Wednesday, December 10, 2014

ሃየሎም አርኣያን በጨረፍታ




(አፈንዲ ሙተቂ)
------
በኢትዮጵያ የታሪክ ሂደት የተፈጠሩ የፖለቲካ ድርጅቶችና ሽምቅ ተዋጊ ቡድኖች በትግል ዘመናቸው ከወደቁ ሰማዕቶቻቸው ሁሉ አግዝፈው የሚመለከቱት አንዳንድ ጀግና አላቸው፡፡ ለምሳሌ የተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ ( ጀብሃ) ትልቁ ሰማዕት “ዑመር እዛዝ” ይባላል፡፡ የህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) ታላቅ ሰማዕት ደግሞ “ኢብራሂም አፋ” ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ) ትልቁ ሰማዕት “ተስፋዬ ደበሳይ” ነው፡፡ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) “ታላቁ ሰማዕት” ኤሌሞ ቂልጡ ይባላል፡፡ የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አባላት በበኩላቸው እንደ ትልቁ ሰማዕት የሚያዩት ሃየሎም አርኣያን ነው፡፡

Hayelom Ar'aya


  ታዲያ ሃየሎም ከሌሎቹ ሰማዕታት የሚለይበት አንድ ጠባይ አለ፡፡ ይህም በጀግንነቱ በህወሓት ብቻ ሳይሆን የህወሓት ቀንደኛ ጠላት በሚባሉ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር የሚወደስ መሆኑ ነው፡፡ እርግጥ ስለሃየሎም ጀግንነት በስፋት መጻፍ የጀመረው እርሱ ከተገደለ በኋላ ነው፡፡ ሆኖም ሃየሎም በህይወት እያለ እንኳ ስለጀግንነቱ ሲሰጡ የነበሩ የምስክርነት ቃሎችን በልዩ ልዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ አንብበናል፡፡ ለምሳሌ የቀድሞው የኢህዴን ሊቀመንበር ያሬድ ጥበቡ (ጌታቸው ጀቤሳ) “መስታወት” በተሰኘ መጽሔት ላይ በጻፉት አንድ ጽሑፍ ሁሉንም የኢህአዴግ መሪዎች በፈሪነት ከፈረጇቸው በኋላ ሃየሎም አርኣያን ብቻ በጀግንነት አወድሰዋል፡፡ በኤርትራና በትግራይ ሲዋጉ የነበሩ የደርግ የጦር መኮንኖችም በተለያዩ መጽሔቶች ስለሃየሎም ኣርኣያ ጀግንነት ሲያወሱ ነበር፡፡

 በመሆኑም በሃየሎም የጦር ሜዳ ጀግንነትና በወታደራዊ ጥበብ አዋቂነቱ ላይ ጥርጣሬ የሚቀርብ አይመስለኝም፡፡ ሆኖም የሃየሎምን አሟሟት ያየ ሰው “ሰውዬው ሰማዕት ነው ሊባል ይችላልን?” የሚል ጥያቄ ሊያቀርብ ይችላል፡፡ ምክንያቱም በተለምዶ ሰማዕታት የሚባሉት በትግሉ ሂደት ሲዋጉ የወደቁ ሰዎች ናቸውና፡፡ ሃየሎም የተገደለው ግን የትጥቅ ትግሉ ካበቃ ከአራት ዓመታት በኋላ በተከሰተ ጸብ ነው፡፡

 የኢህአዴግ ሰዎች “ሃየሎም በሰላም ጊዜ በሚደረገው ትግል መሃል የወደቀ ጓዳችን በመሆኑ ሰማዕት ነው” እንደሚሉ ይታወቃል፡፡ ከሰማዕታቱ መካከል የተናጥል ሃውልት ያቆሙትም ለርሱም ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ወገኖችስ በሰማእትነቱ ላይ ምን ይላሉ? በጉዳዩ ላይ ያላቸውን አቋም እንዲነግሩን እንጠብቃለን፡፡
*****
ሃየሎም አርኣያ ህወሓት (በኋላም ኢህአዴግ) ባካሄዳቸው ዋና ዋና ዘመቻዎች ላይ የመሪነት ሚና ነበረው፡፡ ከነዚያ ዘመቻዎች መካከል ከስሙ ጋር ተቆራኝቶ የቀረው በየካቲት ወር 1978 የተካሄደው “ኦፕሬሽን አግአዚ” ነው፡፡ ይህንን ኦፕሬሽን የሚመለከት ጽሑፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነበብኩት በሚያዚያ 1985 በታተመው “እፎይታ” መጽሔት ላይ ነው፡፡ ተራኪው ደግሞ ሃየሎም አርኣያ ራሱ ነበረ፡፡

 ታዲያ ጽሑፉ በጣም የሚያስደምም በመሆኑ ብዙዎች ታሪኩን በመጠራጠር “ሰውዬው የተናገረው ልብወለድ ነው እንጂ እውነተኛ ነገር  አይደለም” ብለው ነበር፡፡ በዘመኑ ከኢህአዴግ በታቃራኒነት የተሰለፉት የደርግ ከፍተኛ ባለስልጣናት “ኦፕሬሽን አግአዚ” በትክክል የተፈጸመ ዘመቻ መሆኑን መናገር ሲጀምሩ ግን የሃየሎም ትረካ እውነተኛት ሊረጋገጥ በቅቷል፡፡ በዚህ ረገድ የመጀመሪያውን ምስክርነት የሰጡት ጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም እራሳቸው ናቸው (በ1994 የታተመውን የሌ/ኮ/ መንግሥቱ ኃይለማሪያም ትዝታዎችን ያስታውሱ)፡፡ በማስከተልም “ነበር” የተሰኘውን ተወዳጅ መጽሐፍ የጻፉት ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ) “ኦፕሬሽን አግአዚ” በትክክል መፈጸሙን አረጋግጠዋል፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡

   “ኦፕሬሽን አግአዚ” በመቀሌ እስር ቤት ታስረው የነበሩ ከሶስት ሺህ የሚበልጡ የህወሐት ታጋዮችንና ደጋፊዎችን የማስለቀቅ ተልዕኮ ነበረው (ኦፕሬሽኑ የተሰየመለት “አግዓዚ” የሚባለው ታጋይ ከህወሐት መስራቾች አንዱ ነው፤ “አግዓዚ” የትግል ስሙ ሲሆን እውነተኛ ስሙ “ዘርዑ ገሠሠ” ነበር)፡፡ እንደ ጄኔራል ሃየሎም አርኣያ አገላለጽ ኦፕሬሽኑን ለማካሄድ የሚያስፈልገው ቅድመ ዝግጅት ለስድስት ወራት ያህል ተካሄዷል፡፡ በኦፕሬሽኑ የሚሳተፉ ኮማንዲስቶች በሚስጢር ነው የሰለጠኑት፡፡ ሆኖም ሰልጣኞቹ በስልጠናው ላይ በነበሩበት ወቅት ስለኦፕሬሽኑ ምንም መረጃ አልነበራቸውም፡፡ በመሆኑም እነዚያ ሰልጣኞች ለስልጠናው ወደተዘጋጁት የአሸዋ ቤቶች በሚወሰዱበት ጊዜ ከፊሉ “ይህ የመቀሌ ቤተ መንግሥት ነው” ይሉ የነበረ ሲሆን የተቀሩት ደግሞ “አይ! የአየር ማረፊያው ነው” እያሉ ልዩ ልዩ መላምቶችን ይደረድሩ ነበር፡፡

