Thursday, November 27, 2014

“አል-ካብሊ”፤ “ሸዛ ዛሂር” እና “ዓሊ ቢራ”



 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
አንጋፋውን ሱዳናዊ ድምጻዊ ዐብዱልከሪም አል-ካብሊን ከዚህ ቀደም ተዋውቀነው ነበር፡፡ ታዲያ የዚህን ጎምቱ ሰው ድምጽ ዛሬ ከአንድ ጓደኛዬ “አይፓድ” ውስጥ ሰማሁትና በሃሳብ ወደ ልጅነቴ ወሰደኝ፡፡ እናም ከርሱ ጋር “ሸዛ ዛሂር” እያልኩ ሳንጎራጎር “ስለዚህ ዘፈን ለምን አንድ ነገር አልጽፍም?” የሚል ሃሳብ መጣብኝ፡፡ እነሆ ጻፍኩላችሁ!!
*****
Abdul-Keriem Al-Kabli, the legendary Sudanese music icon.

አል-ካብሊ ከሌሎች ሱዳናዊያን ድምጻዊያን ከሚለይባቸው ባህሪዎች አንዱ አብዛኛውን ጊዜ ሙዚቃዎቹን በራሱ የሚጽፋቸው መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሙዚቃዎቹ ውስጥ ከሱዳን የዐረብኛ ዘይቤ ይልቅ ብዙ ጊዜ የጥንቱን “ዐረቢያ አልፉስሓ” (Classical Arabic) የሚጠቀም መሆኑ ነው፡፡ ሦሥተኛው ደግሞ ግጥሞቹን በሚጽፈበት ጊዜ ጥንታዊ የሆኑትን “ቀሲዳ”፣ “ቡርዳ” እና “ሙዓለቃት” የሚባሉት የዐረብኛ የስነ-ግጥም ዘይቤዎችን የሚጠቀም መሆኑ ነው፡፡

ከአል-ካብሊ ዘፈኖች መካከል በጣም የሚደነቀው “ሸዛ ዛሂር” ይባላል፡፡ “ሸዛ ዛሂር” የሚደነቀው በጥንቱ ዐረቢያ ፉስሓ የተገጠመ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን ዜማውም በጣም ማራኪ በመሆኑ ነው፡፡ የዘፈኑ አዝማች በኢራኖቹ “ሩባኢያት” ስልት የተጻፈ ሲሆን ተከታዮቹ ግጥሞች ግን በዐረብኛው “ሙዓለቃት” ስልት ነው የተጻፉት፡፡
 *****
“ሸዛ ዛሂር” በጣም የተደነቀው ግን በግጥሞቹ ውበት ሳይሆን በመልእክቱ እና ደራሲው ግጥሙን ሲጽፍ በተከተለው ለየት ያለ ተምሳሌታዊ (allegorical) ዘይቤ ነው፡፡ ግጥሙ ሲጀምር “ሸዛ ዛሂር” ይላል፡፡ “አበባው ፈነዳ… መዓዛው ምድሩን ሞላ” እንደማለት ነው፡፡ ታዲያ በዘፈኑ ውስጥ በአበባ የሚያስመስለው ሰው ሴት ሳትሆን ወንድ ነው፡፡ ወንድን አበባ እያሉ ማሞገስ አለ እንዴ?… በሌላ ቦታ አይታወቅም፡፡ አል-ካብሊ ግን አደረገው፡፡

   አል-ካብሊ የወደደውን ወንድ ሲያሞግስ “ወአንዙሩ ላ አራ በድረን አንተ ለይለተል በድሩ” ይለዋል፡፡ “ወደ ሰማይ ሳንጋጥጥ ሙሉውን ጨረቃ ለማለት አልቻልኩም፤ ምክንያቱም ያንተ ብርሃን ጨረቃውን አጨልሞታል” እንደማለት ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ “አንተ ረሒቁን ለና” እስከማለት ደርሷል (“አንተ የኛ Nectar ነህ” እንደማለት ነው፤ Nectar ወፎችና ንቦች የሚቀስሙት የአበባ ጣፋጬ ክፍል ነው፤ በአማርኛ ምን ይባላል)፡፡

አል-ካብሊ ከዚህም ርቆ ይሄድና የወደደውን ሰውዬ “ለደቱ አል-ኸምረ ዐን ሸፈቲ፤ ለዐለ ጀማለከል ኸምሩ” ይለዋል፡፡ “አንድም የመጠጥ ብርጭቆ ወደ ከንፈሬ አላስጠጋሁም፤ ነገር ግን ውበትህ “ኸምር” ሆኖ አስክሮኛል” ማለቱ ነው፡፡ ለመሆኑ ሰውዬው ምን ነክቶት ነው ወንድን እንዲህ የሚያሞግሰው (አንዳንዱ ሰው ምናልባት… Gay ሳይሆን አይቀርም ይል ይሆናል….ቂቂቂቂ)

የሰውዬውን ማንነት ከኋላ ትመጡበታላችሁ፡፡ አሁን የዘፈኑን ግጥም ተመልከቱ፡፡

(አዝማች)
ሸዛ ዛህሪን ወላ-ዛህሩ
ፈዐይነ ዚሉ ወን-ነህሩ
ረቢዑ ሪያዲና ወላህ
አሚን አህ ፊከ አን-ነሽሩ
-----
ወሐዘ ነሁሩ የብሱሙሊ ዐኒ-ድ-ዱንያ ወየፍተሩ
ወአንዙሩ ላ አራ በድረን አአንተ ለይለተል በድሩ፡፡
-----
ወቢሂ ሱክሩን ተመለከኒ ወዐጀቡን ከይፈ ቢሂ ሱክሩ
ረድቱ አል-ከእሳ ዐን ሸፈቲ ለዐለ ጀማለከል ኸምሩ፡፡
----
ነዐም አንተ ረሒቁን ለና ወአንተ ሲሕሩ ወልኢጥሩ
ወአንተ ሲሕሩ ሙቅተዲረን ወገይረል ሀይ ወሀዋ ሲሕሩ፡፡
---
ኹዙ ዱኒያ ቢዐጅማኢሀ ሐቢቡን ዋሒዱን ዙኽሩ
ኢዛ ጃአት መጣሊኡሁ ፈኩሉ ሰማኡና በድሩ፡፡
---
ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያዋቱና ኩስሩ፡፡
ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያቱና ኩስሩ፡፡
*****
የአል-ካብሊ ግጥም ቅኔያዊ ፍቺ በመጨረሻው ስንኝ ላይ ነው የሚገኘው፡፡ “ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያቱና ኩስሩ” ማለት “ዱኒያ ይህቺ ናትና እዩዋት፤ መጨረሻ ላይ ተሰባሪ ናት” ማለት ነው፡፡ እውነትም ዱኒያ ተሰባሪ ናት፡፡ አል-ካብሊ ግን ሰውዬን አድንቆት ሲያበቃ “ዱኒያ ተሰባሪ ናት ብሎ” ዘጋው፡፡ ከፊት የተናገረውን መቃረን ይሆናል አይደል…?

ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ አል-ካብሊ እንዲህ ያደነቀው ሰው ጓደኛው ነበረ፡፡ ይህ ጓደኛው ገጣሚ ሲሆን በጣም ውብ የሆኑ ግጥሞችን በመጻፍ ይታወቃል፡፡ አንድ ቀን ግን ሳይጠበቅ “ጭጭ” አለ፡፡ ምንም ሳይታመም ነፍሲያው ወጣች፡፡ አል-ካብሊ በዚህ ድንገተኛ አደጋ ተደናገጠ፡፡ ልቡ ተሰበረች፡፡

ጓደኛው ከተቀበረ ከጥቂት ቀናት በኋላ በሐዘኑ የተጎዳው አል-ካብሊ በምሽት ከቤቱ ወጥቶ ሰማይ ሰማዩን ማየት ጀመረ፡፡ ሰማዩን እያየ ሟች ጓደኛውን ሲያስታውስ ይህ ግጥም መጣለት፡፡ ወዲያውኑ “ሸዛ ዛሂር”ን ጻፈውና መጫወት ጀመረ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ በአንድ አልበም ውስጥ አካተተው፡፡ ግጥሙ በሱዳኖች ዘንድ ሲሰማ ዐጂብ ተባለ፡፡ የሙዚቃ ገምጋሚዎች በበኩላቸው የአል-ካብሊ የምንጊዜም ምርጥ ዘፈን በማለት ሰየሙት፡፡
*****
አል-ካብሊ “ሸዛ ዛህር”ን ከጻፈው በኋላ እንደ መግቢያ የሚጠቀምበት አጭር እንጉርጉሮም አክሎለታል፡፡ ዘፈኑ ለገጣሚው ጓደኛው የተጻፈ መሆኑን በግልጽ የሚያሳውቀው በዚህ እንጉርጉሮ ውስጥ ነው፡፡ ይህ እንጉርጉሮ በተለምዶ “ማለሁ” እየተባለ የሚጠራው ነው (አል-ካብሊ እንጉርጉሮውን “ማለሁ” በማለት ነው የሚጀምረው፤ ዐረብኛ እንዲህ ሲባል “ለምን ሲል ነው?” የሚል ዘይቤአዊ ፍቺ አለው)፡፡ ታዲያ አል-ካብሊ ብዙ ጊዜ ዘፈኑን ከእንጉርጉሮው በመለየት ነው የሚጫወተው፡፡ አንዳንዴ ግን ሁለቱንም በአንድ ላይ ይዘፍናቸዋል፡፡ ሁለቱ ግጥሞች ሲዘፈኑ የተለያየ የድምጽ ውጣ-ውረድን ስለሚጠይቁ ማንም ዘፋኝ ነኝ ባይ በአንድ ላይ ሊዘፍናቸው ይቸገራል፡፡ እኔ ባለኝ ልምድ ግን አንድ ሰው ሁለቱንም በአንድነት ዘፍኖአቸው ተሳክቶለት አይቼአለሁ፡፡

አዎን! ዓሊ ቢራ ነው፡፡ ዓሊ በ1998 የእንቁጣጣሽ በዓልን በማስመልከት በሸራተን አዲስ በተዘጋጀው የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ እንጉርጉሮውንና ሸዛ ዛህርን አንድ ላይ ዘፍኖአቸዋል፡፡ የዓሊ ቢራ አዘፋፈን ውብ መሆኑን ለማየት በዩ-ቲዩብ ላይ የተጫነውን ቪዲዮ ይመልከቱ፡፡
(ቪዲዮውን ለማለት የሚከተለውን ሊንክ ክፈቱ)፡፡

በነገራችን ላይ ዓሊ ቢራ “ሸዛ ዛህር”ን ብቻ ሳይሆን ሌሎች የሱዳን ዘፈኖችንም ሲጫወት በጣም ይሳካለታል፡፡ የዚህ ስኬት አንደኛው ምክንያቱ ደግሞ ዓሊ ግጥሞቹ የተጻፉበትን “ዐረቢያ አል-ፍስሓ”ን በትክክል መናገር የሚችል መሆኑ ነው፡፡ (ዐረቢያ አል-ፉስሓ ሃያ ስምንቱን የዐረብኛ ድምጾች በትክክል ማውጣትን ይጠይቃል)፡፡
*****
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 18/2007
--

Wednesday, November 26, 2014

“ጥጋብ አይቻልም”



ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
እነሆ በድጋሚ ወደ ተረት ዓለም ልወስዳችሁ ነው፡፡ ድሮ የሰማሁት አንድ ተረት ከሰው ልጅ ደካማ ባህሪያት መካከል የሚቆጠረውን “ጥጋብ”ን በተዋበ መንገድ እንዴት እንደሚሄሰው እዩት፡፡
-----
በአንዲት መንደር የሚኖር አንድ ደሃ ሰው የሚበላውን እያጣ ይቸገር ነበር፡፡ ሰውዬው ብዙ ዘመን በችግር ካሳለፈ በኋላ “በተወለድኩበት ምድር በረሃብ ከምሞት ወደ ሌላ ሀገር ልሂድና ሲሳዬን ልፈልግ” በማለት ተሰደደ፡፡ ብዙ ከሄደ በኋላ ድካም ሲጀምረው ከአንድ ዛፍ ስር አረፍ አለ፡፡ ልክ እንደተቀመጠም ከዛፉ ላይ የነበረችው አንዲት በቀቀን “ጥጋብ አይቻልም” እያለች መዘመር ጀመረች፡፡ ሰውዬውም ወደላይ እያንጋጠጠ “እንዲህ ስትይ አታፍሪም እንዴ?! ረሃብ ነው የማይቻለው እንጂ ጥጋብማ በደንብ ነው የሚቻለው” በማለት አጸፋውን መለሰላት፡፡

