ሀላፊዎች ተከሰሰ፡፡ ቦቴ የክሱ ቦታ ወንድሙን ወክሎ ሄደ፡፡ እናም የግንባታ ሃላፊዎች “ይፈርሳል” አሉት፡፡
  “ለምንድነው የሚፈርሰው?”
“ጨረቃ ቤት ስለሆነ ነው”
 “አንተ ነህ ጨረቃ ያደረግከው? ኮከብ ነው የወንድሜ ቤት!”
-----
 ይህኛው ከጥቂት ሳምንታት በፊት የተከሰተ ነው፡፡ ከቦቴ ጋር ተገናኘንና ጨዋታ ጀመርን፡፡ በተለይ እኔና ጓደኛዬ ዘንድሮ የሞተውን አንድ በአራጣ ብድር ሀገር ያስመረረ ቱባ ነጋዴ ሀዘንን በማስመልከት በለከፋ አጣደፍነው፡፡ “ቦቴ ለቅሶ ደርሷል ሲሉ ሰምተናል፡፡ እውነት ነው? እውነት ከሆነ አንተም እንደርሱ የህዝብ ጠላት ነህ” አልነው፡፡
  “እውነት ነው፤ ሄጃለሁ” አለ ቦቴ፡፡
   “ለምን ሄድክ?” በማለት ወጠርነው፡፡ በዚህን ጊዜ ነው ቦቴ እጅግ አስደናቂና አስቂኝ የሆነ ታሪክ ያጫወተን፡፡ እንዲህ ልጻፍላችሁ፡፡
   -----
ድሮ ነበር ፤ በ1966 መጨረሻ ገደማ፡፡ ዒስማኢል አህመዩ፣ ሙሐመድ በከር (የቦቴ አባት)፣ ሙተቂ ሼክ ሙሐመድ (የአፈንዲ አባት) እና ነጃሽ ዒስማኢል (የመሐመድ ነጃሽ አባት) በፖለቲካ ተከሰው በሀረር ከተማ በአንድ ክፍል ታስረዋል፡፡ ከሁለት ቀናት በኋላ  እንደነርሱ በፖለቲካ የተጠረጠረ መገርሳ የሚባል ሰው ተጨመረባቸው፡፡
መገርሳ ለአራቱ ታሳሪዎች ራሱን አስተዋወቀ፡፡ እናም “የየት ሀገር ሰዎች ናችሁ?” አላቸው
 “ገለምሶ”
  “ገለምሶ ከተማ?”
  “አዎን”
  “ታደሰ የሚባለው የፖሊስ አዛዥ አለ?”
  በዚህን ጊዜ ሶስቱ ታሳሪዎች ለመናገር ፈሩ፡፡ ዒስማኢል አህመዩ ግን የፈለገው ይምጣ ብሎ ለመናገር ቆረጠ፡፡
  “ሞቷል ወዳጄ!”
   “እውነት ሞቷል?”
    “አዎን ሞቷል”
   “መቼ ነው የሞተው?”
   “አሁን በቅርቡ ነው የሞተው”

መገርሳ እየየውን አቀለጠው፡፡ “ኡኡኡ” እያለ ያለቃቅስ ገባ፡፡ አራቱ ታሳሪዎች ተረበሹ፡፡ የሚያደርጉት ጠፋቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ሙሐመድ በከር ዒስማኢልን ተቆጣው፡፡ “አንተን መርዶ ነጋሪ ማን አደረገህ? ዘመዱ ከሆነስ ብለህ አትጠረጥርም ነበር?… ይኸው አስለቀስከው.. እንግዲህ እንዳስለቀስከው አንተው ራስህ አፉን አስይዘው” አለው፡፡

መገርሳ ለቅሶውን ቀጠለበት፡፡ “ታዴ ኮ! ወይ ታዴ ኮ” እያለ አለቃቀሰ፡፡ ዒስማኢል ተጨነቀ፡፡ ከመቅጽበት ግን የመገርሳ ቅላጼና የሚወረውራቸው ቃላት በተቃራኒው መሄድ ጀመሩ፡፡ እናም በኦሮምኛ እንዲህ አለ፡፡
  “Yaa Waaqa ofumaaf uumtee ofumam ajjeesta! Maalo maaloo maaloo! Ajeechaa nuti yoo sigargaarree maaluma qaba. Kan akka Taaddasaa kana nuutuu ni nigeenyaafi bari. Yaa Waaqa Maaloo Maloo…..”
ትርጉሙ እንዲህ ይሆናል
    “አዬ ጌታዬ! አንተው ራስህ ፈጥረህ አንተው ራስህ ትገድላለህ! በመግደሉ ላይ እኛ ብናግዝህ ምን አለበት? ለታደሰ ዓይነቱ እኛ ራሳችን እኮ እንበቃዋለን እኮ፡፡ አይ ፈጣሪ! ታደሰን ስትገድለው ብትጠራኝ ምን አለበት?”
  