  “ኦፕሬሽን አግአዚ” በታቀደለት ጊዜ ተካሄደ፡፡ የህወሓት አሸማቂዎችም ማንም ባልጠበቀው ሁኔታ ወደ መቀሌ እስር ቤት በመግባት የሚፈልጓቸውን ታሳሪዎች በሙሉ አስለቀቁ፡፡ በማግስቱ ወሬው በአዲስ አበባ ሲሰማ በሊቀመንበር መንግሥቱና በጦር ጄኔራሎቻቸው ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ ተቀሰቀሰ፡፡ መቀሌ ያሉ የጦር መሪዎችም ለአስቸኳይ ግምገማ ተጠሩ፡፡ በግምገማው ማብቂያም “ለኦፕሬሽኑ መሳካት ትልቁን ሚና የተጫወተው በአካባቢው የነበረው አብዮታዊ ጦር አዛዥ የነበረው ብ/ጄኔራል ታሪኩ ዐይኔ ያሳየው እንዝህላልነት ነው” ተባለ፡፡

  የደርግ መንግሥት ባለስልጣናት ታሪኩን ሲጽፉ “የህወሓት ጦር በእስር ቤቱ ላይ ወረራ በፈጸመበት ወቅት የእስር ቤቱ ሃላፊ ወደ ጄኔራል ታሪኩ በመደወል “በወንበዴ ተወርሬአለው፤ ባሉኝ ጠባቂዎች መከላከል ስለማልችል ረዳት ጦር በአስቸኳይ ይላኩልኝ” በማለት ሲጠይቀው ጄኔራል ታሪኩ “እኔ መደበኛ ወታደር እንጂ የእስር ቤት ጠባቂ ዘበኛ አይደለሁም” የሚል የሹፈት መልስ ሰጥቶት ከቤቱ ገብቶ ተኝቷል፤ የአንድ አብታዊ ጦር ዋና ዓላማ ሀገሩን ከውጭ ወራሪዎችና ከውስጥ ወንበዴዎች መከላከል ሆኖ ሳለ ጄኔራል ታሪኩ ረዳት ጦር ለወህኒ ቤቱ እንዳይደርስ በማድረጉ ወያኔ ታሳሪዎቹን በቀላሉ ለማስመለጥ ችሏል፤ በዚህም ጄኔራሉ የወንበዴዎቹ ዓላማ ተባባሪ ሆኗል” ይላሉ፡፡

 በተለይ ግን ጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም “ኦፕሬሽን አግአዚ”ን በምሬት ነው የሚያነሱት፡፡ ጓድ መንግሥቱ “ወያኔ በዚያ ድንገተኛ ወረራ ሊያመልጡ የማይገባቸውን ወንጀለኞች ለማስለቀቅ ችሏል” በማለት ለጋዜጠኛ ገነት አየለ አንበሴ ነግረዋታል፡፡ ሆኖም ለወንበዴዎቹ ድጋፍ ሰጥተዋል በተባሉት ጄኔራል ታሪኩ ዐይኔ ላይ መጥፎ እርምጃ አልተወሰደም፡፡ ጓድ መንግሥቱ ይህንንም ሲያብራሩ “የታሪኩ ጓደኛ የሆኑ የጦር መሪዎች በአማላጅነት ወደኔ መጥተው “ጓድ ሊቀመንበር! ታሪኩን በዚሁ ብቻ ከምንመዝነው ወደ ኤርትራ ይላክና ችሎታውን ያሳይ” ስላሉኝ እኔም ቃላቸውን በመቀበል ወደ አፋቤት ልኬዋለሁ” ብለዋል (ሆኖም ጄኔራል ታሪኩ ወደ አፋቤት ቢቀየርም ከአራት ዓመታት በኋላ ተረሽኗል)፡፡

እነ ሃየሎም አርኣያ በበኩላቸው በጄኔራል ታሪኩ ላይ የቀረበውን ክስ አይቀበሉም፡፡ ሃየሎም ስለጉዳዩ ሲናገር “ጄኔራሉ ጦሩን ለማንቀሳቀስ ያልቻለው በእንዝህላልነት ሳይሆን የኛ ጦር በመቀሌ ከተማ የተለያዩ ስፍራዎች የማዘናጊያ ውጊያዎችን በመክፈቱ መደበኛው ወታደር በነዚያ ውጊያዎች ስለተወጠረ ነው፤ እኛም የማዘናጊያ ውጊያዎቹን ሽፋን በማድረግ ያለምንም ስጋት እስረኞቹን ለማስለቀቅ ችለናል” ብሏል፡፡ 