  ሰውዬው የሚበቃውን ያህል ካረፈ በኋላ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ ብዙ ከተጓዘ በኋላም ወደ አንዲት ትንሽ ከተማ ገባ፡፡ እዚያም ልመናውን ጀመረ፡፡ ብዙ ቤቶችን አዳረሰ፡፡ የከተማዋ ሰዎችም ያላቸውን ሰጡት፡፡ ሰውዬው ምሽቱን ከአንድ በረንዳ ስር አሳለፈ፡፡ በማግስቱም ልመናውን በመቀጠል ከአንድ ሰፊ ግቢ ደረሰ፡፡ እዚያም “ስለ አላህ! ያላችሁን ስጡኝ! ተዘከሩኝ” በማለት ልመናውን ተያያዘው፡፡ የቤቱ ባለቤት የግቢውን በር ከፈተችና ለማኙን አየችው፡፡ ሰውዬው ከመጎሳቆሉ በስተቀር መልከ መልካም ነው፡፡ አንድም የአካል ጉዳት የለበትም፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሰው መለመኑ ስላስገረማት “አንተ ሰው! እንደዚህ ጤነኛ ሆነህ ነው እንዴ የምትለምነው?” አለችው፡፡ “ምን ላድርግ እመቤቴ ተቸግሬ ነው እኮ!” በማለት መለሰላት፡፡
“ለምን ሰርተህ አትበላም?”
“ስራ የለኝም፤ ትናንት ነው ከሌላ ሀገር የመጣሁት”
“እና ልትለምን ነው የመጣኸው?”
“አዎና እመቤቴ! ስራ የለኝም እኮ”
“ስራ ቢሰጥህ ትሰራለህ?”
“አዎን እሰራለሁ”

ሴትዮዋ የሀብታም ሰው ሚስት ነበረች፡፡ ባሏ በድንገት ሲሞትባት ከባሏ በወረሰችው ገንዘብ እየነገደችና እያስነገደች ትኖር ነበር፡፡ በመሆኑም ለማኙን ሰውዬ ከሌሎች ተቀጣሪዎቿ ጋር እንዲሰራ ፈቀደችና ወደ ግቢዋ አስገባችው፡፡ ከዚያም የለበሰውን ቡትቶ እንዲያወልቅ በመንገር አዲስ ልብስ እንዲሰጠው አደረገች፡፡ የሚኖርበትም ቤት ተሰጠው፡፡ ቀለብም ተቆረጠለት፡፡ ሰውዬወም በሴትዮዋ ለጋስነት እየተገረመና ምስጋና እያቀረበ የተመደበለትን የሱቅ አሻሻጭነት ስራ መስራት ጀመረ፡፡

 ሰውዬው ከስራው ጋር በጥቂት ጊዜ ውስጥ ተለማመደ፡፡ በስራው ውስጥ ከሁሉም ሰራተኞች በላጭ ሆኖ ተገኘ፡፡ በታማኝነቱም የተመሰገነ ሆነ፡፡ ሴትዮዋ በሰውዬው ባተሌነትና በታማኝነቱ ልቧ ተነካ፡፡ እያደርም በፍቅሩ ተነደፈች፡፡ ብዙ አውጥታ ካወረደች በኋላም ልታገባው ወሰነች፡፡ እናም ለሰውዬው ይህንኑ ነገረችው፡፡

   ይሁንና ሰውዬው በሴትዮዋ አባባል አኮረፈ፡፡ “እኔ ከትቢያ ላይ የተነሳሁ አንድ ድሃ ሰው ነበርኩ፤ እንዴት ካንቺ ጋር በጋብቻ መተሳሰር እችላለሁ?” አላት፡፡ ሴትዮዋ ምክንያቱን ነገረችው፡፡ ከብዙ ክርክር በኋላ ሰውዬው ሊያገባት ወሰነ፡፡ በመሆኑም ድል ያለ ድግስ ተደግሶ ያ የጥንት ለማኝ የቤቱ አባወራ ለመሆን በቃ፡፡

ሰውዬው አባወራ ከሆነ በኋላም ኃላፊነቱን በትጋት መወጣቱን ቀጠለ፡፡ ሴትዮዋም ይበልጥ እያፈቀረችው ሄደች፡፡ “ይሄ ሰውዬ ለምንጊዜውም የሚከዳኝ አይመስለኝም፤ ስለዚህ የስራውን ኃላፊነት በሙሉ ለርሱ ልስጠው፤ ትንሽ ቆይቼ ደግሞ ድርጅቱን በርሱ ስም አዛውራለሁ” በማለት ወሰነች፡፡ ከዚያም ሰውዬውን ጠራችና እንዲህ አለችው፡፡

“እስከዛሬ ድረስ እንደ ሰራተኛም እንደ ባልም ሆነህ ጥሩ ጊዜ ከኔ ጋር አሳልፈሃል፤ ባሳየኸኝ ታማኝትና በሰጠኸኝ ፍቅር ሙሉ ደስተኛ ነኝ፡፡ ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ የድርጅቱ ሃላፊም ሆነ ተቆጣጣሪ አንተ ነህ፤ ካንተ በላይ ማንም የለም፤ እኔ ራሴ በአንተ ስር ነኝ” አለችው፡፡ይህንን ካለችው በኋላ የድርጅቱን አስፈላጊ ሰነዶች አስረከበችው፡፡ በቤቷ የሚገኙ የካዝና ቁልፎችንም ስታስረክበው እንዲህ አለችው፡፡

  “እኝሁልህ የካዝናዎቻችን መቆለፊያዎች! ከዛሬ ጀምሮ ባንተ ኃላፊነት ስር ሆነዋል፤ ወርቁም ሆነ አልማዙ በብዛት አለልህ፤ ነገር ግን የአንዱን ካዝና ቁልፍ አልሰጥህም፤ በዚያ ውስጥ ምን እንዳለ እንድትጠይቀኝም አልፈቅድልህም፤ እርሱን የጠየቅከኝ እለት መቆራረጣችንን እወቅ”፡፡ ሰውዬውም ስለጉዳዩ ምንም ነገር ላይጠይቃት ቃሉን ሰጣት፡፡ በመሃላ ጭምር አረጋገጠላት፡፡

    ባልና ሚስቱ እንዲህ ከተግባቡ በኋላ ኑሮአቸው ደራ፡፡ ትዳራቸው ይበልጥ ተሟሟቀ፡፡ ድርጅታቸው በትርፍ ላይ ትርፍ መዛቁን ቀጠለ፡፡ ሰውዬውም ምንም ተቆጣጣሪ ሳይኖረው ገንዘቡን እንዳሻው ያወጣ ጀመር፡፡ እያደር ግን የሰውዬው ልብ መቀየር ጀመረች፡፡ በአንድ ካዝና እና በውስጠ ሚስጥሩ ላይ ጥያቄ እንዳያቀርብ የተጣለበትን እግድ ሲያስታውስ ገና የሀብት ጣሪያ ላይ ያልደረሰ ሆኖ ተሰማው፡፡ ያንን ካዝና ከፍቶ አለማየቱም ያንገበግበው ጀመር፡፡ ሴትዮዋ አንዱን ካዝና ነጥላ በማስቀመጧም “እወድሃለሁ የምትለው ከልቧ አይደለም” በማለት ወቀሳት፡፡ በመሆኑም ካዝናውን ከፍቶ ለማየት ተመኘ፡፡ ወደሴትዮዋ ሄዶም ጥያቄውን አቀረበ፡፡
   
  ሴትዮዋ በጥያቄው ተደናገጠች፡፡ ተገረመችም፡፡ ቃሌን ያከብራል ብላ የገመተችው ሰው ቃል አባይ ሆኖ በመገኘቱ ተናደደችበት፡፡ ነገር ግን ከሰውዬው ፍቅር ስለያዛት የመጨረሻ እድል ልትሰጠውና ከመንገዱ ልትመልሰው ወሰነች፡፡ እንዲህም አለችው፡፡
   “አረ አንተ ሰው የፈጠረህን ፍራ! ስለዚህ ካዝና ጉዳይ አንድም ጥያቄ ላትጠይቀኝ ቃል ኪዳን ሰጥተህኛል እኮ፤ እባክህ ይህንን ጥያቄህን ተውና በሰላም አብረን እንኑር”
“አንቺ ራስሽ እወድሃለሁ የምትይው ከልብሽ አይደለም፤ ያንን ካዝና ከፍተሸ ከውስጡ ያለውን ነገር ካላሳየሽኝ አትወጂኝም ማለት ነው”
“አረ አንተ ሰው መሀላ አታፍርስ! እረፍልኝ ብዬሃለሁ”
“የካዝናውን ቁልፍ እንድትሰጭኝ እፈልጋለሁ”

ሴትዮዋ ተናደደች፤ ነገር ግን ሰውዬውን ስለምትወደው በሽማግሌ ልታመስክረው ሞከረች፡፡ ሽማግሌዎችም “መሃላህን አትብላ! የፈጣሪ ቁጣ ይወርድብሃል፤ እንደ ድሮው በሰላም ብትኖሩ ይሻላል” አሉት፡፡ ሰውዬው ግን “ካዝናው ካልተከፈተ ሞቼ እገኛለሁ” በማለት ሙግቱን አፋፍሞ ቀጠለ፡፡ ሴትዮዋም በነገሩ ተስፋ ቆረጠች፡፡ ሰውዬው ወደ ኋላ የማይመለስ መሆኑን ካረጋገጠች በኋላ የከተማዋ ሽማግሌዎችና ታዋቂ ሰዎች እንዲሰበሰቡ አደረገች፡፡ ከዚያም ካዝናውን ከፈተችውና ከውስጡ ያለውን እቃ አወጣች፡፡ በሀይለ ቃልና በቁጭት በሰውዬው ፊት ላይ ወረወረችው፡፡
----------
ከካዝናው ውስጥ የተገኘው እቃ ሰውዬው ከሀገሩ የመጣበት ቡትቶ ልብስ እንጂ እንቁ ወይንም ሌላ የከበረ ጌጣጌጥ አልነበረም፡፡ ሴትዮዋ ለክፉ ቀን መጠባበቂያ እንዲሆናት ነው ከካዝና ውስጥ የቆለፈችበት፡፡ እውነተኛው ቀን ሲደርስ ልብሱን እዚያ ማስቀመጧ ትክክል እንደሆነ ተረዳች፡፡ ልብሱን በሰውዬው ፊት ላይ ከወረወረችለት በኋላም እንዲህ አለችው፡፡
“አንተ ውለታ ቢስ! ቶሎ ብለህ የኔን ልብስ አውልቅ! አንተ ያመጣኸውን ልብስ ልበስና ከዚህ ቤት ጥርግ ብለህ ጥፋልኝ”

ሰውዬው በድንጋጤ ክው ብሎ ቀረ፡፡ ከትቢያ ተነስቶ በተከበረበት ከተማ መዋረዱ ከፍተኛ እፍረት ውስጥ ጣለው፡፡ በመሆኑም ከከተማዋ በደረቅ ሌሊት ጠፋ፡፡ ወደ ሀገሩ ሊመለስም ጉዞውን ተያያዘው፡፡ ረጅም ርቀት ከተጓዘ በኋላ በቀቀኗን ካገኘበት ቦታ አረፈ፡፡

  ታዲያ በቀቀኗ “ጥጋብ አይቻልም” እያለች የድሮውን መዝሙር መዘመሯን እንደቀጠለች ነው፡፡ ሰውዬውም “እውነትሽን ነው! ጥጋብን ከእግር እስከ ራሱ አይቼው የማልችለው ዐይነት ሲሆንብኝ ወደ ድሮው የድህነት ህይወቴ እየተመለስኩ ነው” አላትና የመዝሙሩን ሐቀኛነት አረጋገጠላት፡፡
-----------
አይጣል ነው መቼስ! በርግጥም ጥጋብ አይቻልም፡፡ በእውነታው ዓለም የተከሰቱ በርካታ ታሪኮችን ከዚህ ጋር ማነጻጻር ይቻላል፡፡ ሀብትን ስናገኝ  አዕምሮአችን ከርሱ ጋር ካላደገ የሰራነው ሁሉ ወደ ዜሮ ሊመልስብን ይችላል፡፡ ለሁሉም ግን ፈጣሪያችን ከእንዲህ ዓይነቱ ክፉ እጣ ይሰውረን!
አሚን!
------
መጋቢት 19/ 2006
አፈንዲ ሙተቂ