 መገርሳ እንዲያ እያለ ለቅሶውን ቀጠለበት፡፡ አራቱ ሰዎች ይህንን ሲሰሙ በጣም ተገረሙና ተያዩ፡፡ እናም ሙሐመድ በከር ለዒስማኢል አህመዩ እንዲህ አለው፡፡
  “እንኳንም ነገርከው! ይህንን የመሰለ ወሬ ልትደብቀው ነበር?.. እንኳንም ነገርከው! አበጀህ! እንኳን ነገርከው!…”
ለካስ ታደሰ አገር ያቃጠለ የፖሊስ መቶ አለቃ ነበር? መገርሳም ያለጥፋቱ ከእስር ቤት ወደ እስር ቤት ሲንከራተት የነበረው መቶ አለቃ ታደሰ በከፈተበት ሀሰተኛ ክስ ሳቢያ ነው፡፡

ቦቴ ይህንን ታሪክ ካጫወተን በኋላ እንዲህ አለ፡፡
  “ለቅሶ የሚሄደው ሁሉ ለሟቹ የሚያለቅስ መሰላችሁ?… እንደ መገርሳ የምስጋና ለቅሶ የሚያለቅስም ሞልቷል እኮ! ለናንተም ለቅሶአችሁን የደስታ ያድርግላችሁ”
-----
እንደ ማሳረጊያ…

  “ቦቴ” በትክክለኛ ስሙ አህመድ ሙሐመድ በከር ነው፡፡ እርሱ ባለበት ቦታ ጨዋታ አይጠፋም፡፡ ሲቀመጥም ሆነ ሲሄድ ሰውን ማሳቅ ይችልበታል፡፡ እናንተ ተጠባችሁ የፈጠራችሁትን ጆክ ለርሱ ብትሰጡት የሳቅ ጎርፍ እንዲያፈልቅ አድርጎት ይቀምመዋል፡፡ ድሮ በህጻንነታችን የሰማናቸው ተረቶች በርሱ አንደበት በመነገራቸው ብቻ ሰውን በሳቅ ሲያፈነዱት አይቼ  “ይህስ የፈጣሪ ጸጋ ነው” እያልኩ ተገርሜአለሁ፡፡

ታዲያ አንዳንዴ እርሱን ራሱ በቅጽል ስሙ መጥራት ሳቅ የሚፈጥር ትዕይንት ሆኖ ይገኛል፡፡ በተለይ ብዙ ሽማግሌዎች “ቦቴ” እላለሁ ይሉና “ቮልቮ” ይሉታል፡፡ አንዳንዶቹ “ጎማ” ሲሉት ያጋጥማሉ፡፡ አንዳንዶቹ ጭራሽ “ቱርቦ” ይሉታል፡፡
  በርግጥም “ቦቴ” ሁሉንም ነው፡፡ የማያልቅበት የሳቅ “ቦቴ”፣ የሳቅ “ቮልቮ”፣ የሳቅ “ጎማ”፣ የሳቅ “ቱርቦ” ወዘተ…ጂንኒ ጀቡቲ….ምናምን…
------ 
አፈንዲ ሙተቂ
መስከረም 2/2006
     

Tuesday, September 10, 2013

በምስራቅ ዕዝ ሙዚቀኞች ላይ የደረሰው እልቂት (ታህሳስ 1980)


ከአፈንዲ ሙተቂ
-------
እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1980 ገደማ በሀረር ከተማ ከአምስት ያላነሱ ኦርኬስትራዎች ነበሩ፡፡ ከነርሱም መካከል ሶስቱ ከሀረርጌ ክፍለ ሀገር አልፎ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ስም ነበራቸው፡፡ እነርሱም በተለምዶ “የምስራቅ እዝ ኪነት” የምንለውና በዘመኑ አጠራር ግን “የአንደኛው አብዮታዊ ሰራዊት ኦርኬስትራ” የሚባለው የኪነት ቡድን (እነ ንግሥት አበበ እና ኑሪያ ዩሱፍን የመሳሰሉ ከዋክብትን ያቀፈ)፣  “የምስራቅ በረኛ አብዮታዊ ፖሊስ የኪነት ጓድ” (እነ ኤልሳቤት ተሾመ፣ ፍቅሩ ቶሌራ፣ ሙሳ ቱርኪ፣ ፋንታሁን ፈረንጅ እና ግርማ ንጋቱ የነበሩበት) እና “ጎሐ ምስራቅ የኪነት ቡድን” (እነ ሰለሞን አካሉ፣ ሙሉጌታ አባተ፣ መፍቱሐ አባስ እና ሙስጠፋ አብዲ የመሳሰሉትን ያቀፈ) ናቸው፡፡