   “ኦፕሬሽ አግዓዚ”ን በተመለከተ አከራካሪ ሆኖ የዘለቀ አንድ ጉዳይ አለ፡፡ ይህም ኦፕሬሽኑን ለማካሄድ የወሰደውን ጊዜ የሚመለከት ነው፡፡ ጄኔራል ሃየሎም አርኣያ “ኦፕሬሽኑ የተካሄደው በአስራ አምስት ደቂቃ ውስጥ ነው፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ስራችንን ሙሉ በሙሉ መጨረስ እንደምንችል ያወቅነው ስልጠናው በሚካሄድበት ወቅት ነው” ብሏል፡፡ የደርግ ባለስልጣናት ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ዘርዘር ያለ ነገር ባይጽፉም ኦፕሬሽኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ መፈጸሙን በደፈናው ያምናሉ፡፡  (በነገራችን ላይ የ“ኦፕሬሽን አግአዚ”ን ታሪክ መሰረት ያደረጉ ሁለት ፊልሞች ተሰርተዋል፤ አንደኛውን ፊልም ያዘጋጀው ታዋቂው አርቲስት ኪሮስ ኃይለ ሥላሤ ሲሆን የሁለተኛውን ፊልም አዘጋጅ ማንነት በትክክል አላውቅም፤ ሆኖም ሁለቱ አዘጋጆች “ኦሪጂናሌው ታሪክ የኔ ነው” በሚል ውዝግብ ፈጥረው እንደነበረ አስታውሳለሁ)፡፡
*****
ሃየሎም አርኣያ የተገደለው በየካቲት ወር 1988 ነው፡፡ ታዲያ የርሱ ሞት ከፍተኛ የመነጋገሪያ ርዕስ ሆኖ ነበር፡፡ በኦፊሴል የወጣው የኢትዮጵያ መንግሥት መግለጫ አሟሟቱን ሲያስረዳ “ጄነራል ሃየሎም አርኣያ ጀሚል ያሲን ከሚባል ኤርትራዊ ወጣት ጋር በተፈጠረ ጸብ ተገድሏል” ነው ያለው፡፡ ጥቂት የማይባሉ ሰዎች ግን የሞቱን ምክንያት ሲያስረዱ “ኤርትራ በሓኒሽ ወደቦች ምክንያት ከየመን ጋር በተጣላችበት ወቅት ሃየሎም አርኣያ “ከኤርትራ መንግስት ጋር ያለን ግንኙነት እንደማንኛውም ኢንተርናሽናል ግንኙነት መታየት አለበት፤ በተለይም በወታደራዊ መስክ ያለን ግንኙነት በሀገራችን ላይ አደጋ የሚጋብዝ መሆን የለበትም፤ ከኤርትራ ጎን ሆነን የምንዋጋበት ምክንያት ሊኖር አይገባም” የሚል አቋም በማራመዱ የሻዕቢያ ጥይቶች ሰለባ ለመሆን በቅቷል” ብለው ነበር፡፡ እነዚህ ወገኖች “የሃየሎም አርኣያ ገዳይ ኤርትራዊ መሆንም ይህንኑ ያረጋግጣል” በማለትም አክለዋል፡፡ ከዚህም አልፎ “በስልጣን ላይ የነበረው የአቶ መለስ ዜናዊ አመራር የግድያው ተባባሪ ነው” የሚሉ በርካታ ሰዎች አሉ፡፡

  ሃየሎምን ተኩሶ የገደለው ወጣት ጀሚል ያሲን ከመሞቱ በፊት ከእፎይታ መጽሔት ጋር ባደረገው ቃለ-መጠይቅ “በምሽቱ ሐሺሽ ወስጄ ነበር፤ በሐሺሽ ተገፋፍቼ ነው የገደልኩት እንጂ የተለየ ጠብ ኖሮን አይደለም” የሚል ቃል ነው የተናገረው፡፡ ሃየሎም በሞተበት ወቅት በአጠገቡ የነበሩት ሰዎችም “ወጣት ጀሚል በስካር ጥንብዝ ብሎ ሃየሎምን በባለጌ ስድቦች ይሳደብ ነበር፤ ሃየሎም ለረጅም ጊዜ ከታገሰው በኋላ ትዕግስቱ ሲያልቅበት ሁለት ጥፊ አቀመሰው፣ በዚህ የተናደደው ጀሚል ሽጉጡን ከመኪናው ውስጥ አምጥቶ ገደለው” የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡

  መንግሥታት በርካታ ጉዳዮችን ሚስጢራዊ ማድረጋቸው የተለመደ ቢሆንም የሃየሎም ሞት ሙሉ በሙሉ ሚስጢራዊ ሆኖ ቀርቷል ለማለት ምንም ዋስትና የለንም፤ እንዲህ የምንለው ከበርካታ ማዕዘናት በመነሳት ነው፡፡ ለምሳሌ የህወሐት (ኢህአዴግ) ባለስልጣናት በየጊዜው ፓርቲውን ለቀው ይኮበልላሉ፡፡ ሆኖም ከነዚያ ባለስልጣናት መካከል አንዳቸውም ቢሆኑ “ሃየሎም ሻዕቢያ በሸረበው ሴራ ነው የተገደለው” በማለት ሲናገሩ አልሰማናቸውም፡፡ ከአቶ መለስ ጋር ተጋጭተው ከድርጅቱ የወጡትና ከመለስ በላይ ሃየሎምን በቅርበት የሚያውቁት አቶ አረጋዊ በርሀም አቶ መለስን በሃየሎም ግድያ ሲከሷቸው አልተሰሙም፡፡ ከህወሐት ጋር ታሪካዊ ጠላት ሆነው የዘለቁት አቶ አብረሃም ያየህም “ኤርትራ ኢትዮጵያን የወረረችው በአቶ መለስ ዜናዊ አደፋፋሪነት ነው” እያሉ ቢጽፉም ለሃየሎም ሞት ሻዕቢያንም ሆነ አቶ መለስ ዜናዊን ተጠያቂ ሲያደርጉ አላየናቸውም፡፡ ከህወሓት ያፈነገጡት እነ ተወልደ ወልደማሪያምና ስየ አብረሃም ለሻዕቢያ ወረራ በየጊዜው የአቶ መለስን ቡድን ተጠያቂ ማድረጋቸው እንደተጠበቀ ሆኖ የሃየሎምን ግድያ ከኤርትራ ጉዳይ ጋር  ሲያገናኙት አልተደመጡም፡፡

ሻዕቢያ ሃየሎምን አስገድሎት ሊሆን ይችላል የሚሉ ሰዎች በበኩላቸው “ሴራውን ይገልጻሉ” የሚሏቸውን አንዳንድ ምልክቶችን ይደረድራሉ፡፡ ለምሳሌ ሃየሎም ከሞተበት ዕለት ጀምሮ የኤርትራ ሚዲያዎችና ዌብሳይቶች ሰውዬውን በጀግንነቱ ሲያደንቁት እንጂ በአሉታዊ መልኩ ሲያነሱት አይታዩም፡፡ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በሚካሄድበት ወቅት እንኳ የኤርትራ ሬድዮ “የአቶ መለስ አገዛዝ ሃየሎምን የመሰለ የጦር ጀግና ያስበላ የወንበዴ ቡድን ነው” ይል ነበር፡፡ እናም በርካታ ሰዎች “እነዚህ የኤርትራ ሚዲያዎች ሃየሎምን የሚያደንቁት የግድያው ሚስጢር እንዳይወጣ ለማፈን ቢሆንስ?” የሚል የጥርጣሬ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

 በኛ በኩል “ተጨባጩ እውነታ ይህ ነው” ብለን ምስክርነት መስጠት አንችልም!! በግድያው ዙሪያ በኢንተርኔትም ሆነ በፕሬስ ሲጻፍ የነበረው ሁሉ ጥርጣሬ እንጂ ሐቅ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ጥርጣሬ እውነትም ሊሆን ይችላል፤ ውሸትም ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም የታሪክ ተመራማሪዎች  አንድ ቀን ሐቁን ያሳውቁናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን!! በዚህ አጋጣሚ የማንክደው ነገር ቢኖር ሃየሎም አርኣያ የጦር ሜዳ ጀግና የነበረ መሆኑን ነው፡፡
----
  አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 7/2007
ገለምሶ-ሀረርጌ