(ተረቱን ያጫወቱኝ የገለምሶ ትልቁ መስጊድ ኢማም የሆኑት ሼኽ ሙኽታር አሊይ ናቸው፤ ዘመኑም እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር 1988 ነበር፤ ሼኽ ሙኽታር በአሁኑ ጊዜ የ85 ዓመት አዛውንት ናቸው፤ አላህ ጤናውንና ብርታቱን ይጨምርላቸው)፡፡

Thursday, October 30, 2014

ሁለት የሀረር ተረቶች



 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-----
“ሀረር ጌይ” በተሰኘው መጽሐፌ ውስጥ “ሀረር የባግዳድ እህት ናት” የሚል የረጅም ጊዜ ልማድ እንዳለ አጫውአችኋለሁ፡፡ ይህም አመለካከት የመጣው ሁለቱ ከተሞች የሚመሳሰሉ በመሆናቸው ነው፡፡ ከተሞቹን ከሚያመሳስሏቸው የህይወት ዘርፎች መካከል አንዱ እምቅ የስነ-ቃል ሀብታቸው ነው፡፡ ከነዚህ የስነ-ቃል ሀብቶች ቀዳሚ ሆኖ የሚጠቀሰው ተረት ነው፡፡ የባግዳድ ተረቶችን በ“አንድ ሺህ አንድ ሌሊት” በኩል አንብበናቸዋል፡፡ የሀረር ተረቶች ግን በመጽሐፍ ያልተሰበሰቡ በመሆናቸው ከብዙኃኑ አንባቢ ዘንድ ሊደርሱ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ እነርሱንም በመጽሐፍ የሚሰበስብ የብዕር ጀግና ያስፈልገናል፡፡

በዚህ ጽሑፍ ሁለት የሀረር ተረቶችን አጋራችኋለሁ፡፡ ሁለቱንም ተረቶች በልጅነቴ የማውቃቸው ቢሆንም በሀረር ከተማ ቆይታዬ በአዲስ መልክ ሰምቼአቸዋለሁ፡፡  

የሓኪም ጋራ መሰንጠቅ

በጥንት ዘመን ሀረር በድርቅ ተመታች፡፡ በድርቁ ሳቢያም ምንጮቿና ወንዞቿ ደረቁ፡፡ አንድ “ኤላ” (የውሃ ጉድጓድ) ግን በተአምራዊ መንገድ ከመጥፋት ተረፈ፡፡ ይሁንና መገኛው ያልታወቀ ትልቅ ዘንዶ ከጉድጓዱ አፋፍ ተቀምጦ “ኤላው የኔ ነው” በማለቱ ከኤላው ውሃ መቅዳት አስቸጋሪ ሆነ፡፡ የሀረር ህዝብ ከኤላው ውሃ መቅዳት ከፈለገ በየዓመቱ አንዲት ቆንጆ ወጣት መገበር እንዳለበት ዘንዶው በአዋጅ አስታወቀ፡፡ የመጠጥ ውሃ ማግኘት የቸገረው የሀረር ህዝብም አማራጭ ሲያጣ ለዘንዶው በመገበር ከኤላው ውሃ ለመቅዳት ተገደደ፡፡

ለዘንዶው የምትሰጠው ልጅ በእጣ ነው የምትወሰነው፡፡ እጣው የሚወጣበት ሁኔታ ግን ፍትሐዊ አልነበረም፡፡ የሀብታምና የባለስልጣናት ልጆች በስውር ዘዴ ከእጣው ውጪ እንዲሆኑ ይደረግና የድሃ ልጆች ብቻ እየተመረጡ ለዘንዶው ይሰጣሉ፡፡ ድሆቹ ይህንን በደል ቢያውቁትም ከሀብታሞቹ ጋር መፎካከር ስለማይችሉ ልጆቻቸውን ለዘንዶው እየገበሩ እምባቸውን መርጨት ግዴታ ሆነባቸው፡፡

ታዲያ በአንድ ዓመት ልጅ የመገበሩ እጣ የደረሰው ለአንዲት “ተቂይ” (አላህን የምትፈራ) ሴት ነው፡፡ ያቺ ሴት አንዲት ልጅ ብቻ ነበራት፡፡ ልጅቷንም ያገኘችው በስተእርጅና ሲሆን ባለቤቷ ከልጅቷ መወለድ በኋላ ሞቶባታል፡፡ በመሆኑም ሴትዮዋ አንድዬ ልጇን እንደ እናትና እንደ አባት ሆና ነው ያሳደገቻት፡፡  እንግዲህ እነዚያ እጣ አውጪዎች ሴትዮዋ በስተእርጅና ያገኛትንና በድህነት ያሳደጋችትን ያቺኑ ልጅ ለዘንዶው እንድትገብር ነው የፈረዱት፡፡

   ይሁንና ሴትዮዋ ልጇን ለዘንዶው አላስረክብም አለች፡፡ የሰፈሯ ሰዎች “እምቢ ካልሽ እኮ ዘንዶው አንቺንም ጨምሮ ይበላሻል” እያሉ ቢያስፈራሯትም ሴትዮዋ ወይ ፍንክች በማለት በቃሏ ጸናች፡፡ ሰዎቹም “በቃ! ውርድ ከራሳችን!! ዘንዶው ቢበላሽ ተጠያቂ አይደለንም” በማለት ብቻዋን ተዋት፡፡ ወደ ዘንዶው ሄደውም ስለሴትዮዋ እምቢተኝነት ነገሩት፡፡ ከዚያም በየቤታቸው ሆነው ተከታዩን ነገር መጠባበቅ ጀመሩ፡፡ ሴትዮዋም ልጇን ከምታስረክብበት ዕለት በፊት ባለው ምሽት የዘንዶውን ጭካኔና የእጣ አውጪዎቹን አሻጥር እያነሳች ፈጣሪዋን ስትለምን አደረች፡፡ በማግስቱም ከቤቷ ቁጭ ብላ ዘንዶው የሚያመጣውን መቅሰፍት መጠባበቅ ጀመረች፡፡

 ሴትዮዋ ልጇን የምታስረክበው ከጧቱ በሶስት ሰዓት ገደማ የነበረ ቢሆንም ዘንዶው በሰዓቱ ግብሩን አላገኘም፡፡ በዚህም የተናደደው ዘንዶ ሴትዮዋን ከነልጅቷ ሊውጣት እጅግ በሚያስፈራ ግርማ ወደ ቤቷ መጓዝ ጀመረ፡፡ የሰፈሩ ሰዎችም “ሊበላት ነው፤ ሴትዮዋ አለቀላት!” እያሉ በአድናቆትና በተመስጦ ትርዒቱን ይመለከቱ ገቡ፡፡

ዘንዶው አቧራውን እያቦነነ ከሴትዮዋ ቤት አጠገብ ደረሰ፡፡ ሴትዮዋንም ሊውጣት መንደርደር ጀመረ፡፡ ፍላጎቱን ከመፈጸሙ በፊት ግን ፈጣሪ ውጥኑን አከሸፈበት!! እጅግ ግዙፍ የሆነ ንስር (አሞራ) ከሀረር በስተሰሜን አቅጣጫ በመምጣት ዘንዶውን ከመሬት ላይ “ላጥ” አድርጎ አነሳው፡፡ ንስሩ ዘንዶውን ወደ ሰማይ በማውጣት ላይ ሳለም የዘንዶው ጭራ ሀረርን በደቡብ በኩል የከበበውን የሀኪም ጋራን በሁለት ቦታ ከፈለው፡፡
 
  ያ ከይሲ ዘንዶ ፈጣሪዋን የምትፈራው ሴትዮ ባደረገችው ጸሎት ተወገደ፡፡ በሀረር ከተማ ላይ የተጣለው ልጅን የመገበር ግዴታም ለዘልዓለሙ ተነሳ!! ይሁንና ያኔ በዘንዶው ጭራ የተከፈሉት ሁለቱ የሐኪም ጋራ ኮረብቶች በአንድ ላይ ሳይመለሱ እስከዚህ ዘመን ድረስ ዘለቁ፡፡

አሚር ሆይ! አንተ “ኸይሩ”ን ብቻ አስብ፤ “ለሸሩ” ባለቤት አለውና!!
------
በጥንት ዘመን አንድ ቅን ሰውዬ በሀረር ከተማ ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ የመጀመሪያው ልጁ ርህሩህና የዋህ የነበረ ሲሆን ሁለተኛው ልጁ ግን ተንኮል እየፈጠረ ሰዎችን ማሞኘትና መሳቅ ይወድ ነበረ፡፡ አባትዬው ትንሹን ልጅ ቢመክረው አልሰማ እያለ አስቸገረው፡፡ ስለዚህ በትንሹ ልጅ ተስፋ የቆረጠው አባት ዘወትር ትልቁን ልጅ እየጠራው “ልጄ ሆይ! አንተ ደጉን ብቻ አስብ፡፡ ለተንኮል ባለቤት አለውና” የሚል ምክር ይሰጠው ነበር፡፡ አባት በዚህም ሳያበቃ ለትልቁ ልጅ “ዓሊ ኸይሮ” (ቅን አሳቢው ዓሊ) የሚል ቅጽል አወጣለት፡፡ ትንሽየውን ግን “ዓሊ ሸርሮ” (ተንኮለኛው ዓሊ) በማለት ሰየመው፡፡
 
   ከጊዜ በኋላ አባት የአዱኛውን ዓለም ተሰናበተ፡፡ በዚህም የተነሳ ልጆቹ ተቸገሩ፡፡ ኑሮ በጣም ከበዳቸው፡፡ በመሆኑም ወደ ሀረሩ አሚር ሄደው በችግር መቆራመዳቸውን ነገሩት፡፡ አሚሩ በአጋጣሚ የቤተ መንግሥት ከብቶችን የሚጠብቅ ሰው ይፈልግ ነበርና ወንድማማቾቹ ለእረኝነት እንዲቀጠሩ ጠየቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹ ለስራው የሚሰጣቸውን ምንዳ ሲጠይቁት ከሚበሉት ምግብና ከሚለብሱት ልብስ በተጨማሪ በዓመቱ መጨረሻ ላይ አንዲት ጊደር እንደሚያገኙ አሳወቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹም ከአሚሩ የቀረበላቸውን ጥያቄ በደስታ ተቀበሉትና ስራቸውን ጀመሩ፡፡

ወንድማማቾቹ በመቶዎች የሚቆጠሩትን የአሚሩን ከብቶች “አው-ሓኪም”፣ “አቦከር” እና “ሸድዳ ዋ መድዳ” ወደሚባሉት ተራሮች እያሰማሩ በትጋት ማገዱን ተያያዙት፡፡ ስራቸውን በደህና ሁኔታ እያከናወኑ ዓመቱን አገባደዱት፡፡ የዓመቱ መጨረሻ እየተቃረበ ሲመጣ ግን የ“አሊ ሸርሮ” ልብ በግለኝነት መመታት ጀመረች፡፡ ለምንዳ የምትሰጣቸውን ጊደር ጉዳይ ሲያስብ አዕምሮው በስስት ተወጠረ፡፡ በመሆኑም “ወንድሜን ገድዬው ጊደሪቱን የግሌ ማድረግ አለብኝ” በማለት ወሰነ፡፡ እቅዱንም በአው ሓኪም ተራራ ላይ ለመፈጸም ቆረጠ፡፡