   ከሶስቱ ቡድኖች አንዱ የሆነው የምስራቅ ዕዝ ኪነት ቡድን ከሻዕቢያ ጋር ለሚፋለመው ሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ዝግጅቱን ለማቅረብ ወደ ሰሜን ተጓዘ፡፡ ግን በሰላም አልተመለሰም፡፡ ንግሥት አበበን ጨምሮ በርካታ አባላቱን በሞት አጣ፡፡ በቡድኑ ላይ የደረሰው እልቂት በኢትዮጵያ ሬድዮ ሲነገር በርካቶችን በእንባ አራጨ፡፡ በተለይ ከዘመኑ አፍለኛ ዘፋኞች አንዷ የነበረችው የንግሥት አበበ ሞት የብዙዎችን ልቦና የሰበረ ነበር፡፡ ያ አሳዛኝ ትራጄዲ እንዴት ተከሰተ? የቡድኑ አስተዋዋቂ የነበረውና ከሞት የተረፈው  ግርማ ከበደ (በቅጽል ስሙ “ግርማ ዲናሬ”) ሁኔታውን ለኢትኦጵ መጽሔት እንደሚከተለው አብራርቶ ነበር፡፡
-----
ኢትኦጵ፡- አንድ ጊዜ የምስራቅ እዝ ኪነት ቡድን ወደ ሰሜን አቅንቶ በሻዕቢያ ደፈጣ ተዋጊዎች እንደተመታ ሰምቻለሁ፡፡ በዚያን ጊዜ አንተ ነበርክ?

ግርማ፡ አዎን እኔም ነበርኩ፡፡ ደመናው ከልሎኝ ከተረፉት ጥቂቶች አንዱ እኔ ነኝ፡፡ ጊዜው 1980 ዓ.ም. ታሕሳስ 21 ቀን ነው፡፡ ዝግጅታችንን ግንባር ላለው ሰራዊት አቅርበን ወደ አስመራ ስንመለስ ጠላት አድፍጦ ይጠብቀን ነበርና 17 አርቲስቶች በዚያ ውጊያ ህይወታቸው ጠፋ፡፡ ካጀቡን ወታደሮችም 20 ያህሉ በውጊያው ተሰውተዋል፡፡ 14 አርቲስቶች ደግሞ ቆስለዋል፡፡ አራት ሰዎች ብቻ ምንም ጉዳት አልደረሰብንም፡፡

ኢትኦጵ፡- የምስራቅ እዝ የተዋጣላት ድምጻዊት ንግሥት አበበ በዚህ ውጊያ ላይ ነበር ህይወቷ ያለፈው?

ግርማ፡- አዎን (በሐዘን ስሜት አቀረቀረ)::

ኢትኦጵ፡- እስቲ ያንን ሁኔታ እንዴት ትገልጸዋለህ?

ግርማ፡- ወደ አስመራ ስንመለስ ትልቅ ስጋት ነበረብን፡፡ ሻለቃ ታደሰ የተባሉ አዛዣችንም ጥንቃቄ እንድናደርግ ደጋግመው አሳስበውናል፡፡ እሳቸውም እዚያው ነው የተሰውት፡፡ ሻለቃው እንደሰጉት እኛም አንዳች አደጋ ሊገጥመን ይችላል ብለን ፈርተን ነበርና አልቀረልንም፡፡ አደጋው መጣ፡፡ ንግሥት በፈንጂ ደረቷ ስር ተመትታ ነው የወደቀችው፡፡ ብዙ ቦንብ ነበረ የሚወረውሩብን፡፡ አጃቢዎቻችን ለመከላከል ብዙ ሞከሩ፤ ግን አልሆነም፤ አለቁ፡፡ እነርሱን መጨረሳቸውን ሲረዱ አርቲስቶች ወዳሉበት መኪና ተኩስ ከፈቱ፡፡ እየተላቀስን በጥይት ቀጠቀጡን፡፡ “ሁሉንም ጨርሰናል” ብለው ካደፈጡበት ወጡ፡፡ የተረፈ እንዳለ ፈተሹ፡፡ እኔ አንድ ስርቻ የሞተ መስዬ ተደበቅኩ፡፡ መቼም ፈጣሪዬን እንደዚያ ቀን የተማፀንኩበት ጊዜ አልነበረም፤ ተረፍኩ፡፡

ኢትኦጵ፡- ያንን አደጋ እንጠብቀው ነበር ስትል?