Tuesday, December 9, 2014

ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለማሪያም እና የሀይሌ ፊዳ ሞት




አፈንዲ ሙተቂ
------

ዶ/ር ሃይሌ ፊዳ በፎቶግራፉ ላይ የምትመለከቱት ነው፡፡ ፎቶውን የሰጡን አንጋፋው ደራሲ አበራ ለማ ናቸው፡፡ ጋሼ አበራን እያመሰገንን በሃይሌ ፊዳ አሟሟት ዙሪያ የተጠናቀረውን ይህንን ጽሑፍ ጀባ ብለናችኋል፡፡

                                                                          *****
ኮ/ል መንግሥቱ ሀይለማሪያም “ሀይሌ ፊዳ የተገደለው በገበሬዎች ነው” ባይ ናቸው፡፡ ከጋዜጠኛና ደራሲ ገነት አየለ ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ የሀይሌ ፊዳን ሞት እንዲህ በማለት አስረድተዋል፡፡

ገነት፡ ሀይሌ ፊዳስ? በነሐሴ 1970 ተይዞ ከአንድ ዓመት በኋላ ነገር ከበረደ፤ ሁሉ ነገር ከተረጋጋ በኋላ ነው የተገደለው፡፡ በዚያን ጊዜ የኃይሌ ፊዳ በህይወት መኖር መንግሥትን ያሰጋ ነበር?

መንግሥቱ፡ መቼ ነው የሞተው ሀይሌ ፊዳ?

ገነት፡ በሀምሌ 1971 ነው::

መንግሥቱ፡ ማነው የገደለው?

ገነት፡ እኔ ምን አውቃለሁ? አስከሬኑ ከቀድሞው የራስ አስራተ ካሣ ግቢ ነው ተቆፍሮ የወጣው፡፡ እዚያ ነው የተገኘው፡፡

መንግሥቱ፡ ሀይሌ?

ገነት፡ አዎን! ሀይሌ ፊዳ፡

መንግሥቱ፡ እዚያ ምን ሲሰራ?

ገነት፡ እዚያ ነው አስከሬኑ የተገኘው፡፡

መንግሥቱ፡ እኔ አላውቅም፡፡

ገነት፡ መሞቱንም አያውቁም? እርሱንም እዚህ ከመጡ በኋላ ነው የሰሙት?

መንግሥቱ፡ መኢሶኖች እኮ ጥለውን ሄደዋል፡፡ የሶማሊያ ጥቃት አይሎ ሲመጣ የሻዕቢያዎች ጎራ ስለጠነከረ ከዚህ ከደከመ መንግሥት ጋር ምን እንሰራለን ብለው አይደል እንዴ ጥለው የነጎዱት? በነሱ ሃሳብ እኛ በመዳከማችን ወደፊት ከኛ ጋር በመቀጠል የስልጣን ጥማታቸውን የሚያረኩበት መንገድ ስለማይኖር ልዩ ልዩ ምክንያት ሲያቀርቡ ቆይተው በመጨረሻ ፈርጥጠዋል፡፡ በዚህን ጊዜ እነ መስፍን ካሱ ወደ ሲዳሞ፡ እነ ሀይሌ ፊዳ ወደ ወለጋ ሲሄዱ አግኝቶ ገበሬ ነው የከሰከሳቸው፡፡

ገነት፡ እዚያ ነው የተገደሉት?

መንግሥቱ፡ በሙሉ!

(ገነት አየለ አንበሴ፡ የሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም ትዝታዎች፡ 1984፣ ገጽ 207-208)
                                                                          *****
ሊቀመንበር መንግሥቱ “የሀይሌ ፊዳን መሞት ሰው ነው የነገረኝ” ነው የሚሉት፡፡ ነገር ግን ሀይሌ በነሐሴ 1969 ከተያዘ በኋላ በደርግ ምርመራ ክፍል ሲሰቃይ ቆይቶ እንደተገደለ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ማስረጃ የሆነውንና ሀይሌ ከመሞቱ በፊት የሰጠውን ባለ 36 ገጽ የምርመራ ቃል በልዩ ልዩ መንገዶች ታትሞ አንብበነዋል፡፡ ከሀይሌ ጋር በአንድ ክፍል ታስረው የነበሩ ጓዶችም ሀይሌ በዚያ ወር እንደተገደለ ተናግረዋል፡፡ የደርግ የቅርብ ሰው የነበሩት አቶ ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ) “ነበር” በሚል ርዕስ በጻፉት ባለሁለት ቅጽ መጽሐፍ የምርመራ ቃሉን ከማተማቸውም በላይ ሀይሌ ከሱሉልታ ኬላ ተይዞ ወደ ደርግ ጽ/ቤት በመጣበት ወቅት በብሄራዊ ቤተመንግሥት እንዳዩት መስክረዋል፡፡
    

  በዚህም መሰረት “ሊቀመንበር መንግሥቱ ሀይሌን በእርግጥ ገድለውታል ወይ?” የሚለው ጥያቄ ለአሁኑ ዘመን አይሰራም፡፡ “መንግሥቱ ሀይሌን ለምን ገደሉት?” የሚለው ግን አሁንም ያከራክራል፡፡ ገነት አየለ እንደገለጸችው ሀይሌ በተገደለበት ወቅት ነገሮች ሁሉ በጣም በርደዋል፡፡ የሶማሊያ ወራሪዎች ከምስራቅ ኢትዮጵያ ከተባረሩ አንድ ዓመት አልፎአቸዋል፡፡  ሻዕቢያና ጀብሃ በሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ክፉኛ ተደቁሰው ወደ ሱዳንና ወደ ሳሕል በረሃ ገብተዋል፡፡ ከነዚህ ሁለት ክስተቶች ቀደም ብሎም ሀገር ያተራመሰውና ሺዎችን የቀሰፈው የቀይ ሽብር ዘመቻ ደርግ በሚፈልገው መልኩ ተጠናቋል፡፡ አብዮታዊው መንግሥት ከዚያ በፊት ያላየው ሰላምና እርጋታ በሀገሪቱና በሁሉም የስራ መስኮች ሰፍኗል፡፡ ታዲያ በዚህ ሰላማዊ ወቅት ሀይሌ ፊዳን ማስገደሉ ለምን አስፈለገ?
  