ወንድማማቾቹ ከብቶቹን ወደ “ሓኪም” ተራራ በወሰዱበት በአንደኛው ቀን “አሊ ሸርሮ” ለወንድሙ “አንተ ከዚህ ሆነህ ከብቶቹን ጠብቅ፤ እኔ ተራራው ላይ ወጥቼ ለምለም ሳር እንዳለ ልይና ልመስ” አለው፡፡ “አሊ ኸይሮ”ም በቀረበለት ሃሳብ ተስማምቶ ከብቶቹን ለብቻው መጠበቅ ጀመረ፡፡ “አሊ ሸርሮ” ከተራራው ላይ እንደ ወጣ ትልቅ ድንጋይ አንቀሳቅሶ ወንድሙ ወዳለበት አቅጣጫ ቁልቁል ለቀቀው፡፡ ድንጋዩ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ ወረደ፡፡ ከ“አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ ግን ወደ ወርቅነት ተቀየረ፡፡ “አሊ ኸይሮ” በዚህ ተአምር ተገረመ፡፡ “ወደ ወርቅነት የተቀየረው ድንጋይ እኔና ወንድሜ ሀብታም እንድንሆን ዘንድ ከአላህ የተሰጠን ነው” በማለት በደስታ ፈጣሪውን አመሰገነ፡፡ የተፈጠረውንም ተአምር ለወንድሙ ለመንገር በጉጉት ይጠባበቅ ጀመር፡፡
 
 “አሊ ሸርሮ” በበኩሉ “አሊ ኸይሮ በድንጋይ በመገደሉ “ጊደሪቱ የኔ ብቸኛ ሀብት ትሆናለች” እያለ በደስታ ከተራራው ወረደ፡፡ ወንድሙ ወደነበረበት ቦታ ሲደርስ ግን ያልጠበቀውን ነገር አየ፡፡ “ይህ ወርቅ ከየት ነው የመጣው?” በማለትም ወንድሙን ጠየቀው፡፡ አሊ ኸይሮም “አንድ ትልቅ ድንጋይ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ መጥቶ እኔ ጋ ሲደርስ ይህንን ወርቅ ሆነ” በማለት መለሰለት፡፡ “አሊ ሸርሮም “ድንጋዩ የተንከባለለው ከስሩ የነበረውን ለምለም ሳር ለማየት ብዬ ስላንቀሳቀስኩት ነው፤ እዚህ ደርሶ ወደ ወርቅ ከተቀየረ እኔም የራሴ ወርቅ ሊኖረኝ ይገባል፡፡ ስለዚህ አንተም በተራህ ወደ ተራራው ውጣና ሌላ ድንጋይ አንከባልልኝ” አለው፡፡

“አሊ ኸይሮ”ም ከወንድሙ የሰማውን ሳይጠራጠር ወደ ተራራው ወጥቶ ትልቅ ድንጋይ አነሳና “አሊ ሸርሮ” ወደነበረበት አቅጣጫ አንከባለለው፡፡ ይሁንና ድንጋዩ ወደ ወርቅነት ሳይቀየር “አሊ ሸርሮ”ን ጭፍልቅ አድርጎ ገደለው፡፡ “አሊ ኸይሮ” ከተራራው ወርዶ ወንድሙ ወደነበረበት ስፍራ ሲሄድ ወንድሙ ሞቶ አገኘው፡፡ በዚህም በጣም ደነገጠ፡፡ ወደ ሀረሩ አሚር ሄዶም የተከሰተውን ሁሉ አንድ በአንድ ነገረው፡፡ ሆኖም አሚሩ ሊያምነው አልቻለም፡፡ “ወንድምህን ራስህ ነህ የገደልከው” በማለትም ከሰሰው፡፡ በመሆኑም “ነፍስ ያጠፋ ሰው ይገደል” በሚለው የሀረር ከተማ ጥንታዊ ህግ መሰረት በድንጋይ ተጨፍልቆ እንዲሞት ተፈረደበት፡፡
 
“አሊ ኸይሮ”ም ፍርዱ ሊፈጸምበት ወደ “ሐኪም” ተራራ ግርጌ ተወሰደ፡፡ ከተራራው ላይ ትልቅ ድንጋይ ተንዶ ቁልቁል ተወረወረበት፡፡ ይሁንና ድንጋዩ “አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ እንደገና ወርቅ ሆኖ ቁጭ አለ፡፡ የቅጣቱን አፈጻጻም ለማየት በስፍራው ተሰብስቦ የነበረው የሀረር ህዝብም በተፈጠረው ነገር በጣም ተገረመ፡፡ “ይህ ተአምር ልጁ ወንድሙን እንዳልገደለ በሐቅ ይመሰክራል” በማለትም ደመደመ፡፡ የሀረሩ አሚር በበኩሉ “የዓሊ ኸይሮ”ን ተአምር ሲያይ “በህይወቴ ስፈልገው የነበረውን ሐቀኛ ሰው ዛሬ አገኘሁት” የሚል ቃል ተናገረ፡፡ “አሊ ኸይሮ”ንም የዙፋኑ ወራሽ በማድረግ ሾመው፡፡
-----
ወደ ሀረር ከተማ ከመጣችሁ “Amiroo! Kheyruma yaadi, Sharriin abbuma eeydii” የሚል አባባል ትሰማላችሁ፡፡ “አሚር ሆይ! አንተ ኸይሩን ብቻ አስብ፤ ለሸርሩ ባለቤት አለውና” እንደማለት ነው፡፡ ከአባባሉ ጀርባ ብዙ ታሪኮች ይነገራሉ፡፡ ከነዚያ ታሪኮች መካከል አንዱ ከላይ የቀረበው ተረት ነው፡፡

 በተረቱ እንደተገለጸው ተንኮለኛ ሰው በለስ የቀናው መስሎት ብዙ የሸር ትብታቦችን ሊተበትብ ይችላል፡፡ ይሁንና እንደዚህ ዓይነቱ ሰው አጓጉል ሆኖ ነው የሚቀረው፡፡ የማታ ማታ ራሱ በሸረበው የተንኮል ድር መታሰሩ የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህ በህይወት እያለ ደግ ደጉን ብቻ አስብ!! ለተንኮሉ ባለቤት አለውና!!
በድጋሚ Amiroo kheyruma yaadi, Sharriin abuma eeydi ብለናል፡፡
----
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 20/2007
-----
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 8/2007
ሀረር-ምስራቅ ኢትዮጵያ

Sunday, September 21, 2014

መሐመድ ወርዲ- ዘመን የማይሽረው አርቲስት

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
                                                       
----
 እነሆ ነፍስ የሆነውን አርቲስት ልናነሳው ወደድን!! ተወዳጅ፣ ጥበበኛ፣ ባለ ተሰጥኦ ከያኒ!! እውነተኛ የሙዚቃ ቀማሪ! ሱዳን ያፈራችው የምንጊዜም ጌጥ!! ከካይሮ እስከ ዑጋንዳ፣ ከጅቡቲ እስከ ማሊ ምንጊዜም እንደተወደደ ያለ የጥበብ ዋርካ!! ሙሐመድ ወርዲ!!

  “ወርዲ” ማለት ለሱዳኖች ንጉሥ እንደማለት ነው፡፡ እኛም ከአንጋፋ አርቲስቶቻችን ነጥለን አናየውም፡፡ በድሮ ጊዜ ወርዲን በፍቅር ሰምተነዋል፡፡ ዛሬም ወርዲን በመደጋገም እየሰማነው ነው፡፡
*****
ወርዲ ከልቡ ዘፋኝ ነው፡፡ ዘፈኖቹ ከኛ ጋር ከመዛመዳቸው የተነሳ እኛን እኛን ይሸታሉ፡፡ በርካታ ዜማዎቹ እኛ የምንጊዜም ምርጦች አድርገን ለምንወዳቸው ታዋቂ ዘፈኖቻችን መነሻ ለመሆንም በቅተዋል፡፡ ለምሳሌ አንጋፋው ድምጻዊ ጥላሁን ገሠሠ ያዜመውን “አንቺ ከቶ ግድየለሽም”ን ውሰዱት፡፡

አንቺ ከቶ ግድ የለሽም
ስለፍቅር አይገባሽም
ሁሉን ነገር እረስተሽው
ችላ ብለሽ ስለተውሽው
ቻልኩት ፍቅር ለብቻዬ፡፡

አዎን! ዛሬም ድረስ የዚህ ዜማ ተወዳጅነት አልቀነሰም፡፡ ለዚህ ዜማ መሰረቱ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ነው፡፡ ሙሐመድ ወርዲ ዘፈኑን ሲያዜመው እንዲህ ነበር ያለው፡፡

“አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ
ጠል ዐዛበክ ዋ ሱሃዲ
ዋ ሽጃያ አነ ዐዛቢ”

ታዲያ ሙሐመድ ወርዲ የተጫወተውን ዜማ ጋሽ ጥላሁን ወደ አማርኛ የመለሰው እንዲሁ በጋጠወጥነት አይምሰላችሁ፡፡ በነገሩ ውስጥ  የወርዲ ሙሉ ቡራኬ አለበት፡፡ በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመን የካርቱም መንገድ ለኛ አርቲስቶች የውሃ መንገድ ነበረ፡፡ ለሱዳኖችም ከዋዲ ሃልፋ ይልቅ ሸገር ነበር የምትቀርባቸው፡፡ እናም በዚህ ምልልስ መሀል የኛዎቹ አንጋፋዎች (ጥላሁን ገሠሠ፣ ምኒልክ ወስናቸው፣ አለማየሁ እሸቴ፣ ዓሊ ሸቦ፣ ዓሊ ቢራ ወዘተ..) እና የሱዳኖቹ አንጋፋ አርቲስቶች (አሕመድ አል-ሙስጠፋ፣ ሰይድ ኸሊፋ፣ ሙሐመድ ወርዲ፣ አብዱልከሪም አል-ካብሊ፣ አብዱል ዓዚዝ አል-ሙባረክ ወዘተ…) የአንድ ቤተሰብ ልጆች ሆነው ነበር፡፡ ሱዳኖቹ ያዜሙትን የኛዎቹ ወደ አማርኛ፣ ኦሮምኛና ሶማሊኛ እየመለሱ ይጫወቱታል፡፡ የኛንም ዘፈኖች ሱዳኖች በቋንቋቸው እየተረጎሙ ይዘፍኑታል፡፡ አንዳንዴ ዕድል ሲገጥማቸው ሁለቱም ዘፋኞች አንዱን ዜማ በአንድ መድረክ ላይ በየቋንቋቸው ይጫወቱታል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ነው እንግዲህ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ወደ አማርኛ የተመለሰው፡፡

አዎን!! እነ ጋሽ ጥላሁን እንደ አሁኖቹ ዘፋኞች (አንዳንዶቹን ማለቴ ነው) የሱዳንና የፈረንጅ ዜማን ወደ አማርኛ እየገለበጡ “የራሴ ድርሰት ነው”  ብለው ሊያሞኙን አይከጅሉም፡፡ ዋናው አርቲስት ባለበት ጭምር እየዘፈኑ ያሳዩትና “እንዴት ነው! አበላሽቼብህ ይሆን?” በማለት ምክርና እገዛ ይጠይቁታል፡፡ ሱዳናዊው አርቲስትም በሰማው ነገር ላይ የራሱን አስተያየት ይሰጣል፡፡ የኛዎቹም ከሱዳናዊያኑ አርቲስቶች የሚሰጣቸውን አስተያየት ተንተርሰው እጅግ የተሻለ ስራ ይሰሩና ህዝቡን እንካችሁ ይሉታል፡፡ ለዚያም ነበር ስራው የሚዋጣላቸውና ዘመን ተሻጋሪ የሚሆንላቸው፡፡

በዚህ ስሌት ወደኛ ቋንቋዎች ከተቀየሩት ተወዳጅ የሱዳን ዜማዎች መካከል የጥላሁን ገሠሠ “እዩዋት ስትናፍቀኝ” (ሰይድ ኸሊፋና ኢብራሂም አውድ በጋራ ከዘፈኑት ዘፈን የተወሰደ)፣ የአሰፋ አባተ “ሸግዬ ሸጊቱ” (ከአሕመድ አል-ሙስጠፋ “ሐቢቢ በኪቱ” የተወሰደ)፣ የምንሊክ ወስናቸው “ስኳር” (ከአብዱልከሪም አል-ካብሊ “ሱከር” የተወሰደ) የዓሊ ቢራ “ኦፊ ረፋ ቡልታ” (ከሙሐመድ ወርዲ “ያ ኑረል-ዐይን” የተወሰደ) ይጠቀሳሉ፡፡
                                                                          *****
    በርካታ የሀገራችን የሙዚቃ ወዳጆች ከመሐመድ ወርዲ ዜማዎች መካከል ለ“ገመር ቦባ” እና ለ“ቲስዐተ ዐሸር ሰና” (ብዙዎች የሚያውቁት  “ሰበርታ” በሚለው ስም ነው) ልዩ ፍቅር አላቸው፡፡ ሆኖም ሱዳኖች በአንደኛ ደረጃ የሚያሰልፏቸው ሌሎች በርካታ የወርዲ ዜማዎች አሉ፡፡ በተለይም “ሱድፋ”፣ “ቃሲ ቀልበክ”፣ “አልሀወል አወል”፣ “አነ ማ በንሳክ”፣  “አንናስ አል-ጊያፋ”፣ “ሐረምተ አድ-ዱንያ”፣ “ያ ኑረል ዐይን”፣ “ሸተል ዘማ”፣ “አል-ሙርሳል” የመሳሰሉት ከምርጥ የወርዲ ዜማዎች መካከል ይሰለፋሉ፡፡ እኔ በግሌ በጣም ከምወዳቸው የሱዳን ዜማዎች መካከልም አንዱ የሙሐመድ ወርዲ “አዚብኒ ወተፈነን” ነው፡፡