ግርማ፡ ብዙ ጭንቀት ነበረብን፡፡ ለምሳሌ ንግሥት አበበ የሶስት ወር አራስ ነበረች፡፡ ዝግጅታችንን ስናቀርብ “ለጥምቀት ሀረር አንደርስም ወይ? እኔ ልጄን ክርስትና አስነሳለሁ፤ እንደምንም ብለን በዚህ ጊዜ መጨረስ አለብን” ትል ነበር፡፡ አዛዣችንም ጉዞ ስንጀምር “እኔም ለልጆቼ፣ እናንተም ለቤተሰቦቻችሁ ስትሉ በጉዞ ላይ ጥንቃቄ አድርጉ” ይሉን ነበር፡፡ ይህንን ስንሰማ ሁላችንም ስጋታችን አየለ፡፡ እንደፈራነው ያን ዓይነት እልቂት ጠበቀን፡፡ ሀዘኑ እስከ ህይወቴ ፍጻሜ የሚጠፋ አይመስለኝም፡፡ በጠቅላላው የምስራቅ እዝ ኦርኬስትራ ነው የተመታው፡፡ የት ይደርሳሉ የሚባሉ አርቲስቶች ናቸው በዚያ ጨካኝ ትዕይንት ያለቁት፡፡
-------
(ኢትኦጵ መጽሔት፣ ቅጽ 4፣ ቁጥር 7፣ ሰኔ 1994፣ ገጽ 40)
እንዲህ ነው እንግዲህ አደጋው የተፈጠረው! ንግስትን ጨምሮ በርካቶች ያለቁት በዚያ አደጋ ነው፡፡ ታዲያ ሻዕቢያ በተመሳሳይ ወቅት ናደው የሚባለውን እዝ አጥቅቶ እጅግ ወሳኝ የሆነ ድል መቀዳጀቱም ይታወሳል፡፡

ከዚያ አደጋ ቆስለው ከተረፉት አርቲስቶች አንዷ የነበረችው የኦሮምኛ ዘፋኟ ኑሪያ ዩሱፍ በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይታለች (ኑሪያ በአደጋው አንድ እግሯን አጥታለች)፡፡ ግርማ ዲናሬ በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባ ነው የሚኖረው፡፡ ፒያሳን የሚያዘወትሩ ሰዎች ሊያገኙት ይችላሉ፡፡

  በነገራችን ላይ አንዳንዶች በስህተት “በአደጋው ያለቁት የምስራቅ በረኛ ፖሊስ የኪነት ጓድ አባላት ናቸው” እያሉ ሲናገሩ ሰምቻለሁ፡፡ ትክክለኛው ታሪክ ግን በግርማ ዲናሬ አንደበት ከላይ የተገለጸው ነው፡፡ ሰላም!
------
You can get also more articles on this page https://www.facebook.com/afendimutekiharar

Saturday, September 7, 2013

==ከትምህርት ቤት መዝሙሮቻችን በጥቂቱ (ለትዝታ)==


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን ያጠናቀቅኩት በቁጥር ሁለት ት/ቤት ነው፡፡ የትምህርት ቤታችን ዋነኛ ህንጻ በስዕሉ ላይ የምትመለከቱት ነው፡፡ ይህንን ህንጻ የኢጣሊያ ወራሪዎች ናቸው የሰሩት፡፡ በከተማችን ውስጥ ለረጅም ዘመናት በቁመቱ ከርሱ ጋር የሚስተካከል ሰው ሰራሽ ግንባታ አልነበረም፡፡ በዚህም የተነሳ በኦሮምኛ ስሙ “Mana Dheeraa” (ረጅሙ ህንጻ) በማለት ነው የምንጠራው፡፡

  የትምህርት ቤቱ የኦፊሴል ስም ነው “ገለምሶ ቁጥር ሁለት አንደኛ ደረጃ ት/ቤት” ነው፡፡ በተለምዶ ህንጻውን የምንጠራበት “ቁጥር ሁለት” የተሰኘው የአማርኛ ስሙ የተገኘው ከዚሁ ነው፡፡

 “ቁጥር ሁለት” (“መነ ዴራ”) በኢጣሊያ ወራሪዎች ዘመን የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ነበር፡፡ ጣሊያኖቹ ሲወጡ የወረዳ ጽ/ቤት ሆኖ ማገልገል ጀመረ፡፡ ከዚያም ወደ አዳሪ ት/ቤት ተቀየረ፡፡ በ1962 ገለምሶ የአውራጃ ዋና ከተማ ስትሆን ደግሞ ህንጻው ወደ እስር ቤት ተቀየረ፡፡ በርሱ ምትክም ሌላ ትምህርት ቤት በከተማው የምስራቁ ክፍል ተሰራ፡፡

  “ቁጥር ሁለት” እስከ ዘመነ ቀይ ሽብር ድረስ እንደ እስር ቤት ካገለገለ በኋላ በ1972 ገደማ እንደገና ወደ ትምህርት ቤት ተቀየረ፡፡ ሁለቱን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በስም ለመለየት በሚልም “ቁጥር ሁለት” የሚለው ስያሜ ተሰጠው፡፡ እያደገ የመጣውን የተማሪ ብዛት ለማስተናገድ እንዲችልም በርካታ ክፍሎች በግቢው ውስጥ ተሰሩለት፡፡ በማስከተልም ሌሎች በርካታ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በከተማው ውስጥ ተከፈቱ፡፡  