  
በርካታ ተመልካቾች የየራሳቸውን ግምት አስቀምጠዋል፡፡ አንዳንዶች ነገሩን ከቂም በቀል ጋር ያያይዙታል፡፡ “መንግሥቱ አንድ ቀን የገላመጠውን እንኳ የማይምር ቂመኛ ነው” -ይላሉ እነዚህ ወገኖች፡፡ የተወሰኑት ደግሞ መንግሥቱ በችሎታና በእውቀት ከርሱ የሚበልጥ ሰው ከታየው ወደፊት ስልጣኔን ይነጥቀኛል በሚል እንደሚያስገድለው ያወሳሉ፡፡ እነዚህኛዎቹ ክርክራቸውን ሲቀጥሉ “መንግሥቱ ሀይለማሪያም ሀይሌ ከእስር ቢለቀቅ ወይም ቢያመልጥ የራሱን ቡድን አደራጅቶ ወይ አንዱን ጄኔራል ተጠግቶ ከስልጣኔ ሊያሽቀነጥረኝ ይችላል” የሚል ፍራቻ ነበረው” ባይ ናቸው፡፡
     

   ከሁለቱ ወገኖች የሚለይ አስተያየት የሚሰጡ ጸሐፊያንና የታሪክ ሰዎችም አሉ፡፡ እነዚህኛዎቹ እንደሚሉት ኮሎኔል መንግሥቱ ሃይለማሪያም በሀይሌ ጉዳይ ላይ የሞት ውሳኔ ያሳለፉት እርሳቸውን ያስደነገጠ አንድ አደገኛ ክስተት ስለተፈጠረ ነው፡፡ እስቲ ታሪኩን አብረን እንየው፡፡
                                                                          *****

     ሊ/ር መንግሥቱ ለጉብኝት ወደ ኩባ ይጋበዛል፡፡ ከጓድ ፊደል ካስትሮ ጋር ጉብኝትና ስብሰባውን ማካሄድ ይጀምራል፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን ለስራ ጉዳይ ወደ ውጪ ሀገር በመሄዱ ህይወቱ ለጥቂት የተረፈችው የመኢሶኑ ዶ/ር ነገደ ጎበዜ አዲስ አበባ መግባቱ ይነገረዋል፡፡ “እንዴት መጣ?” ብሎ ቢጠይቅ “የደቡብ የመንን ፓስፖርት ይዞ፤ ከደቡብ የመን ልዑካን ጋር ተቀላቅሎ” ሆነ መልሱ! (ደቡብ የመን አሁን ከሰሜን ጋር ተዋህዳለች)፡፡ “ዶ/ር ነገደ ተይዟል ወይ?” ብሎ ሲጠይቅ አለመያዙ ተነገረው፡፡ ያለበትን ቦታ ጠይቆ የተሰጠውን መልስ ሲሰማ ደግሞ ሊ/ር መንግሥቱ በድንጋጤ ፈዝዞ ቀረ!
                                                                          *****
 በርግጥ ዶ/ር ነገደ አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ ነገር ግን መጥፎ አጋጣሚ ሆኖ ድሮ ከሚያውቀው የኤርፖርት ደህንነት ሃላፊ ጋር አይን ለአይን ተገጣጠመ፡፡ ደህንነቱ ነገሩን ወዲያኑ ለደርጎች አስታወቀ፡፡ ደርጎችም ነገደ ጎበዜን ለመያዝ ተንቀሳቀሱ፡፡ ሆኖም ዶ/ሩ ኩባ ኤምባሲ ገብቶ ተደበቀ፡፡ ሁኔታው ለጓድ ፊደል ካስትሮ ሲነገራቸው ካስትሮ አማላጅ ሆኑና በነገሩ ውስጥ ገቡ፡፡ በርሳቸው ተማጽኖም ዶ/ር ነገደ ከኤምባሲው ወጥቶ ወደ አውሮጳ ተመለሰ፡፡
  

   ይህ ድርጊት የተከሰተው የሶማሊያ ወረራ ካበቃ ከጥቂት ወራት በኋላ ነበር፡፡ ደርጎች ነገሩን እንደ ኩዴታ ነው የወሰዱት፡፡ ለዚህም ነው በውስጣቸው ከፍተኛ መሸበር የተፈጠረው፡፡ እርግጥ ሀገራቱ ኩዴታ እናድርግ ቢሉ የማስፈጸም አቅሙ ነበራቸው፡፡ በወቅቱ የ"ሶማሊያን ወረራ ለመቀልበስ በተደረገው ዘመቻ አብዮታዊ አጋር ሆኖ የመጣው የኩባ ሀያ ሺ ሜካናይዝድ ጦርና የየመን ሁለት ሺህ መድፈኛ ጦር ኢትዮጵያ ውስጥ ስለነበሩ እነርሱን ይዘው አንድ ነገር ማድረግ ይችሉ ነበር ተብሎ ይገመታል፡፡ የዘመኑ ሀያል ሶሻሊስት ሀገር የሆነችውን ሶቪየት ህብረትንም ለእርዳታ ቢጠሯት “በጄ” ከማለት የምትመለስ አይሆንም-ከመንግሥቱ ይልቅ ኩባና ደቡብ የመን ይበልጡባታልና፡፡ ሆኖም የዶ/ር ነገደን መምጣት ብቻ በማየት “ኩዴታ” ተጠንስሷል ለማለት ይከብዳል፡፡


     ሊ/ር መንግሥቱ በዚህ መረጃ ላይ በመመርኮዝ “ኩዴታ” እንደታቀደባቸው አሰመሩበት፡፡ ሀገራቱ ፈጸሙብኝ ላሉት በደል ደግሞ ቀጥተኛ ምላሽ ከበዳቸው -ምክንያቱም የክፉ ቀን ወዳጆች ናቸውና፡፡ በሌላ በኩል ግን ሊቀመንበሩ ቁጭታቸውን መዋጥ አቃታቸው፡፡    ለምን ቢባል እንኳንስ እንዲህ ዓይነቱን ምልክት አግኝተው ይቅርና በጥርጣሬ ብቻ ብዙዎችን ቀስፈዋልና፡፡ የቀይ ሽብሩ ትርዒት ሳይደመር የተፈጁትን ሰዎች ቤት ይቁጠረው፡፡ ሌ/ኮ/ አጥናፉ አባተን “ለሀገራችን ሶሻሊዝም አይጠቅማትም፤ እንደ ዩጎዝላቪያ የቅይጥ ኢኮኖሚ መርህ መከተል አለብን” በማለታቸው ብቻ አስገድለዋቸዋል፡፡ “ለኤርትራ ጥያቄ ሰላማዊ መፍትሔ ያስፈልጋል” ያሉ በርካታ ጓዶቻቸውን አስረሽነዋል፡፡ አቡነ ቴዎፍሎስ፣ ቄስ ጉዲና ቱምሳ እና ሼኽ ሰይድ ቡደላ (የአብሬት ሼኽ) የመሳሰሉ የሀይማኖት አባቶች ያለ አንዳች ምክንያት ተገድለዋል፡፡ ከዚህ አንጻርም ለዶ/ር ነገደ ጎበዜ ድፍረት የሚሰጡት ቅጣት ከፍተኛ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ግን ዶ/ር ነገደ አልተያዘም፡፡ ስለዚህ ቁጭቱ በምን ይውጣላቸው?