ዐዚብኒ ወዚድ ዐዘባ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚይክ
ዜይመን ሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚክ፡፡
አዚብኒ ወተፈነን ፊ አልዋን ዐዛቢ
ማ ቲምሳሕ ዲሙዒ ማ ቲርሐም ሸባቢ፡፡
ኸሊኒ ፊሹጁኒ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ
ዜይ መንሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ፡፡

ወርዲ በዚህ ዘፈን ለወዳጁ “ልብሽ ጨክኖብኝ ፍቅርሽ አቃጥሎ እየጨረሰኝ ነው፤ መጥተሸ እምባዬን የማታብሺልኝ ልበ-ደረቅ ነሽ” የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው የፈለገው፡፡ ወርዲ ይህንን ዜማ የዛሬ 20 ዓመት ገደማ በአዲስ አበባ ስታዲየም እጅግ ባማረ ሁኔታ የተጫወተው ሲሆን የሀገራችን አድናቂዎችም በጋለ ስሜት ተቀብለውታል ( ቪዲዮውን በሚከተለው ሊንክ ላይ ተመልከቱት፡፡  https://www.youtube.com/watch?v=WkegFEEwjjM&feature=related
                                                                          *****
ታዲያ የወርዲ ፍቅረኛ በ“አዚብኒ-ወተፈነን” ውስጥ እንደተገለጸው በጭካኔዋ አልዘለቀችም፡፡ ወርዲ በጉንጮቹ ላይ የሚያፈሰው እምባ አሳዝኖአት ከፍቅር በረከቱ ልታቀምሰው መጥታለታለች፡፡ ወርዲም ፍቅረኛውን ያገኘበትን ቀን “የቀኖች ሁሉ ረጢብ፣ እጅግ በጣም ገዳም፣ የምኞቴን ያሳካሁበት ቀን መጥቶልኛል” በማለት ገልጾታል፡፡
“ሱድፋ” የሚለውን የሙሐመድ ወርዲን ዘፈን እናውቀው የለ?.. በዚያ ዘፈን ውስጥ ወርዲ ለወዳጁ ያለውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን ከናፈቁት ወዳጅ ጋር መገናኘቱ የሚሰጠውን ደስታ በተዋቡ ቃላት ገልጾታል፡፡ እኔ በበኩሌ እጅግ በጣም የምወደው የወርዲ ዘፈን ይኸው ሱድፋ ነው፡፡ እነሆ የሱድፋን ሙሉ ግጥም ተጋበዙልኝ፡

ሱድፋ… ሱድፋ
ሱድፈ ወ አጅመል ሱድፈነ የውም ላቄታ
አስዓድ የውም የውሚል ሐዬታ
ኑረ ዐይነያ አያም ሓቤታ

ይህ አዝማቹ ነው እንግዲህ፡፡ “ሱድፋ” ማለት አስገራሚ ዕድል ማለት ነው (በእንግሊዝኛ fortunate የሚለው ቃል ይቀርበዋል)፡፡ ተከታዮቹ ግጥሞች የሚከተሉት ናቸው፡፡

አን-ነዘራት በሪዓ ገመም ዘውፍጀል ኸጀል
አልበሰማት ተበዊ ዘይ ኑረል ዐመል
ወጅሂክ ቤን መዛህሪክ ዘይ በድሪ-ክ-ከመል
ወሽሻመክ ኺዴድክ ዘይ ጠዕመል ኹበል
ተስኪር ገልቢ
ወተሽዒል ሑቢ
ኢሽሀክ ረብቢ
አነ በህ ዋ
-----
ማ ቃዲር አጉል ሊክ አን ሑብቢል ከቢር
ወስፉ ዓለይያ ቃሲ መዓዪሽ ፊ-ድ-ደሚር
ቀድረል ከውን ተኩልሉሁ አክበር ቤ ከቲር
ማሊክኒ ሙሐዪይርኒ ሹፍከል ቢል ኣሲር
አስአሊ ቀልቢ
ኢኪኒ ዪቅደር
ኢሽራሕ ሑቢ
አነ ሙሕታር
------
ሱድፈ ዑዩኑ ሻፈክ ሌይሊ ባቂ ይነዊር
ያ አይያም ረቢዒ ዑምሪ መዓኪ አዝሐር
ፊሃ አጥ-ጤይር ይገኒ ሚን አል-ሓኒ ዪዝከር
ቀልቢ ፈራሸ ሐውሊ ወኢንቲ ሸባቢከ አኽደር
ያ መበሒብቢ
ባዕቡድ ሑብቢክ
አለሻን ሑብቢክ
ሩሒ ፈዳክ
*****
ለመሆኑ መሐመድ ወርዲ ማን ነው?

  ሙሉ ስሙ ሙሐመድ ዑስማን ሳሊሕ ወርዲ ነው፡፡ እርሱ ግን “ሙሐመድ ወርዲ” ወይንም በአጭሩ በቤተሰቡ ስም “ወርዲ” ተብሎ ነው የሚታወቀው፡፡ የተወለደው እ.ኤ.አ. በ1932 “ዋዲ ሀልፋ” በተሰኘው ሰሜናዊው የሱዳን ክፍለ ሀገር፣ “ሱወርዳ” በተባለች ትንሽዬ የገጠር መንደር ውስጥ ነው፡፡ እናቱ የኑቢያ ተወላጅ ስትሆን አባቱ ዐረብ ነው፡፡

ወርዲ የሙት ልጅ ነው፡፡ ሁለቱንም ወላጆቹን በልጅነቱ ነው ያጣው፡፡ በመሆኑም በዘመዶቹ ጥበቃ ስር ሆኖ ነው ያደገው፡፡ ትምህርቱን በዋዲ ሀልፋ እና በካርቱም ተከታትሏል፡፡ የተወለደበትን ሀገር እስከ 1956 በመምህርነት ሙያ ካገለገለ በኋላ በወቅቱ ይሞካክራቸው የነበሩት ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ጣቢያ ተቀርጸው በመተላለፋቸው በህዝብ ልብ ውስጥ ገባ፡፡ ያገኘው የሞራል ድጋፍ ማነሳሻ ስለሆነው መምህርነቱን ትቶ የአርቲስትነቱን ጎራ ተቀላቀለ፡፡ ከዚያም ሱዳኖች ከሚያፈቅሯቸው ቁንጮ ዘፋኞቻቸው አንዱ ለመሆን በቃ፡፡
 
    ወርዲ በህይወቱ የተረጋጋ ኑሮ አልኖረም፡፡ በሱዳን የተለዋወጡት መንግሥታት በተቃዋሚነት እየፈረጁት አንገላተውታል፡፡ በመሆኑም ለሀያ ዓመታት ያህል በካይሮና በለንደን ነው የኖረው፡፡ በ2002 ግን ወደ ሀገሩ በክብር ተመልሷል፡፡ ወርዲ በሙዚቃው ዕድገት ላደረገው አስተዋጽኦ ከካርቱም ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸልሟል፡፡ ከልዩ ልዩ የአውሮጳ፣ አፍሪቃና እስያ ሀገራትም ሽልማቶችን ተቀብሏል፡፡
 መሐመድ ወርዲ በመጨረሻዎቹ ዓመታት በደረሰበት የጤና መታወክ ሁለት ኩላሊቶቹ ከጥቅም ውጪ ሆነው ነበር፡፡ ይኸው የኩላሊት ህመም ፋታ ነስቶት በየካቲት ወር 2012 ከዚህች ዓለም አሰናብቶታል፡፡
*****
ከመግቢያዬ እንደገለጽኩት የሀገራችን የሙዚቃ አፍቃሪዎች በጣም የሚወዱት የመሐመድ ወርዲ ዘፈን “ሰበርታ” ነው፡፡ እኔም “ሱድፋ”ን ከሁሉም እንደማስበልጥ ገልጫለሁ፡፡ በሱዳኖች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነው የመሐመድ ወርዲ ዜማ ግን “ገመር ቦባ” ነው፡፡ ሱዳኖች እ.ኤ.አ. በ2000 ባደረጉት ምርጫ “አል-ገመር ቦባ” የተሰኘው ዘፈን የክፍለ ዘመኑ ምርጥ “ነጠላ ዜማ” ተብሎ ተመርጧል፡፡እኔም ገመር ቦባን በድምጽ (ኦድዮ) ልጋብዛችሁና ላብቃ፡፡

ቦባ ዐሌክ ተጊል… ቦባ ዐሌክ ተጊል
አል-ገመር ቦባ ዐሌይክ ተጊል፡፡
አስ-ሰጊሩን አል-ማ-ከቢር
አር-ሪጌበት-ጊዛዛት አሲር
አስኑን በርራጊን የሺል
አል-ዑዩን መሥለል ፈናጂል
ቢንተ-ሱዳን አሲል
ያ ገመር ቦባ ዐሌክ ተጊል፡፡

(ገመር ቦባን በዚህ ሊንክ ላይ ይስሙት https://archive.org/details/MohammedWardi-AlQamarBoeba )
------
አፈንዲ ሙተቂ
መጀመሪያ ታሕሳስ 6/2006 ተጻፈ፡፡
እንደገና ተሻሽሎ መስከረም 9/2007 ተጻፈ፡፡
---
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.
 You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click this link to go to his facebook page.



Monday, September 15, 2014

የኤርትራ ህልም!

ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
----------                                               
ኤርትራ ዛሬ ራሷን የቻለች ሀገር ናት፡፡ ትናንት ግን የኛው አካል ነበረች፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሤ ብልጥ የሆኑ መስሎአቸው ለሁላችንም አስፈላጊ የነበረውን የፌዴሬሽን ፎርሙላ ሰረዙትና ህዝቡን አስቀየሙት፡፡ ደርግ ደግሞ የራሳችንን ህዝብ እንደ ባዕድ እየቆጠረ በመትረየስ አጨደው፡፡ በታንክ ደመሰሰው፡፡ በዚህም የተነሳ ወጣቱ “አደይ ኤሪቲሪያ”ን እየዘመረ ወደ ባርካና ሳህል ነጎደ፡፡ ራሱን አደራጅቶ ጀብሃና ሻዕቢያ ሆኖ መጣ፡፡ ውጤቱም 1983 ላይ ታየ፡፡
  
   የደርግና የኃይለ ሥላሤ መንግሥታት ያደረጓቸው ነገሮች ሲገርሙን በጣም ግራ የሚያጋባው ሶስተኛው መንግሥታችን መጣ፡፡ ይህ የኛ መንግሥት “የተበላሸውን ሁሉ አስተካክለን አብረን መኖር እንችላለን” ብሎ መከራከር ሲገባው ጭራሹኑ “ኤርትራ ካልተገነጠለች ኢትዮጵያ ሰላም አታገኝም” ባይ ሆኖ ተገኘ፡፡ ክፍለ ሀገሩ “ሓርነት ወጣ” ከተባለ በኋላ ደግሞ መንግሥቱ ከሚከተለው ግልጽነት የጎደለው አሰራር የተነሳ በ1990 ሺዎችን ያረገፈ ግዙፍ ጦርነት ተቀሰቀሰ፡፡ ከአንድ ምንጭ የተቀዱ ህዝቦች ተጋደሉ፡፡ እነሆ ዛሬም ድረስ ነገሩ ሳይለይለት በጨለማ ውስጥ ነው ያለነው፡፡
                                                               