ስለ ቁጥር ሁለት ታሪክ ይህንን ያህል ካልኳችሁ ይበቃል፡፡ አሁን ደግሞ የዚህ ትምህርት ቤት ተማሪ ሳለሁ እንዘምራቸው ከነበሩት መዝሙሮች ጥቂቶቹን ላካፍላችሁ፡፡
 -----
ዝናብ ሲዘንብ በዝምታ አናሳልፍም፤ በከፍተኛ ድምጽ እንዘምራለን እንጂ! መዝሙሩን እኛ ብንረሳ እንኳ አስተማሪዎቻችን “ዘምሩ” ይሉናል፡፡ በዚህ በኩል እስከ አሁን ድረስ ትዝ የሚሉኝ የሚከተሉት ናቸው፡፡
  
ሀ/. ዋንታ ነሜራ
ዋንታ ነሜራ ዋሂራ ዋንታ ነሜራ
ዋንታ ነሜራ ዋሂራ ዋንታ ነሜራ
ዝናቡ ዘነበ ደጁ ረሰረሰ
አንዱን ሳላጠና ፈተና ደረሰ
ዋንታ ነሜራ ዋሂራ ዋንታ ነሜራ

“ዋንታ ነሜራ” የኩባ ዘፈን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ አዝማቹ ብቻ ተወስዶ ወደ አማርኛ መዝሙር የተቀየረበትን መነሾ ግን አላውቅም፡፡
--
ለ/. “ዝናቡ ዘነበ”
ዝናቡ ዘነበ አትምጪ ስልሽ
ይኸው እንደፈራሁት ጎርፍ ወሰደሽ፡፡
በሀምሳ በሰላሳ ሲገዛ ፈረስ
በመቶ ብር ገዛሁ የሰው አጋሰስ፡፡

በዚህ ግጥም ውስጥ የወንድ ትምክህት አለ አይደል? ያኔ ግን ህጻናት ነበርና ምንነቱ አይታወቅንም ነበር፡፡ እንዲያውም አንዳንድ የአማርኛ ቃላትን ትርጉም እንኳ በፍጹም አናውቅም ነበር፡፡ ለምሳሌ “አጋሰስ” ምን ማለት እንደሆነ በኋላ ላይ ነው የተረዳሁት፡፡
-----
ብዙ መዝሙሮች የምንዘምረው በሙዚቃ ክፍለ ጊዜ ነበር፡፡ ከነዚያ መዝሙሮች መካከል ከየዘርፉ አንድ ሁለቱን ልጻፍላችሁ፡፡

  ሀ/. “አንቅልፍ ጨርሰን” (ስለግል ንጽህና)

እንቅልፍ ጨርሰን ጠዋት ስንነሳ
የምንሰራውን ልጆች እንዳንረሳ
ልብሳችንን ለብሰን ሽንት ቤት ደርሰን
ሳሙናና ውሃ ለፊት አቅርበን
እጅና ፊታችን ማጠብ አለብን፡፡
የጸጉርም ጽዳት መጠበቅ አለበት
በደንብ አበጥሮ ከተገኘም ቅባት
ቀብቶ መሄድ ነው ወደ ትምህርት ቤት፡፡

ለ/. ዝንቦች (ስለንጽህና)

ዝንቦች መጥፎ ናቸው
  “እሽ! እሽ!” ይበሏቸው፡፡
  ዐይንን ያጠፋሉ
  በሽታን ያመጣሉ
  እናባርር በሙሉ!!
   እናባርር በሙሉ፡፡
  
 ሐ/. አብዮታዊ ሰራዊት (ስለ አብዮታዊው ጦር)

አብዮታችን በጣም በጣም ደመቀ
የድል ጮራ ዳር እስከ ዳር ፈነጠቀ፡፡
በምስራቅ በደቡብ በመሀል አልፎ
ጠላቱን ወራሪ ማረፊያ አሳጥቶ
እንደ ካራማራ እን ጭናክሰን
ድል ተቀዳጅቶ ገስግሶ በሰሜን፡፡
ተዋግቶ ተዋግቶ
አጥንቱን ከስክሶ ደሙን አፍስሶ
አብዮታዊ ሰራዊት ድል አድርጎ ሲገባ
በሉለት ጉሮ ወሸባ! በሉለት ጉሮ ወሸባ!!