    እንግዲህ በአንዳንዶች እምነት ዶ/ር ሀይሌ ፊዳ የተገደለው በዚህ እርግጠኛነቱ ባልታወቀ የዶ/ር ነገደ ጎበዜ “ኩዴታ” ጦስ ነው፡፡ ኩባና የመንን መበቀል ሲያቅታቸው ቁጭታቸውን በግቢአቸው ባጎሩት እስረኛ ላይ ተወጡት፡፡ ሀይሌን በአንድ ቀዝቃዛ ምሽት አሰናበቱት፡፡
                                                                          *****

     በቅርብ ጊዜ የተገኙ መረጃዎች ግን ከላይ የቀረበውን ታሪክ ዋጋ ቢስ አድርገውታል፡፡ እነዚህ መረጃዎች እንደሚሉት ዶ/ር ነገደ ጎበዜ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው የመጡት በሊቀመንበር መንግሥቱ እውቅና ነው፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ ባሳተሙት መጽሓፋቸው “ነገደ ጎበዜ በመንግሥቱና በኩባዊያን እውቅና መምጣቱን ነግሮኛል” በማለት ጽፈዋል፡፡ ከአሜሪካ የስለላ ምንጮች የተገኘው መረጃም ይህንኑ ያረጋግጣል፡፡ ስለዚህ ደርጎች “መፈንቅለ መንግሥት ሊካሄድ ነበር” እያሉ ወከባ ይፈጥሩ የነበረው ህዝቡንና የተቃዋሚውን ክፍል ለማደናገርና የበለጠ ጸጥ ለማድረግ ነው ማለት ነው፡፡ የሀይሌ ፊዳ ግድያም ከመፈንቅለ መንግሥቱ ጋር አንዳች ግንኙነት አልነበረውም፡፡

  
     በአንጻሩ ደግሞ ሀይሌ ፊዳ የተገደለበት ሀምሌ 1971 በውል ሊመረመር የሚገባው የታሪክ ወቅት ሆኖ ሳለ ምሁራን በጥልቀት ሳያስሱት መቅረታቸው ይገርማል፡፡ ይህ ወር መንግሥቱ ከቀይ ሽብርና ነጭ ሽብር የተረፉ በርካታ ተቃዋሚዎቹን፣ አማካሪዎቹንና ታዋቂ ግለሰቦችን በድብቅ የገደለበት ጊዜ ነበር፡፡ እነ አቡነ ቴዎፍሎስን ጨምሮ የኢህአፓው ብርሀነ መስቀል ረዳ፣ የመኢሶኖቹ ከበደ መንገሻ፣ ንግሥት አዳነ፣ ደስታ ታደሰ፣ መስፍን ካሱ ወዘተ… በዚሁ ጊዜ ነበር የተገደሉት፡፡ “የማዕከል” ጥያቄ ደርጎችን ያናቆረው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ ኢማሌድህ የሚባለውን የማርክሲስቶች ህብረት ከመሰረቱት አምስት ድርጅቶች (አብዮታዊ ሰደድ፣ መኢሶን፣ ወዝሊግ፣ ኢጭአት እና ማሌሪድ) መካከል መንግሥቱ ከሚመሩት “ሰደድ” ጋር በመድረኩ ላይ የቀረው የማሌሪድ መሪ ተስፋዬ መኮንን የታሰረውና የማሌሪድ ግብአተ ሞትም የተፈጸመውም በዚህ ወር ነበር፡፡ ስለዚህ ያ ታሪካዊ ወቅት የምሁራን እይታ ሊያርፍበት ይገባል፡፡
------
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 21/2006

አንጋፋው ሻዕቢያ



ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-------
   


 አትሳሳቱ! በምስሉ ላይ የምትመለከቱት ሰው ዐረብ አይደለም፡፡ ኢራናዊም አይደለም፡፡ ህንዳዊም አይደለም፡፡ በቀዳሚ ዘመኑ የኢትዮጵያ ፖስፖርት ነበረው፡፡ በኋላ ላይ ግን “ኤርትራ ነጸ መውጣት አለባት” ብሎ ኤርትራዊነትን ሰብኳል፡፡ ለዚህም በረሃ ወርዶ ብረት አንስቷል፡፡ በውጪ መዲናዎች “ሓርነት” እያለ ጮኋል፡፡ ይሁንና ያሰበው ከግቡ ሳይደርስለት ይህቺን ዓለም ተሰናብቷል፡፡ በአንድ ወቅት እርሱ ይመራቸው የነበሩ ወጣቶች ግን ዓላማውን አሳክተዋል፡፡
                                                                          *****
     “ጀብሃ” እና “ሻዕቢያ” በሚል ርዕስ የቀረበውን ተከታታይ ጽሑፍ ተከታትላችኋልን? እንዲያ ከሆነ “ሻዕቢያ” የተሰኘው ድርጅት ከጀብሃ ተገንጥሎ በሁለት እግሩ እንዲቆም የረዳው አንድ አደገኛ “ዲፕሎማት” እንደሆነ ተረድታችኋል ማለት ነው፡፡ ያ “ዲፕሎማት” በምስሉ ላይ የምትመለከቱት ሰው ነው፡፡ የዚህ ሰው ልደት የተበሰረው በሞቃት አየሯ በምትታወቀው ውቢቷ የምጽዋ ከተማ አጠገብ ባለችው “ሀርጊጎ” በተሰኘች ባህረ-ገብ መንደር ነው፡፡ ወላጆቹ በምሥራቅ ኤርትራ ከሚኖሩት የአሳውርታ (ሳሆ) ብሄረሰብ ነው የተገኙት:: የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በምጽዋ ካገባደደ በኋላ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአዲስ አበባ ከተማ አጠናቋል፡፡ በ1950ዎቹ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ በመምህርነት ተመርቋል፡፡ በስራው ዓለም ወደ ምጽዋ ከተማ ተመልሶ በትምህርት ቤት ዳይሬክተርነት አገልግሏል፡፡ በዚህ ሙያ ላይ እያለም ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትቀላቀል ሲደረግ እርምጃውን የተቃወመው “ማህበር ሸውአተ” (ሀረካ) አባል ሆኗል፡፡ በ1961 “ተጋድሎ ሐርነት ኤርትራ” (ጀብሐ) ሲመሰረት ደግሞ ከሀረካ ወጥቶ ጀብሃን ተቀላቅሏል፡፡ ድርጅቱንም ለረጅም ጊዜ በውጪ ጉዳይ ኃላፊነት አገልግሏል፡፡ ድርጅቱ እስከ አሁን ድረስ የሚታወቅበትን “ሰውራ” የተሰኘ መጽሔት መስርቷል፡፡ ከ1970 በኋላ ግን የድርጅቱን አካሄድ በመቃወም “ህዝባዊ ሀይሊ” የተሰኘ ንቅናቄ ጀምሯል፡፡ ይህንን ቡድን “ሰልፊ ነጻነት” ከተሰኘው የደገኛ ኤርትራዊያን ቡድን ጋር በማዋሃድ በታሪክ ገጾች “ህዝባዊ ሓርነት ሀይልታት” ወይንም “ሻዕቢያ” የተሰኘውን ጥምረት መስርቷል፡፡ ጥምረቱንም እንደ “ውስጠ ዘ” (defacto) ሊቀመንበር እና እንደ ውጪ ጉዳይ ሃላፊ ሆኖ አገልግሏል፡፡ በስተመጨረሻው ግን ከወጣቶቹ ጋር መግባባት ስላልቻለ በልዩነት ተሰናብቷል፡፡