   እኛ ግን ተስፋ አንቆርጥም! በአያያዝ ጉድለት የተለየንን ወገናችንን መመለስ እንፈልጋለን፡፡ ህዝቡ ለጊዜው ሪፈረንደም አድርጎ ነጻነቱን ማወጁን እናደግፋለን፡፡ ቢሆንም ህልም አይከለከለምና አንድ ቀን ተቀራርበን በጋራ ስለመስራት እንወያይ ይሆናል ብለን እናልማለን፡፡ የኛ ልጆች ደግሞ በኮንፌዴሬሽን ስለመስራት ያስቡ ይሆናል፡፡ የልጅ ልጆቻችን በፈቃደኝነት ስለመዋሃድ ያስቡ ይሆናል፡፡ በዚያን ጊዜም አሁን የምንመኘው በአንድነት ውብ የመሆን ሚስጢራችን ይመለስልናል ብለን እንመኛለን፡፡ ምን ይታወቃል? ለፈጣሪ የሚሳነው ነገር የለም፡፡

ወገኖቼ ደጉን ነው የተመኘሁት፡፡ በቅን ልቦና በርትተን ከጸለይንና ከኛ የሚጠበቀውን ካደረግን ሁሉንም የሚችለው ፈጣሪ ህልማችንን እውነት ያደርግልናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
-------
   ምን እንደጣለብኝ እንጃ! ያንን ምድር እጅግ ሲበዛ እወደዋለሁ፡፡ እኔ ለተወለድኩበትና አብዛኛውን ዕድሜዬን ለጨረስኩበት የምስራቅ ኢትዮጵያ ክልል ጎረቤት ከሆነችው ሶማሊያ ይልቅ በ1600 ኪ.ሜ. የምትርቀው አስመራ ናት የምትናፍቀኝ፡፡ ስለሶማሊያ የተጻፈ መጽሐፍ ማንበብ ብዙም አይማርከኝም፡፡ ስለ ኤርትራ የተጻፈ መጽሐፍ ካጋጠመኝ ግን ሳላየው አላልፍም (ይህ ግን ሶማሊያን ከመጥላት እንደማይቆጠርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ)፡፡

    ታዲያ በርካቶቻችሁም እንደኔው ትመስሉኛላችሁ፡፡ ለምሳሌ ከ1970ዎቹ ጀምሮ ሲታተም የቆየው የቤኒ አምሩን ወጣት የሚያሳየው ፖስተር ዛሬም ድረስ ከኛ ጋር ተሳስሮ ነው ያለው፡፡ አሁንም ድረስ በበርካታ ስፍራዎች ተለጥፎ አይቼዋለሁ፡፡ በፌስቡክም እርሱን እንደ ፕሮፋይል ፒክቸር የሚጠቀም ኢትዮጵያዊ ሞልቷል፡፡ በሌላ በኩል የኤርትራን ሙዚቃ የሚያዳምጡ ሰዎች በሽ ናቸው፡፡ ደራሲ መሐመድ ሳልማን መቐለ ሄዶ ያየው ነገር ቢያስገርመው “በኤርትራ ሙዚቃ የምትጨፍር ከተማ” የሚል አስደናቂ ወግ ጽፎ እውነቱን አስረድቶናል፡፡ መንግሥታት ቢጣሉ እንኳ ህዝቦች ምንጊዜም እንደሚነፋፈቁ ከዚህ በላይ የሚያስረዳ ዋቢ ያለ አይመስለኝም፡፡
--------
     ማርታ ሀይሉን አስታወሳችኋት? አዎን! ማርታን “ብራ… ነው… ብራ ነው”፤ “አዘዞ”፤ “ሎጋ ..ና እናውጋ” በተሰኙት ዘፈኖቿ እናውቃታለን፡፡ ከማርታ ዘፈኖች ዘወትር ቀልቤን ይገዛ የነበረው ግን የትግርኛ ዜማዋ ነው፡፡ አዝማቹ እንዲህ ይመስለኛል፡፡

 ካብ አስመራ ድንገት ርእዮ
ምጽዋ ገባሁ ልበይ ሕብዮ፡፡

እንተርጉመው እንዴ?… ግድ የለም ማርታ ራሷ እንዲህ እያለች በአማርኛ ተርጉማዋለች፡፡

“ከአስመራ ድንገት አይቼው
ምጽዋ ገባሁ ልቤን ሰጥቼው”፡፡

     አዎን! ትናንት የኛ ናት ስንላት ለነበረችው ኤርትራ ነው እንዲህ የዘመርንላት፡፡ ዛሬም ብንዘምርላት እንከበራለን እንጂ አንወቀስም፡፡ ምክንያቱም በመንግሥት ደረጃ ነው የተለያየነው፡፡ ሁለት ፓስፖርት እንዲኖረን ነው የተደረግነው፡፡ ሁለታችንም ግን አንድ ህዝቦች ነን፡፡ በደምም ሆነ በባህል በጣም የተዋሃድን የአንድ መሬት ብቃዮች ነን፡፡ ሁለታችንም የተዋብን የሴምና የኩሽ ህዝቦች ውቅር ነን፡፡ እንደኛ የሚያምር ህዝብ በትኛውም ዓለም የለም፡፡ የጀበና ቡና፣ ዶሮ ወጥ፣ ድፎ ዳቦ፣ የስጋ ፍትፍት፣ አምባሻ፣ ወዘተ…. ሁለታችን  ዘንድ ብቻ ነው ያለው፡፡
-----
    በርግጥ እላችኋለሁ፡፡  በምንባብና በወሬ እንጂ በአካል የማላውቃት ኤርትራ ትናፍቀኛለች! ያ በታሪክ ምዕራፎች “ምድሪ ባህረ ነጋሽ” እየተባለ ሲጠራ የኖረው ጀግና መሬትና ህዝብ ይናፍቀኛል፡፡ ያ የሰሜኑ በረኛ እያልን ስንመካበት የነበረው ህዝባችን ይናፍቃል፡፡

እውነትም ኤርትራ ! የዳማት ታሪክ ውቅር! የመጠራ አብያተ መንግሥታት ከርስ! የሀውልቲ ፍርስራሾች ቀብር! የአዱሊስና የዙላ ወደቦች መዘክር! የሱዋኪምና የዳህላክ ሱልጣኖች ደብር!

ኤርትራ የአብረሃ ደቦጭ ሀገር! የሞገሥ አስገዶም ሀገር! የዘርዓይ ደረስ ሀገር! የሎሬንዞ ታዕዛዝ ሀገር! የደጃች ሀረጎት ሀገር! በአይበገሬ ጀግንነታቸው ድፍን አፍሪቃን ያኮሩ አርበኞች የበቀሉበት ምድር!

ኤርትራ የበረከት መንግሥተ አብ ሀገር! የፀሐይቱ ባራኪ ሀገር! የአብረሃም አፈወርቂ ሀገር! የአሕመድ ሼኽ ሀገር! የሄለን መለስ ሀገር! የየማነ ባሪያው ሀገር! የሄለን ጳውሎስ ሀገር! በስርቅርቅ ድምጻቸው የሰውን ልብ እየሰረሰሩ የመግባት ሀይል ያላቸው የጥበብ ከዋክብት የወጡበት መንደር!

ኤርትራ የፊያሜታ ጊላይ ሀገር! የስዕላይ በራኺ ሀገር! የኦቦይ ተኽሌ ሀገር! የተክላይ ዘድንግል ሀገር! የሆቴል ፓራዲዞ ሀገር! የዕቁባይ ሲላ ሀገር! የምንወደው ደራሲያችን በዓሉ ግርማ በ“ኦሮማይ” መጽሐፉ እንደ ፊልም ግልጥልጥ አድርጎ እየተረከልን ዝንተ-ዓለም እንድንወዳት ያደረገን የቀይ ኮከብ ትዝታ ወመዘክር!

ኤርትራ የፊዮሪ ሀገር! የሳባ ሀገር! የማርቲና ሀገር! የብርኽቲ ሀገር! ፊያሜታ ጊላይን የመሳሰሉ “ሽኮሪናዎች”ን ያበቀለች ውብ የውቦች እመቤት!
-----
  ኤርትራን ስንጠራ በቅድሚያ ወደ አዕምሮአችን የምትመጣው አስመራ ናት፡፡ የአስመራ ናፍቆት ይገድላል፡፡ አስመሪና፣ አስመሪቲ፣ አቲ ጽብቕቲ!…

ውይ ስታምር! “ቀሽቲ” እኮ ናት፡፡ ያኔ በልጅ አዕምሮአችን በዘምባባ ጥላዋ ተሸክፋ በፖስትካርድ ስትቀርብልን “የኛ ውቢት” እያልን እንመጻደቅባት ነበር፡፡ እንቆቅልሽ ስንጫወትና መልሱ ጠፍቶን “ሀገር ስጠኝ” ስንባል እርሷን ለመስጠት እንሰስት ነበር፡፡ ጠያቂውም የዋዘ ስላልሆነ “አስመራ” ካላልነው ለጠየቀን ጥያቄ ትክክለኛውን መልስ አይነግረንም ነበር፡፡ ከማናውቃቸው “ዋሽንግተን” እና ሮማ ይልቅ አስመራ ነበር የምትበልጥብን፡፡ በትምህርት ቤት መዝሙራችንም እንዲህ እንል ነበር፡፡

ኦኬ ኦኬ ኦኬ ስራ
ሰላም ሰላም ወደ አስመራ
አዲስ አስተማሪ ከጃፓን የመጣ
ማስተማሩን ትቶ በቦክስ የሚማታ
አናግረኝና አናግርሃለሁ
በአሜሪካ ሽጉጥ አዳፍንሃለሁ፡፡
አማርኛም አልችል ትግርኛም አልሰማ
ሰተት ብዬ ልግባ አስመራ ከተማ፡፡

ግጥሙ “አንታራም” የሚሉት የህጻናት ጨዋታ ዓይነት ነው፡፡ ነገር ግን አስመራ ከልባችን እንዳትጠፋ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ዛሬም በልባችን ነግሳለች አስመሪና!
 ----
አስመሪና! እቲ ሽኮሪና! ሰሜናይት ጽብቕቲ! በዓሉ ግርማ ላንቺ ክብር የጻፈው ትዝ ይልሻል? እስቲ እናስታውሰው!

አስመሪና አስመራዬ
ካብ ሐንቲ ንግሥቲ ይበልፅ መልክእኪ
አማአድዬ ክርእየኪ ከሎኹ ኽአ
አብ ኢደይ ዘሎ ነገር ይወድቕ፡፡

(አስመራ አስመራዬ)
(ከአንድ ንግሥት ይበልጣል መልክሽ)
(በሩቅ ሲያይሽ በውበቷ ስለተማረሽ)
በእጄ ያለ ነገር ሳይታወቀኝ ይወድቃል)
------
  ጸጸራት፤ ፎርቶ፣ ሐዝሐዝ፣ አርበእተ አስመራ፣ እምባጋሊያኖ፣ ኮምቢሽታቶ፣ አዲ ጓእዳድ፣ ቃኘው፣ ማይተመናይ፣ ሰምበላይ፣ ጎዳይፍ፣  ገጀረት፣ ወዘተ… በጽሑፍ የማውቃቸው የአስመራ ሰፈሮች ናቸው፡፡ አንድ ቀን በሆነልኝና ባየኋቸው እያልኩ አልማሁ፡፡  እነዚህ አስገራሚ የአስመሪና ሰፈሮች ብዙ ባለታሪኮችን አብቅለዋል፡፡ ብዙዎች ገድላቸው እየተደጋገመ ሲነገርላቸው እሰማለሁ፤ አነባለሁ፡፡ ለኛ ቅርብ የነበረ አንድ ውድ ልጅ እየተረሳ በመሆኑ ግን አዝኛለሁ፡፡
 
     አማኑኤል እያሱ ይባላል! አስታወሳችሁት አይደል? አዎን! አማኑኤል በኛ ዕድሜ ዘመን ኢትዮጵያ ዋንጫ መብላት እንደምትችል ያስመሰከረው የታላቁ የ1980 የእግር ኳስ ቡድናችን ቋሚ ተሰላፊ ነበረ፡፡ የማሊያ ቁጥሩ 2 ይመስለኛል፡፡ አማኑኤል የያኔው ቡድናችን ባደረጋቸው ሁሉም ጨዋታዎች ተሰልፏል፡፡ ቡድኑ ዋንጫውን ሲበላም ከጓደኞቹ ጋር ቤተመንግሥት ድረስ ተጋብዞ ተሸልሟል፡፡ አማኑኤልን ያስገኘው ከዚያ ዘመን ዝነኛ ቡድኖቻችን መካከል አንዱ የነበረው የኤርትራ ጫማ ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን የኤርትራ አንደኛ ዲቪዚዮን ዋንጫን በተደጋጋሚ ያሸነፈ ነው፡፡
 