መ/. ውሸታሙ እረኛ (ስነ-ምግባር)

ውሸታሙ እረኛ
ሲያልፍ መንገደኛ
ቀበሮ መጣብኝ
በጎቼን በላብኝ፡፡
እያለ ዘወትር
ሲቀልድ ሲያስቸግር
በዚህ አድራጎቱ
ደግሞም በውሸቱ፡፡
አንድ ቀን ቀበሮ
መጣና በድንገት
በጎቹን በላበት፡፡
ውሸታሙ እረኛ
ዘወትር ልማደኛ
ኡኡ እያለ መጣ
የሚረዳውን አጣ፡፡
-----
በሙዚቃ ክፍለጊዜአችን በርካታ “ትርኪምርኪ” መዝሙሮችንም እንዘምራለን፡፡ እስቲ ሁለት “ትርኪምርኪ” መዝሙሮችን ልጋብዛችሁ፡፡

ሀ/ ጋሼ ደያስ
 
አራቱንም ጣቴ ጋሼ ደያስ
  ቢላዋ ቆርጦኛል ጋሼ ደያስ
  አንዱ ብቻ ቀርቶኝ ጋሼ ደያስ
  ያንገበግበኛል ጋሼ ደያስ

ጋሼ ደያስ ተክሌ የሁለተኛ ክፍል የአማርኛ መምህራችን ነበር፡፡ በተጨማሪም የፈረቃ መሪ (ዩኒት ሊደር) ነበር፡፡
-
ለ/. ኦኬ ኦኬ

 ኦኬ ኦኬ ኦኬ ስራ
ሰላም ሰላም ወደ አስመራ
አናግረኝና አናግርሃለሁ
በአሜሪካ ሽጉጥ አዳፍንሃለሁ፡፡
 ሁለትና ሁለት ሲደመር አራት
ፍቅርሽ ይጣፍጣል ከማር ከወተት፡፡
  -----
በሙዚቃ ፔሬድ መዝሙር መዘመር ብቻ ሳይሆን እየዘፈኑ ዳንስ መደነስም ነበር፡፡ እያንዳንዱ ተማሪ የሚያውቀውን ዘፈን እየዘፈነ ይደንሳል፡፡ እኛም ክብ ሰርተን ከሳር ላይ ተቀምጠን ዘፈኑን ከደናሹ ተማሪ እየተቀበልነው እናጨበጭባለን፡፡ 
 
ተማሪው የሚዘፍነው ዘፈን ከካሴት ላይ የተገኘ፣ በሬዲዮ የተለቀቀ፣ በቀበሌ ኪነትና የአካባቢ ሚሊሻ የተዘፈነ ወዘተ ሊሆን ይችላል፡፡ ይሁንና አብዛኛው ተማሪ ተመሳሳይ ነገር ስለሚደጋግም ያሰለቻል፡፡ አንዳንድ ተማሪዎች ግን ከየት እንደተገኙ በማይታወቁ አስገራሚ ዘፈኖች እየደነሱ ያዝኑናል፡፡ ከነርሱም መካከል የሁለተኛ ክፍል አለቃችን የነበረው አያሌው አብነት ፈጽሞ የሚረሳ ሰው አይደለም፡፡

   “አያሌው  ለማ ከፈረስ ወድቆ ከንፈሩ ደማ” የሚለውን ዘፈን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት ከአያሌው አብነት ነው፡፡ አያሌው “ያ ማሙሹ መለሜላ” የሚል የኦሮምኛ ዘፈንም ነበረው፡፡ ሲፈልግ ደግሞ “ሎሜ ሎሜ አይሳ!” እያለ ወላይትኛ ሊዘፍን ይሞክራል (“ሎሜ ሎሜ” ከሚለው ሐረግ በስተቀር ሌላው በሙሉ አማርኛ ነው፤ ያኔ ግን እንደ ወላይትኛ ነው የምንቆጥረው)፡፡ አያሌው ሲያሻው እንግሊዝኛ ልዝፈንላችሁ ይልና አስረሽ ምችው ያስነካል፡፡ እስቲ የርሱን እንግሊዝኛ ዘፈን ልጋብዛችሁና ልሰናበት፡፡

      አይ ጌቾ ጌቾ ( እኛ “ፐረስ ፐረስ” እያልን እንቀበለዋን)
     አይ ጌቾ ቤቢ
     ማዘር ከፋዘር
     ወለዱ ሲስተር
    ሄዱ በአየር
    ገቡ ጎንደር
  -----
   በወዳጅነታችን እንሰንብት፡፡
አፈንዲ ሙተቂ
ጳጉሜ 2/2005
  -----