     ይህ ሰው እ.ኤ.አ. በ1978 ከጀብሃ ጋር በጋራ አብሮ የመስራት ስምምነት የተፈራረመ ሲሆን በ1980 ገደማም የርሱን መስመር ከሚከተሉ ሌሎች ታጋዮች ጋር “ህዝባዊ ሓርነት ሀይልታት ሰውራዊ ባይቶ” የተሰኘ ድርጅት መስርቶ ነበር፡፡ ሆኖም በወቅቱ “ሻዕቢያ” የተሰኘው ግንባር ከርሱ ጋር በሀሳብ የተለዩትን ድርጅቶች እያሳደደ ይመታ ስለነበር ወደ ሀገር ቤት ገብቶ የትጥቅ ትግል ለመጀመር አልቻለም፡፡ ቢሆንም ሰውዬው በፖለቲካው መስክ አልሰነፈም፡፡ በውጪው ዓለም ከፍተኛ የዲፕሎማሲ ትግል ማድረጉን ቀጥሏል፡፡ በ1987 ግን ይህችን ዓለም ተሰናብቷል፡፡
                                                                          *****
  ሰውየውን አውቃችሁታል አይደል? አዎን! ዑስማን ሳልህ ሳቤ ነው፡፡ ዛሬ በኢሳያስ የሚመራውን ህዝባዊ ግንባር (ሻዕቢያ) የመሰረተው እርሱ ነው፡፡ ይህ ሰው በታሪክ ምሁራን እጅግ ከፍተኛ ችሎታ ያለው ፖለቲከኛ ተብሎ ነው የሚጠቀሰው፡፡ በርካታ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ድርጅቶች በጨቅላነታቸው ዘመን የርሱ እርዳታ በእጅጉ አስፈልጎአቸዋል፡፡ የኢህአፓ ታጋዮች የትጥቅ ትግል እንዲጀምሩ ያበቃቸውን ስልጠና ያገኙት በርሱ አማካኝነት ነው፡፡ ከአስር የማያንሱ ጠመንዣዎችንም ያስገኘላቸው እርሱ ነው፡፡ የኦነግ ጠንሳሾች የሚባሉት እነ ጃራ አባገዳ በመሳሪያ ተደራጅተው ትግሉን ለመጀመር የበቁት እርሱ ባደረገላቸው እርዳታ ታግዘው ነው፡፡ ለሌሎችም እንዲሁ የእርዳታ እጁን ዘርግቷል፡፡

  “ሻዕቢያዎች” ከዑስማን ሳልህ ሳቤ ጋር መጣላታቸው እሙን ነው፡፡ በአንድ ዘመን ሀይለኛ የፕሮፓጋንዳ ጦርነት አካሂደውበታል፡፡ ከነጻነት በኋላ ግን በትግሉ ላበረከተው አስተዋጽኦ እውቅና ሰጥተዋል፡፡ በርሱ ስም ትምህርት ቤትና ጎዳና ሰይመዋል፡፡ ይህም ከጀብሃ ጋር ንክኪ የነበረው ማንኛውም ግለሰብ ያላገኘው እድል ነው፡፡ ከርሱ ጋር ይህንን እድል በጥቂቱ ለመጋራት የቻለው አንጋፋው የጀብሃ ታጋይ ኢድሪስ ገላውዴዎስ ብቻ ነው፡፡
 -----
አፈንዲ ሙተቂ
ታሕሳስ 1/2006

Monday, December 8, 2014

“አሕመድ ያ ሐቢቢ”



ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
-------
አንዳንዶች “ነቢዩ ሙሐመድን (ሰ.ዐ.ወ) ትጠላላችሁ፤ በነቢዩ ላይ ሰለዋት አታወርዱም” ይሉናል፡፡ ሐቁ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ በነቢዩ ላይ ሰላምና ሰለዋት በማውረድ ከኛ የሚቀድም ማን ነው? እንዲያውም የነቢዩን ታላቅ ደረጃ በዜማ እየዘከርን እና ገድላቸውን እየተረክን ነው በርሳቸው ላይ ሰላምና ሰለዋት የምናወርደው:: ይህንን እውነታ ያስረዳልን ዘንድ የሱፊ ሼኾቻችን ትተውልን ያለፉትን አንድ “ነሺዳ” (የነቢዩ ውዳሴ”) እንጋብዛችሁ፡፡
  *****  *****  *****
    ነሺዳው መጠሪያ “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ይሰኛል፡፡ “አሕመድ ወዳጄ ሆይ” እንደማለት ነው፡፡ እኛ ስናሰፋው “ አሕመድ የልቤ ወዳጅ”፤ “አሕመድ የነፍሴ ስር” ልንለው እንችላለን፡ (“አሕመድ” የነቢዩ ሙሐመድ -ሰ.ዐ.ወ- ሁለተኛ ስም ነው፡፡ ነቢዩ በመጨረሻው ቀን/የውመል ቂያማ የሚጠሩት አሕመድ በተሰኘው ስማቸው ነው)፡፡
    