    አማኑኤል እያሱ በኢትዮጵያ ትቅደም አንደኛ ደረጃ ዋንጫም ለኤርትራ ክፍለ ሀገር ምርጥ ቡድንም ተሰልፎ ተጫውቷል፡፡ ባልሳሳት የ1981 የኢትዮጵያ ዋንጫን ያሸነፈው እነ አማኑኤል የነበሩበት የኤርትራ ክፍለ ሀገር ቡድን ነው፡፡ የአማኑኤል እያሱን ወሬ ለመጨረሻ ጊዜ ያነበብኩት በ1988 ለወዳጅነት ጨዋታ አዲስ አበባ መምጣቱን በማስመልከት በርካታ የግል ጋዜጦች ቃለ-መጠይቅ ባደረጉለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ መረጃው የለኝም፡፡ እስቲ የአስመራ ልጆች ወሬው ካላችሁ ስለአማኑኤል እያሱ አንድ ነገር በሉን፡፡
-----------------
አሁን ወደ ምዕራብ ኤርትራ ተሻግረናል! ባርካና ጋሽ የሚባሉት ቆላማ አውራጃዎች እዚህ ነው ያሉት፡፡ አቆርዳት፣ ተሰነይ፣ አሊጊደር፣ ኡምሐጀር፣ ባሬንቱ የተሰኙት ከተሞች በቆላው ምድር ውስጥ ተዘርግተዋል፡፡ ኩናማ፣ ናራ እና ቤጃ የሚባሉት ብሄረሰቦች እዚህ ነው የሚኖሩት፡፡ የአካባቢው ዋነኛው ህዝብ ግን ለኛ በጣም ቅርብ የሆነውን ሳቂታውን የቤኒ አምር ወጣት ያስገኘው የትግረ ህዝብ ነው፡፡

  የትግረ ህዝብ በውስጡ በርካታ ጎሳዎች አሉት፡፡ ከሁሉም የሚበረክተው ግን የቤኒ አምር ጎሳ ነው፡፡ ህዝቡ የሚነጋገርበት የትግረ ቋንቋ ከሴማዊ ቤተሰብ ነው የሚመደበው፡፡ ለዚህ ቋንቋ በጣም የሚቀርበው በደጋው ኤርትራና በኛዋ የትግራይ ክልል የሚነገረው ትግርኛ ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ቋንቋዎች ከጥንታዊው የግዕዝ ቋንቋ ነው የተወለዱት፡፡ የትግረ ቋንቋን ከ35 በመቶ የማያንሰው የኤርትራ ህዝብ ይናገረዋል፡፡ “ትግረ” ከኤርትራ ሌላ በሱዳንም (ከሰላ አካባቢ) በስፋት ይነገራል፡፡

ትግረና ትግርኛ በጣም ከመመሳሰላቸው የተነሳ እንግዳ ለሆነ ሰው አንድ ዓይነት ቋንቋዎች ሊመስሉት ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም ለትግርኛ ተናጋሪዎች የትግረ ቋንቋን መልመድ በጣም ቀላል ነው ይባላል፡፡ የትግረ ተናጋሪም ትግርኛን በቶሎ መልመድ ይቀለዋል፡፡ በመሆኑም ከጠቅላላው የኤርትራ ህዝብ 50% የሚሆነው ሁለቱንም ቋንቋዎች መናገር ይችላል (ይህ ቁጥር ትግርኛ ብቻ የሚናገሩትን፣ ወይንም “ትግረ” ብቻ የሚናገሩትን አይጨምርም)፡፡

 ምዕራባዊው ቆላ ኤርትራዊያን በጣም የሚያደንቋቸውን እንደ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ፣ ሙሐመድ ኢድሪስ እና ኢድሪስ ገላውዴዎስን ያፈራ መሬት ነው፡፡ በዚህ ሰሞን ልቤን ያሸፈተው የትግረ ልጅ ግን “አሕመድ ሼክ” ነው፡፡ አሕመድ ሼክን አወቃችሁት አይደል? አዎን! “ባቡሬይ”፣ “ኢላ ሰርጎ” ወዘተ.. እያለ በማይጠገበው የትግረ ምት የሚያዜመው ተወዳጅ ድምጻዊ ነው፡፡ አንድ ኤርትራዊ ወዳጃችን “ኤላ ሰርጎ”ን ሲፈታልን `ከጀርባው ፌሎሶፊ አለው” ነው ያለኝ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡
 
   የትግረ ሴት ለምትወደው አንድ ሰው (ለባሏ) እንጂ ለማንም ጸጉሯን አትገልጠውም፡፡ ስለዚህ ጉብሊቷን ልጅ የወደደው አሕመድ ሼክ በተዋቡ ግጥሞች እያወደሳት ዘፈነላትና ፍቅሩ ልቧ ውስጥ ዘልቆ መግባቱን ለማረጋገጥ ጸጉሯን ማየት ጀመረ፡፡ እርሷም ግጥሞቹን ከሰማችለት በኋላ ጸጉሯን ገልጣ አሳየችው፡፡ ድል አድራጊው ወዲ ሼክም ይዟት በረረ፡፡ “ኤላ ሰርጎ! ኤላ ሰርጎ” እያለ ነጎደ!
------
ሰሜን ኤርትራ!

ተወዳጇ የከረን ከተማ እዚህ ነው ያለችው! የሀረርጌዋ የድሬ ዳዋ ከተማ መንትያ እህት የምትመስለው ውቢቷ የሰሜን ፈርጥ! በቪዲዮ አይቻት ውበቷን አደነቅኩላት! አበቦቹ! ቤቶቹ! መንገዶቹ ሁሉም ውብ ናቸው፡፡ ከትግራይ የተገኘው ዝነኛው ብርሃነ ሃይለ አንድ ላይ በነበርነበት ዘመን ለከረኗ ጉብል እንዲህ ብሎላታል፡፡

ሸው በሊ ብለነይ ብለነይ
ዝለሊ ብለነይ ብለነይ
አሊሊ ብለነይ ብለነይ
አቲ ጓል ከረነይ ብለነይ

አዎን! ቢለን ከከረን ከተማ ጋር ስሙ የሚጠቀስ ብሄረሰብ ነው፡፡ ቋንቋው ከኛው የአገው ቋንቋ ጋር አንድ ዐይነት ነው፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ነው አንባቢ ሊመራመር የሚገባው፡፡ በወሎና በጎጃም የሚኖረው አገው ምን ሊያደርግ እዚያ ሄደ?… መቼ ነው እዚያ የሄደው?… መላምት ከመዘብዘብ በስተቀር ማንም ሰው ይህንን እንቆቅልሽ በሚያመረቃ ሁኔታ ሊፈታው አልቻለም፡፡ ኤርትራና እኛ አንድ ነን የሚያሰኘኝ እንዲህ ዓይነት ተጨባጭ ማስረጃ ስላለን ነው፡፡
  
  ቢለን ውብ ባህል ያለው ህዝብ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ሴቶቹ ካገቡ በኋላ ጸጉራቸውን መሰተር ግድ ነው፡፡ ህዝቡ የቢለን ቋንቋ ተናጋሪ ቢሆንም የትግረ ቋንቋንም ይጠቀማል፡፡ ትግርኛም በስፋት ይነገራል፡፡ በጣም ታዋቂ የሆነው የቢለን ተወላጅ “ዑመር እዛዝ” ነው፡፡ የጀብሃ ጦር ከመፍረክረኩ በፊት የሁለተኛው ዞን አዛዥ እንደነበረ ከዚህ በፊት ጽፌ ነበር፡፡

  ከከረን ሽቅብ ወደ ሰሜን ስናመራ ታሪካዊቷ አፋቤት አለች፡፡ ጄኔራል ታሪኩ አይኔ የሚመራው ናደው እዝ እዚህ ነበር የሰፈረው፡፡ የቀይ ኮከብ ዘመቻ ዋና አምባም ይህ ነበር፡፡ ከአፋቤት ወደ ሰሜን ስንበር ንዳዳማውና አስቸጋሪው የሳህል መሬት አለ፡፡ በሳህል እምብርት ላይ የኤርትራ ገንዘብ መጠሪያ ለመሆን የበቃችው “ናቅፋ” አለች፡፡ በዓሉ ግርማ እንደተረከልን ከሆነ ሳህል ማለት እሳት ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ይኖሩበታል፡፡ ከብቶች ይሰማሩበታል፡፡ ተክልም ይበቅልበታል፡፡ እዚህ አካባቢ በብዛት የሚኖረው ህዝብ “ረሺዳ” ይባላል (አንዳንዶች “ራሻይዳ” ይሉታል፤ ስህተት ነው፤ ትክክለኛው አጠራር “ረሺዳ” ነው)፡፡

  የ“ረሺዳ” ህዝብ ከሌላው የኤርትራ ህዝብ የሚለይበት በርካታ ነገሮች አሉት፡፡ ለምሳሌ ይህ ህዝብ ከሳዑዲ ዐረቢያ ተነስቶ ወደ ኤርትራ የገባው በቅርብ ዘመን (በ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ) ነው፡፡ በዚያ ወቅት የአሁኗ ሳዑዲ ዐረቢያ አልነበረችም፡፡ ሀገሩ ሁሉ በጎሳዎች የተከፋፈለ በረሃማ ምድር ነበር፡፡ ከነዚህ ጎሳዎች አንዱ አል-ረሺድ ይባላል፡፡ ይህ የአል-ረሺድ ህዝብ የአካባቢው የበላይ እንዲሆን በኦቶማን ቱርክ ተወሰነ፡፡ አብዛኛው ህዝብም ለነርሱ አደረ፡፡ “አል-ሱዑድ” የሚባለው ቤተሰብ ግን “አሻፈረኝ” አለ፡፡ “ራሴ በረሃውን ጠቅልዬ መግዛት ስችል ለምን በአል-ረሺድ ጎሳ የበላይነት አድራለሁ” በማለት አንገራገረ፡፡ በሁለቱ መካከል ጠብ ተነሳ፡፡ በመጀመሪያው ላይ የአል-ረሺድ ጎሳ አሸነፈ፡፡ አል-ሱዑዲዎች ወደ ኢራቅ ሸሹ፡፡

   ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን የአል-ሱዑድ ቤተሰብ በእንግሊዞች ደጋፊነት ራሱን አጠናክሮ መጣ፡፡ በአል-ረሺድ ጎሳ ላይም ድልን ተቀዳጀ፡፡ በዚህም የተነሳ የዐረቢያ በረሃ ለአል-ረሺድ ጎሳ አባላት ሲኦል ሆነ፡፡ ረሺዳዎች እየተያዙ በጅምላ ታረዱ፡፡ ንብረታቸው ተዘረፈ፡፡ በፊት ይረዳቸው የነበረው የቱርኮች መንግሥት በራሱ ችግር በመወጠሩ ምንም ሊያደርግላቸው አልቻለም፡፡ በመሆኑም ከእልቂቱ ለመዳን ሲሉ ባህር እያቋረጡ ወደ አፍሪቃ ምድር ተሰደዱ፡፡ በሱዳንና በኤርትራ መኖሪያቸውን ቀለሱ፡፡

እንግዲህ ረሺዳዎች ከዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሸሽ ወደ ኤርትራ የመጡ ተፈናቃዮች ናቸው ማለት ነው፡፡ በኤርትራ ውስጥ ንጹህ የዐረብ ዝሪያ የሚባሉት እነርሱ ናቸው፡፡ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸውም ዐረብኛ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ለአካለ መጠን የደረሰች ማንኛዋም ሴት ፊቷንም ሆነ ጸጉሯን መሸፈን ግዴታዋ ነው፡፡ በዓሉ ግርማ በኦሮማይ ውስጥ ሲተርክልን “ማንኛውም የረሺዳ ባል የሚስቱን ፊት ገልጦ የሚያይበትን ሰው አይፈልግም” በማለት የተናገረውም የባህላቸው አንድ አካል ነው፡፡
-------
አሁን ወደ ምስራቅ ኤርትራ ተሻግረናል፡፡ ብርኽቲ የሆነችው ምጽዋ እዚህ ነው ያለችው፡፡ ብርሃነ ሃይለ “ሸው በሊ ብለነይ” የተሰኘውን ዘፈን ሲቀጥል ምጽዋን እንዲህ ይላታል፡፡