Wednesday, September 4, 2013

==የሀረላ ወግ==



ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
----------

ከታችኛው አዋሽ አካባቢ ተነስታችሁ እስከ ጅጅጋ ድረስ በተዘረጋው መሬት ባሉት መንደሮች ውስጥ ስትጓዙ የጥንታዊ ግንባታ ፍርስራሾች በብዛት ያጋጥሟችኋል። የየመንደሮቹን ነዋሪዎች ስለግንባታዎቹ እንዲነግሯችሁ ብትጠይቋቸው ሀረላ የሚባል ጥንታዊ ነገድ መኖሪያዎች እንደነበሩ ያወጓችኋል። ስለዚያ ጥንታዊ ነገድ የበለጠ ማወቅ አምሯችሁ ወግ ቢጤ ብትጀምሩ ደግሞ በጣም የሚነሽጡ ወጎችን ያጫውቱአቸዋል፡፡ እስቲ የሀረላ ወጎችን በጥቂቱ ልጻፍላችሁ፡፡
*****     *****   *****
     የሀረላ ነገድ ሰዎች ቁመተ ረጃጅም ነበሩ፡፡ አንድ የሀረላ ሰው በቁመቱ የዘመናችንን ሰው ስድስት ጊዜ ያህል ይበልጠዋል፡፡ ግዝፈቱ ደግሞ ለከት የለውም። ትከሻው በጣም ሰፊ ነው። እጅግ በጣም ጠንካራ በመሆኑ ትልልቅ ቋጥኞችን በቀላሉ እየፈነቀለ ይወረውራል። ቤቱን የሚገነባውም ከተራራ ላይ ቋጥኝ እየፈነቀለ ነው። በሸለቆ ውስጥ የሚፈሱ ወንዞችን እየጠለፈ ሽቅብ እንዲፈሱ በማድረግ ውሃው ወደ እርሻው እንዲደርስ የሚያደርግበትን ብልሀት ተክኗል።
 
    ሀረላ ገበሬ መኖሪያ ቤቱ በልበሌቲ (ምዕራብ ሀረርጌ) ቢሆን እርሻው አሰቦት ያህል ሊሆን ይችላል። በየቀኑም ከበልበሌቲ ተነስቶ እርሻው ወዳለበት አሰቦት አካባቢ ይሰማራል። ሚስቱ ሆጃ እና ላቀን (ምሳ) እዚያ ድረስ ትወስድለታለች። ከዚያም ሲመሽ ሀረላው በሬዎቹን እየነዳ ወደቤቱ ያዘግማል። ሀረላው ይህንን ረጅም ርቀት (በደርሶ መልስ 250 ኪ.ሜ. የሚሆን) የሚጓዘው ዘና ብሎ ነው።

     ሀረላ ገበሬ ምሽት ላይ ወደ ቤቱ የሚመለሰው ባዶውን አይደለም፤ በእጁ የአትክልትና ፍራፍሬ መአት ተሸክሞ ነው እንጂ። ይህም ድርጊት ዓመቱን በሙሉ ዘላቂ ሆኖ ይቆያል። ምክንያቱም እርሻው ውሃ አያጣምና። በክረምት ጊዜ ዝናብ አለ፡፡ በበጋ ጊዜ ሀረላው ተራራውን እየሰረሰረ ውሃ ያወጣል፡፡ ስለዚህ እርሻው ለዘወትር በመስኖ ውሃ እንደረጠበ ነው የሚቆየው፡፡

    ታዲያ የሀረላ ነገድ በሚኖርበት ዘመን የኛን ዓይነት ሰዎችም (የኛ ቅድመ አያቶች) ይኖሩ ነበር፡፡ እነዚያ ቅድመ አያቶቻችን ከሀረላ ጋር በአንድ መሬት ላይ ቢኖሩም ከሀረላ ጋር ብዙም ቀረቤታ አልነበራቸውም። ሀረላዎች ዘራችንን ያበላሻሉ በማለት ከነርሱ ጋር አይቀራረቡም፤ አይጋቡምም፡፡ ሀረላዎች በቅድመ አያቶቻችን አጭር ሰውነት እየተገረሙ በሽምብራ ጥላ ስር የሚጋደሙ ድንክዬዎች ይሏቸው ነበር፡፡ የኛ ቅድመ አያቶች እንደጥላ የሚያርፉባቸው ዛፎች በቁመታቸው የሀረላ ገበሬ ከሚዘራው ሽንብራ ስለማይበልጡ ነው ሀረላዎቹ ቅድመ አያቶቻችንን እንዲያ ብለው የሚያናንቁት፡፡

   አንድ የኛ ቅድመ አያት ወደ ሀረላ እርሻ ተደብቆ በመግባት ስርቆት ከፈጸመ ብዙም የሚያጎድለው ነገር ስለሌለ ሀረላዎች እርሻቸው መሰረቁ አይታወቃቸውም፡፡ ሰውየው እሰርቃለሁ ቢል ከአንድ ቲማቲም በላይ መሸከም አይችልምና፡፡ ይህ ሰው በእርሻው ውስጥ ሳለ ሀረላ ድንገት ከያዘው ለቅጣቱ ብዙም አይጨነቅም፡፡ ከሽምብራው ዛፍ ላይ ትንሽ ቅርንጫፍ ይቆርጥና ሌባውን ቅድመ አያታችንን ሶስት ጊዜ ያህል ሾጥ ሾጥ ያደርገዋል፡፡ ሌባው ወዲያውኑ ከዚህች ዓለም ይሰናበታል፡፡
   