   ይህንን “ነሺዳ” ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት በ1995 ዓ.ል. ይመስለኛል፡፡ ነሺዳውን በህብረት ሲዘምሩ የነበሩት መሰረቱን በኦምዱርማን ከተማ ባደረገውና “ፊርቀቱ-ሳሕዋ” በሚባለው ዝነኛ የሱዳን የነሺዳ ቡድን የታቀፉት ስድስት ወጣቶች ነበሩ፡፡ የቡድኑ አባላት የሚያዜሙት በአብዛኛው በታዋቂው ሼኽ ዐብዱረሒም አል-ቡረኢ የተጻፉትንና “መዲሕ” የሚባሉትን የነቢዩን ግጥማዊ መወድሶች በመሆኑ “አሕመድ ያ ሐቢቢ”ም የሼኽ አል-ቡረኢ ድርሰት ይመስለኝ ነበር፡፡ በ2001 ወደ ሀረር ከመጣሁ ወዲህ ግን “አሕመድ ያ ሐቢቢ” በአንድ ዘመንና በአንድ ስፍራ ያልተገደበ ውዳሴ እንደሆነ ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ለዚህ ያበቃኝ ደግሞ በቀድሞ ዘመናት የተጻፈ አንድ “የመዲህ” ኪታብ (መጽሐፍ) በሀረር ለማየት መታደሌ ነው፡፡

     በርግጥም “የፊርቀቱ ሳሕዋ” ወጣቶች የሚዘምሩት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” እና ከሀረር ያገኘሁት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” አንድ መሰረት ያላቸው መሆኑን ከግጥሞቹ አሰካክ ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሆኖም በመካከላቸው መጠነኛ ልዩነቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ ሱዳናዊያኑ ወጣቶች “አሕመድ ያ ሐቢቢ” በሚል ሐረግ የሚጀምረውን ባለሁለት መስመር ግጥም እንደ አዝማች አድርገው ይደጋግሙታል፡፡ የሀረሩ “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ግን አዝማች የለውም፤ በዚህኛው ስልት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” የሚለው ሐረግ አንድ ጊዜ ከታየ በኋላ አይደገምም፡፡ በሁለተኛ ደረጃም ሁለቱ የ“አሕመድ ያ ሐቢቢ” ስልቶች በግጥሞቻቸው ብዛት ይለያያሉ፡፡ የሀረሩ ስልት በኦምዱርማኑ ስልት ውስጥ የሌሉ ግጥሞቹ አሉት፡፡ በመሆኑም በግጥሞቹ ብዛት ከኦምዱርማኑ ስልት ይበልጣል፡፡
  
   የሀረሩ ስልት በትርፍነት ከያዛቸው ግጥሞች ውጪ ባሉት ግጥሞቹ ከኦምዱርማኑ ስልት ጋር የመመሳሰል ነገር ይታይበታል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን በሁለቱ ስልቶች ያሉት ግጥሞች መቶ በመቶ የሚመሳሰሉበት ሁኔታ የለም፡፡ ግጥሞቹ አንዳንዴ በሁለት ስንኞቻቸው ብቻ ይመሳሰሉና በሶስተኛው ስንኝ ይለያያሉ፡፡ ሲያሻቸው ደግሞ በተመሳሳይ ሁኔታ እየተጓዙ በቃላት ደረጃ ይለያያሉ፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ሁሉም ስንኞች እኩል ርዝመት ነው ያላቸው፡፡ ሁላቸውም “ሰላም ዓለይከ” በሚል ሐረግ የሚጀምሩ መሆናቸው ደግሞ የነሺዳው ኪናዊ ውበት ምንጭ ሆኗል፡፡
 
   በዚህ መጣጥፍ የምጋብዛችሁ የኦምዱርማኑን “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ነው፡፡ ከኔ ጋር ነሺዳውን በ“ፊርቀቱ ሳሕዋ” ዜማ ለመዘመር ተዘጋጁ! ዳይ!!!
(ዐረብኛውን ወደ አማርኛ መተርጎም ይከብዳል፡፡ ስለዚህ እንዳለ ልተተው ተገድጃለሁ)፡፡
  *****  *****  *****
አሕመድ ያ ሐቢቢ ሰላም ዓለይከ
ያ ሚስኪ ወጢቢ ሰላም ዓለይከ
---
ሰላም ዓለይከ ዜይነል አንቢያኢ
ሰላም ዓሌይከ አትቀል አትቂያኢ
ሰላም ዓለይከ አስፉል አስፊያኢ
ሰላም አለይከ ሚን ረብቢ-ሰማኢ
ሰላም ዓለይከ ዳኢመን ቢላ ኢንቲሃኢ
ሰላም ዓለይከ
----
ሰላም ዐለል ሙቀደም ሊል ኢማማ
ሰላም ዐለል ሙዘለል ቢል ጘማማ
ሰላም ዐለል ሙዘወጅ ሊል ከራማ
ሰላም ዐለል ሙሰቢህ ሊል ሰላማ
ሰላም ዐለል ኹላሳ ሚን ቱሐማ
ሰላም ዐለል ሙሸፍፊዕ ቢልቂያማ
ሰላም ዓለይከ
-----
ሰላም ዐለይከ ጣሃ ያ ሐቢቢ
ሰላም ዐለይከ ያ ሚስኪ ወጢቢ
ሰላም ዐለይከ ያ -ማሂ ዙኑቢ
ሰላም ዐለይከ ያ ጃሊል ኩሩቢ
ሰላም ዓለይከ
 -----
ሰላም ዐለይከ ያ ኸይረል አናሚ
ሰላም ዐለይከ ያ በድረ ተማሚ
ሰላም ዐለይከ ያ ኑረል ዘላሚ
ሰላም ዐለይከ ያ ኩለል ጉራም
ሰላም ዐለይከ
----
ሰላም ዐለይከ ያ ዘል ሙእጂዛቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ዘል በይናቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ሐቢቡ ዛቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ሐሱነ-ስ-ሲፋቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ዙኽረል ዑሳቲ
ሰላም ዐለይከ
----
ሰላም ዐለይከ አሕመድ ያ ሙሐመድ
ሰላም ዐለይከ ያ ጣሃ ያ ሙመጀድ
ሰላም ዐለይከ ዘል መንተፈረጅ
ሰላም ዐለይከ
---
ሰላም ዐለይከ ያ ሩክነ-ሰላሂ
ሰላም ዐለይከ ያ ዘይነል ኢላሂ
ሰላም ዐለይከ ያ ዳኢል ፈላሒ
ሰላም ዐለይከ
---
አሕመድ ያ ሐቢቢ ሰላም ዓለይከ
ያ ሚስኪ ወጢቢ ሰላም ዓለይከ
  *****  *****  *****
አፈንዲ ሙተቂ
ሸገር- አዲስ አበባ
ጥቅምት 2/2006