“አብ ዋሊድ ማሳዋ
ኩለ ሊየን ሒልዋ”
 
   ትርጉሙን በትክክል ባላውቀውም “የምጽዋ ልጆች ሁሉም ጣፋጭ ናቸው” የሚል መልዕክት እንዳዘለ ይገባኛል፡፡ የምጽዋ ልጆች ቆንጆ ናቸው ተብሎ እየተደጋገመ ተነግሮላቸዋል፡፡ ከወደብ ከተማ የተገኙ በመሆናቸው ዓለም አቀፍ ስልጣኔና ልዩ ልዩ ባህሎች በነርሱ ላይ ሲነፍስ ይታያል፡፡

  ምጽዋ በጣም ውብ ናት፡፡ በተለይም ኪነ-ህንጻዋ ብዙ ተብሎለታል፡፡ ከዑስማናዊያን ቱርኮች ዘመን ጀምሮ ብዙ ገዥዎች ሲፈራረቁባት የነበረች መሆኗ በከተማዋ የሚታየውን ኪነ-ህንጻ እንዳሳመረው ምሁራን ያስረዳሉ፡፡
  
ኤርትራዊያን ምጽዋን ይወዷታል፡፡ እኛም እንወዳታለን፡፡ ነገር ግን ወደዚያ ለመድረስ የሚሻ ሰው እንደ እሳት የሚፋጀውን ሙቀቷን መቻል አለበት-ከተማዋ በዓለም ላይ ከፍተኛ ሙቀት ካላቸው ስፍራቸው አንዷ ናትና፡፡ የዚህች ከተማ ህዝብ ኑሮውን ከአየር ጸባዩ ጋር እንዲጣጣም አድርጎ ቀይሶታል፡፡ በመሆኑም አብዛኛው የንግድ እንቅስቃሴ የሚከናወነው ከምሽት እስከ እኩለ ሌሊት ባለው ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ከተማዋ ለዘወትር እንደጋለች አትቀርም፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ሙቀቱ ጋብ ይልና ጤናማው አየር ይነፍስባታል፡፡ ይህም ከጥር-የካቲት ባለው ጊዜ እና በሀምሌ ወር ነው፡፡ በነዚህ ወራት ከተማዋን የሚጎበኘው ቱሪስት በጣም ይጨምራል፡፡ በቀድሞው ዘመን ቀዳማዊ ኃይለሥላሤም ከተማዋን ለመጎብኘት የሚመጡት በነዚህ ወራት ነው (እርሳቸው ያሰሩት ቤተ-መንግሥት እስከ አሁን ድረስ አለ)፡፡

     ምጽዋ በወደብነት አገልግሎት መስጠት የጀመረችበት ዘመን በትክክል አይታወቅም፡፡ የታሪክ ምሁራን እንደሚሉት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በአካባቢው ከተማ ቀመስ ሰፈራ ነበር፡፡ ይሁንና እስከ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እንደ ወደብ ሲያገለግሉ የነበሩት ከምጽዋ አጠገብ የነበሩት ጥንታዊያኑ “ዙላ” እና “አዱሊስ” ነበሩ፡፡ የምጽዋ ተፈላጊነት ጉልህ ሆኖ የተከሰተው የባህር መደቡ በ1508 በዑሥማናዊያን ቱርኮች (Ottoman Turks) በተያዘበት ወቅት ነው፡፡ ከቱርኮቹ በማስከተልም ግብጾችና የኢጣሊያ ወራሪዎች ተፈራርቀውባታል፡፡

   ኢትዮጵያና ኤርትራ በፌዴሬሽን ከተዋሃዱ በኋላ ምጽዋ ከፍተኛ እመርታ ማሳየት ጀምራ ነበር፡፡ ከ1970ዎቹ መግቢያ ጀምሮ ግን የጦርነት ቀጣና ሆነች፡፡ የሻዕቢያ ሀይሎችና የኢትዮጵያ ሰራዊት ከፍተኛ እልቂት የተፈጸመባቸውን ጦርነቶች አካሂደውባታል፡፡ በተለይም በ1982 (እ.ኤ.አ. 1990) በተካሄደው ጦርነት ከሁለቱም ወገን በአስር ሺህ የሚቆጠር ሰራዊት መርገፉን ሁኔታውን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖችና የዐይን ምስክሮች ገልጸዋል (የሀምሳ አለቃ ታደሰ ቴሌ ሳልባኖን “አይ ምጽዋ” አስታውሱት)፡፡ የቀድሞው የኢትዮጵያ መሪ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያምም “ለከፍተኛ ሽንፈትና ኪሳራ የዳረገን ውድቀት ያጋጠመን በምጽዋ ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

የድሮው ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) የአሁኑ “ህዝባዊ ግንባር ንዴሞክራሲን ንፍትሒን” (ህግዴፍ) ምጽዋን የተቆጣጠረበትን ዘመቻ “ኦፕሬሽን ፈንቅል” በማለት ይጠራዋል፡፡ ምጽዋ የተያዘችበት ዕለትም (የካቲት 20) በየዓመቱ ይከበራል፡፡ በርካታ ህዝብ ወደ ምጽዋ ከሚጎርፉባቸው ዕለታት መካከልም አንዱ ይህ “የኦፕሬሽን ፈንቅል” መታሰቢያ የሚከበርበት ቀን ነው፡፡

ምጽዋ የብዙ ህዝቦች መኖሪያ ናት፡፡ ዋነኞቹ ነዋሪዎች ግን የአሳውርታ፣ ሳሆ፤ እና አፋር ብሄረሰቦች ተወላጆች ናቸው፡፡ በከተማዋ በዋናነት የሚነገረው ቋንቋ ዐረብኛ ነው፡፡ የሻዕቢያ መስራች ተብሎ የሚታወቀው ዑሥማን ሳልህ ሳቤ የተወለደው በምጽዋ አጠገብ ካለችው ሂርጊጎ የተባለች አነስተኛ መንደር ነው፡፡ ኢብራሂም አፋ፣ ረመዳን መሐመድ ኑር እና ዓሊ ሰዒድ አብደላን የመሳሰሉት የህግሓኤ (ሻዕቢያ) እውቅ ኮማንደሮችም የምጽዋ ልጆች ናቸው፡፡ 

  ከምጽዋ ወደብ ዝቅ ብሎ ጥንታዊቷ የአዱሊስ ወደብ ትገኛለች፡፡ ይህች የወደብ ከተማ ከክርስቶስ ልደት በፊት ጀምሮ የተጓዦች መግቢያና መውጪያ ነበረች፡፡ የጥንቱ ሮማዊያንና ግሪኮችም በደንብ ያውቋታል፡፡ አጼ ካሌብ ወደ ደቡብ ዐረቢያ ሲዘምት ወታደሮቹን በመርከብ ያስጫነው ከዚህች የወደብ ከተማ ነው፡፡ በሀገራቸው ከፍተኛ በደል ያጋጠማቸው የነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ተከታዮች ከጥቃቱ ለመሸሽ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ በአዱሊስ በኩል ነበር ያለፉት፡፡ ሌላም ብዙ ታሪክ ተስተናግዶአል-በአዱሊስ፡፡
---------
ከምጽዋ ወደ መሀል ኤርትራ ለመጓዝ መንገዱን ስንጀምር በቅድሚያ የምናገኘው የሳሆ ህዝብን ነው፡፡ ይህ ህዝብ በስተደቡብ በኩል ከሚጎራበተው የአፋር ህዝብ ጋር ተመሳሳይ የሆነ የኢኮኖሚ መሰረት አለው፡፡ ሁለቱም በከብት እርባታ ነው የሚተዳደሩት፡፡ ሁለቱም ኩሻዊ ቋንቋ ነው የሚናገሩት፡፡ በአለባበስ ግን ሳሆን ከአፋር በቀላሉ መለየት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ የሳሆ ተወላጅ የሆነ ሰው አፋሮች የሚታጠቁትን “ጊሌ” የሚባለውን ረጅም ቢላዋ አይታጠቅም፡፡ የሳሆ ሰው የሚያሸርጠው ሽርጥም ከአፋር ሽርጥ ረዘም ይላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሳሆ ብዙ ጊዜ ከእጁ ጦር አያጣም፡፡ ታዲያ የሳሆ ቋንቋ በትግራይ ክልል ምስራቃዊ ዞን የሚኖረው የኢሮብ ህዝብ ከሚናገረው ቋንቋ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ኢሮብና ሳሆ የሚለያዩት በሚከተሉት እምነትና በኢኮኖሚ መሰረታቸው ነው፡፡ ሳሆ ሙሉ በሙሉ የእስልምና እምነት ተከታይ ነው፡፡ ኢሮብ ግን በአብዛኛው ክርስቲያን ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ የሚበዙትም ካቶሊኮች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል የኢሮብ ህዝብ አራሽ ገበሬ ይበዛዋል፡፡ ከላይ እንደተገለጸው የሳሆ ህዝብ በከብት እርባታ ነው የሚተዳደረው፡፡

ሳሆን ስናልፍ ደግሞ ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ በስፋት የሚኖርባቸውን የአከለ ጉዛይ፣ ሰራዬ እና ሐማሴን አውራጃዎችን እናገኛቸዋለን፡፡ በኤርትራ ውስጥ ካሉት ብሄረሰቦች መካከል ብዙ ቁጥር ያለው (50 % የሚሆነው) ይህ ትግርኛ ተናጋሪ ህዝብ ነው፡፡ ይህ ህዝብ በባህሉም ሆነ በቋንቋው ከኛው የትግራይ ህዝብ ጋር ይመሳሰላል፡፡ ህዝቡ በአብዛኛው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ መሆኑም ከትግራይ ህዝብ ጋር ያመሳስለዋል፡፡ ይሁንና ቋንቋው ባለፉት በርካታ ዘመናት ከጣሊያንኛ፣ ከዐረብኛ እና ከትግረ ቋንቋዎች ጋር በመወራረሱ በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚነገረው ትግርኛ የተለየ ዘዬ ሊሆን በቅቷል፡፡

አጅግ በርካታ የሆኑ የኤርትራ ከተሞች ያሉት በዚህ ክልል ነው፡፡ ጊንዳዕ፣ ሐሙሲት፣ ሰገነይቲ፣ ደቀምሐረ፣ መንደፈራ (አዲ ዑግሪ)፣ አዲኳላ፣ ሰንዓፈ፣ ደባሩዋ ወዘተ… እዚህ ነው የሚገኙት፡፡ በመሀከላቸው ደግሞ አስመራ ጉብ ብላ ትታያለች፡፡ ከከተሞቹ መካከል የሚበዙት በጣሊያን ዘመን የተቆረቆሩ ናቸው፡፡ በሰራዬና በአከለ ጉዛይ አውራጃ ውስጥ ግን የጥንቱ የአክሱም ዘመነ መንግሥት ታዋቂ ከተሞች የነበሩትን እንደ “ሀውልቲ” እና “መጠራ” የመሳሰሉ መንደሮችን ማግኘት ይቻላል፡፡ በነዚህ ከተሞች ፍርስራሽ ስር ገና ያልተነካ ድልብ የአርኪዮሎጂ ሀብት አለ፡፡ ወደፊት ቆፈረን የምናወጣቸውን ማቴሪያሎች የህዝቦቻችንን አንድነት የሚመሰክሩ ቋሚ ቅርሶች አድርገን ልጆቻችንን እናስተምራለን ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ 
-------
ኤርትራን በኢትኖግራፊ ጉዞ እንዲህ ቃኝተናታል፡፡ ነገር ግን በዚሁ አናበቃም፡፡ ወደፊትም በተሻለ ዝግጅት ተመልሰን እንዘይራታለን፡፡ ለአሁኑ በዚሁ ይብቃን!!
ሰላም!!
-----
አፈንዲ ሙተቂ
ነሐሴ 30/2006
-----
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his facebook page. Just click this link