   ቅድመ አያቶቻችን የሟቹን ደም ለመበቀል በርከት ብለው ጦርነት ሲያውጁ ደግሞ ሰባት ሀረላ ብቻ ይመረጥና ይላክባቸዋል፡፡ እነዚያም ሰባት ሀረላዎች ለጦርነቱ ቀስትም ሆነ ደጋን አይታጠቁም፡፡ አምስት ያህል ድንጋይ ብቻ ይይዙና ለውጊያ ይሰለፋሉ፡፡ ቅድመ አያቶቻችን ውጊያውን ሲጀምሩ ሀረላዎቹ ለጥቂት ጊዜ ቆም ብለው ያዩዋቸዋል፡፡ ቅድመ አያቶቻችን በአንድ ቦታ በርከት ሲሉላቸው ሀረላዎቹ አንዳንድ ድንጋይ ይወረውሩባቸዋል፡፡ አንዱ የሀረላ ድንጋይም አንድ ሻምበል ጦር (100 ሰው) ይገድላል፤ (ምክንያቱም የሀረላው ድንጋይ በኛና በቅድመ አያቶቻችን ስሌት መሰረት  የተራራ ቋጥኝ ነውና)፡፡ ቀሪው ጦርም ይህንን ሲያይ በፍርሃት ይበተናል፡፡
*****     *****   *****
      ሀረላ በጣም ሀብታም ነው፡፡ እያንዳንዱ ሀረላ ለመቶ ዓመት የሚሆነውን ቀለብ ቀደም ብሎ አጠራቅሟል፡፡ በየዓመቱ የሚያገኘውን አዲስ ምርት ለፈንጠዚያና ለፌሽታ ነው የሚያውለው፡፡ ሁሉም ያሰኘውን ነገር ስለሚያገኝ ገበያ ሄዶ መሸጥና መግዛት የለም፡፡
 
      ታዲያ የሀረላ ፌሽታ የዋዛ እንዳይመስላችሁ! በተለይ ሰርግ ሲሰረግ ከሙሽራው ቤት አንስቶ እስከ ሙሽሪት ቤት ድረስ እንጀራ ይነጠፍና ሰርገኞች በዚያ ላይ እንዲሄዱ ይደረጋል። የሰርጉ ታዳሚዎች እጃቸውን የሚታጠቡትም በወተት ነው።  ማርና ቅቤው ሀያ አራት ሰዓት ይበላል፡፡ ጭፈራና ዳንኪራው ይቀልጣል፡፡ በአጠገባቸው የሚኖሩትን አጫጭር ሰዎች (የኛ ቅድመ አያቶች) ሲመጡ ወደ ድግሳቸው አያስጠጓቸውም፡፡ በረሀብ ቢሞቱ እንኳ ዞር ብለው አያዩዋቸውም፡፡ በተለይ በአንድ ወቅት ሀይለኛ ረሀብ በሀገሩ ገብቶ አጫጭሬዎቹ ለእርዳታ ቢማጸኗቸው ሀረላዎች የሜሪ አንቷኔትን ለምን ኬክ አይበሉም? ዓይነት መልስ ሰጧቸው፡፡ እንዲያውም ጥርግ ብትሉንና ያለ አንዳች ቀለዋጭ በደስታ በኖርን! አሏቸው፡፡
 
   ቅድመ-አያቶቻችን በሀረላ ጭካኔ አዘኑ፡፡ እምባ ለእምባ ተራጩ! ወደ ፈጣሪ ጮሁ፡፡ ፍርድህን በቶሎ አሳየን! አሉት፡፡ ፈጣሪም ጸሎታቸውን ሰማቸው፡፡ ፍርዱንም እንደሚከተለው በየነ፡፡
   
       ሁሉም ሀረላዎች ለትልቅ ጉባኤ በመተሀራ ተሰበቡ፡፡ ጉባኤውንም አደረጉ፡፡ ከጉባኤው በኋላም እንደለመዱት ፌሽታቸውን ጀመሩ፡፡ በዚህን ጊዜም ከየት መጣህ የማይሉት እሳተ ጎመራ ፈነዳ፡፡ ምድር ተቀወጠች፡፡ ሀረላዎች ነደዱ፡፡ ለወሬ ነጋሪ እንኳ አንድ ሰው ሳይተርፍላቸው ሁሉም አለቁ፡፡
 
   በሀረላ ከርሰ መቃብርም ላይ የአሁኑ የመተሀራ (በሰቃ) ሀይቅ ፈለቀ፡፡ አንድ ጥቅም የሌለው መርዝ የሆነ ውሃ! ጥም የማይቆርጥ ለእርሻ የማይሆን ግም ውሃ!! ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁ ግን? ሀረላዎች ያኔ ሲፈነጥዙ የሸኑት ሽንት እኮ ነው!! ግም አሲዳም ውሃ! ሽንተ ርጉማን ዘኮነ ዘብሄረ ሀረላ!! ወዘተ...ጂንኒ ጀቡቲ.......
  
------
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 30/2005